Tuesday, March 27, 2012

የዋልድባ ገዳም መብት ለማስከበረ በዋሽንግተን ዲሲ ሰላማዊ ሰልፍ ተካሄደ


የአባቶቻችን ርስት እና ቅርስ ተጠብቆ ለትውልድ ይተላለፍ የሚል መሪ ቃል ያለው የአቤቶታ ሰላማዊ ሰልፍ የአሜሪካን መንግስት መቀመጫ በሆነችው 


 በዋሽንግተን ዲሲ በኢትዮጵያ ኤምባሲ ዛሬ መጋቢት172004 / በአካባቢው የሰዓት አቆጣጠር 9am ላይ ተካሄዶዋል:: በአቤቶታ ሰላማዊ ሰልፉ ላይበቦታው የተገኙ አባቶች በጸሎት አስጀምረዋል:: በሰልፉም ከአንድ ሺህ በላይ ክርስቲያኖች እንደተገኙ በአካባቢው የነበሩ ዘጋቢዎቻችን ገልጸውልናል:: በአቤቶታ ሰላማዊ ሰልፉም በአስተዳደር ምክንያት የተለያዩ ወገኖች በአንድነት የቤተ ክርስቲያን ህልውና የሚፈታተኑን ከድርጊታቸው እንዲቆጠቡ ጠይቀዋል:: ለአራት ሰዓታት ያህል የቆየው የአቤቶታው ሰልፍ በተለያዩ መዝሙራት የታጀበ ነበረ:: ተሳታፊዎቹም ጥያቄዎቻቸውን በእንባ እና በጩኸት ለኤምባሲው አሰምተዋል:: 

የጠቅላይ ሚንስተሩ /ቤት ከዋልድባ ገዳም በተወከለቱ የገዳሙ አባቶቻችን ላይ ያሳየውን ንቀት የዋሽንግተን ዲሲው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ለአቤቶታ በወጡ ክርስቲያኖች ላይ ንቀቱን ደግሞታል:: አቤቶታ አቅራቢዎች ለሦስት ሰዓታት ተኩል ያህል በኤምባሲው በር ላይ መብታችውን ሲጠይቁ ከኤምባሲው ማንንም ምንም የመንግስት ተወካይ ወጥቶ ሊያናግራቸው አልቻለም ነበር:: በመጨረሻም አንድ ተላላኪ ወጥቶ ዛሬ ሳይሆን ነገ እናግራችኋለን በማለት አሳፋሪ ምላሽ እንደሰጣቸው ዘጋቢዎቻችን ገልጸውልናል:: መንግስት በኢትዮጵያ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አማኞች ላይ እያደረገ ያለውን ንቀት በዋሽንግተን ዲሲ ባስቀመጣቸው ተወካዮቹ ጭምር ደግሞታል:: ታድያ ንቀቱ እስከ መቼ ድረስ ይሆን? 


ክርስቲያኖች በአላውያን ነገስታት ወይም በእምነት የለሽ ገዢዎቻቸው ጭቆና ሲበዛባቸው በጸሎት አምላካቸውን ከመማጸን በተጨማሪ ድምጻቸውን ለመንግስታት ማሰማት በአሐት አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ የተለመደ ነው:: የግብጽ፣ የአርመን እና የሶርያ ክርስቲያን ወንድሞቻችን በተለያዩ ጊዜያት በገዢዎቻቸው ጭቆና ሲደርስባቸው ለዓለም መንግስታት እና ለራሳቸውም መንግስታት በአቤቶታ ሰላማዊ ሰልፍ ጩኸታቸውን እንደሚያሰሙ በተለያዩ የዓለም አቀፍ የመገናኛ ብዙኃን ሲዘግቡ እንሰማለን:: በሕገ ክርስትና በኢ-አማኞች ጭቆና ሲደርባችሁ የአቤቶታ ሰላማዊ ሰልፍ አትውጡ የሚል ነገር የለም:: ስለዚህ ክርስቲያኖች የአቤቶ ታሰላማዊ ሰላማዊ ሰልፍ መውጣታችው ተገቢ ነው:: 

አቤቶታን ለዓለም መንግስታት ማቅረብ በአሐት አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ እንደተለመደው ሁሉ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክሳውያን ዘንደም መለመድ አለበት በማለት የሰላማዊ ሰልፍ አዘጋጆቹ በቦታው ለተገኙ ዘጋቢዎቻን ገልጸውላቸዋል:: 


በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያ ከአርባ ዓመት ወዲህ በተለያዩ ጊዜያት ክርስቲያኖች ሲታረዱ፣አብያተ ክርስቲያናት ሲቃጠሉ፣ ቅዱስ ፓትርያርኩ ለወህኒ ወርደው በግፍ ሲገደሉ እንደሌሎች እሕት አብያተ ክርስቲያናት የኢትዮጵያ ክርስቲያኖች ድምጻቸውን ለዓለም መንግስታት አላሰሙም ነበረ:: ይህ ዛሬ የተካሄደው የአቤቶታ ሰላማዊ ሰልፍ ከእንግዲህ ወዲህ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች ዝምታው በቃን ድምጻችን እናሰማለን በማለት የተጀመረ ይመስላል:: ስለዚህ ሀገራችን ኢትዮጵያ ውስጥ ጨምሮ በተለያዩ ዓለማት የሚኖሩ የተዋሕዶ ልጆች በጥታውያን ገዳማቶቻችን እየደረሰ ያለውን ጥፋት ለማስቆም የአቤቶታ ሰላማዊ ሰልፍ እንቅስቃሴ ለማካሄድ የዛሬው አቤቶታ መልካም ጅምር ነው:: በሰላማዊ ሰልፉ የተነሱ ጥያቄዎች እንደሚከተለው ቀርቧል:: 
  • · ክርስቲያኖች ዋልድባን ነጻ ያወጣሉ፣ 
  • · በዋልድባ ጉዳይ ክርስቲያኖች ሁሉ በአንድነት እንቆማለን፣ 
  • · ጳጳሳት ውሳኔያችሁ ይሰማ፣ 
  • · የአባቶቻችን ርስት ተጠብቆ ለትውልድ ይተላለፍ፣ 
  • · የገዳማት አባቶቻችን መብት ይጠበቅ፣ 
  • · ዋልድባ ነጻ ትውጣ፣ መንግስት የመነኮሳቱ ድምጽ ይስማ፣ 
  • · ዋልድባ የቅዱሳን እንጂ የኢንቨስተር አይደለችም፣ 
  • · አባቶቻችን ያስቀመጡልን ገዳማት ሲፈርሱ ዝም አንልም፣ 
  • · የቤተ ክርስቲያን መሪ አባቶች ዝምታችሁ ይብቃ፣ 
  • · ገዳማትን የሚያፈርስ መንግስት አንፈልግም፣ 
  • · የስልጣኔ ምንጭ የሆነች ቅድስ ቤተ ክርስቲያን መብቷ ይከበር፣ 
  • · ገዳማት የጸሎት ቦታ እንጂ የመዝናኛ ቦታ አይደሉም፣ 
  • · ክርስቲያኖች የገደሉ ለፍርድ ይቅረቡ፣ 
  • · አድባራትንና ገዳማትን ማጥፋት ኢትዮጵያዊነትን ማጥፋት ነው፣ 
  • · የአባቶቻችን ተረፈ አጽማቸው ይከበር፣ አጽማቸው ቆፍሮ ማውጣት ይቁም 
  • · ልማት ገዳማትን በማፍረስ አይመጣም፣ 
  • · ሃይማኖታችን የማንነታችን መገለጫ ናት ስለዚህ መንግስት ይህንን ያክብር፣ 
  • · ሃይማኖት ከሌለ ሀገር አይኖርም፣ 
  • · ገዳማት የሚያፈርስ መንግስት ተቀባይነት የለውም፣ 
  • · አብያተ ክርስቲያናት ያቃጠሉ ለፍርድ ይቅረቡ፣ 
  • · ቅዱስ ሲኖድ የገዳማትን ይዞታ የማስከበረ ግዴታ አለበት፣ 
  • · ገዳማትን ማጥፋት በታሪክ ያስጠይቃል፣ 
  • · ገዳማቱ እንዲከበሩ እንፈልጋለን፣ 
  • · ገዳማትን የሚያፈርሱ አይከበሩም፣ 
  • · ዋልድባን ለማጥፋት የሚሞክሩ ይጠፋሉ፣ 
  • · ገዳማቶቻችን ታሪካችን ናቸው፣ 
  • · የአብነት ተማሪው ናታንን የገደሉ ለፍርድ ይቅረቡ፣ 
  • · የኢትዮጵያ ክርስቲያኖች ለሃይማኖታቸው ዝም አይሉም፣ 
  • · መንግስት ሃይማኖታችን ከማጥፋት ይቆጠብ፣ 
  • · አጥፊዎች ለፍርድ ይቅረቡ፣

የሚሉ ናቸው:: የጥንታውያን ገዳማት ህልውና ማስጠበቅ የቤተ ክርስቲያናችን ህልውና ማስጠበቅ ነውና በተለያዩ ቦታዎች የሚኖሩ የተዋሕዶ ልጆች በአጠቃላይ የፖለቲካ እና የዘር ልዩነታቸውን ትተው የአንድነት ድምጻቸውን ለሚመለከተው ሁሉ እንዲያሰሙ የሰላማዊ ሰልፍ አስተባባሪዎች አደራ ብለዋል:: አሐቲ ተዋሕዶ ይህንን የአደራ ቃል ለምእመኑ ሁሉ እንዲዳረስ የበኩሏን ጥረት ታደርጋለች::

የመላው ዓለም የተዋሕዶ ቤተሰብ

No comments:

Post a Comment