Sunday, March 25, 2012

ይድረስ ለአቡነ ጳውሎስ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ይድረስ ለአባ ጳውሎስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ፣ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም፣ ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዝዳንት፣ የዓለም ሃይማኖቶች ምክር ቤት ለሰላም የክብር ፕሬዝዳንት

 አባታችን ይህቺን ትንሽዬ ጦማር እከትብሎ ዘንድ ያነሳሳኝ “ሰሞኑን” በተከሰቱ ሁለት ዓበይት ጉዳዮች ዙሪያ ጥያቄዎች ስላሉኝ ጥያቄ ለመጠየቅና በጉዳዮቹ ዙሪያ የተሰማኝንና የታዘብኩትን ነገር ልነግሮት በመፈለጌ ነው:: ይህቺን ጦማር ስከትብሎ እርሶ ጋር ላይደርስ ይችላል የሚል ጥርጣሬና ሀሳብ አላደረብኝም:: እናም በአንድም ሆነ በሌላ እንደሚድርስዎት እርግጠኛ ስለሆንኩ የተሰማኝን ነገር ሳላስቀር እንዲህ ከትቤዋለሁ::ጉዳዮቹም ሰሞኑን ከፍተኛ አደጋ ተጋርጦባቸዋል ተብሎ ስለሚነገረው ስለሶስቱ ታላላቅ ገዳማት: ማለትም ስለአሰቦት: ዝቋላ እና ዋልድባ ገዳማት በረከታቸው ይደርብንና ስለብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሽኖዳ ሺኖዳ 3ኛ ዜና እረፍት ናቸው::

  • አቢይ ጉዳይ አንድ

  አባታችን ሰሞኑ ከተለያዩ የመገናኛ ብዙኃንና ከአንዳንድ ባልንጀሮቼ በአሰቦትና በዝቋላ ገዳማት ላይ በዙሪያቸው ባሉት የዳን ቃጠሎ ምክንያት: በዋልድባ ገዳም ደግሞ በአከባቢው በመካሄድ ላይ ባለው ከወልቀይት ስኳር ልማት ፕሮጀክት ጋር ተያይዞ የሕልውና አደጋ እንደተጋረጠባቸው ሰማሁ:: አባታችን ስለአደጋው መጠን ትክክለኛነት የተነገረው ያህል ነው: አይደለም: ተጋነነ ወይም ደግሞ እንደ “ታሪከኛው”: “ተዓምረኛው”: “ጉደኛው”ና “አደገኛው” ኢቲቪ በዋልድባ ምንም ችግር የለም እሳቱም በቁጥጥር ስር እየዋለ ነው: ውሏል ወዘተ…ብዬ በእርግጠኝነት መናገር ባልችልም አንዳች አደጋ ስለመኖሩን ግን አልጠራጠርም:: እናም አባታችን አደጋ ስለመኖሩ አንዳች አመላካች ነገር እንዳለ እርግጠኛ ስለሆንኩ ጥያቄዬ እውነት የተጋረጠ አደጋ አለ ወይስ የለም አይደለም:: ችግሮቹን ማን ፈጠረ? እንዴት ተፈጠረ? ለምንስ ተፈጠረ? ወዘተ እያልኩ ዝርዝር ነገሮችን እንዲነግሩኝም አይደለም:: በርግጥ እነዚህን ነገሮች እንዲነግሩኝ ስለማልፈልግ አይደለም:: ጉዳዮቹን ባንድም ሆነ በሌላ በመጠኑ ስለሰማሁ ነገር ማብዛት እንዳይሆንብኝ ፈልጌ እንጂ:: እናም አባታችን ጥያቄዬ እርሶ የቤተ ክርስቲያኒቱ የበላይ ኃላፊ እንደመሆንዎ: የትኛውም የቤተ ክርስቲያኒቷም ጉዳይ ከማንም በላይ ያገባዎታልና: በአመረርዎ በኩል እንዲህ አይነት የቤተ ክርስቲያኒቱን ሕልውና አደጋ ላይ ሊጥሉ የሚችሉ ችግሮች ከመከሰታቸው በፊት የሚደረግ ጥረት አለ ወይ? ከተከሰቱ በኋላስ ችግሮቹን ለመፍታት የሚደረግ ጥረት ምን ያህል ነው? የሚል ነው::

አባታችን በርግጥ የሚሰጡኝ መልስ አዎ አደጋ እንዳይከሰት ቅድመ ጥንቃቄ እናደርጋለን:  ከተፈጠሩ በኋላም ለመፍታት ያላለሳለሰ ጥረት እናደርጋል: ….ወዘተ ወዘተ እንደሚሉኝ እገምታለሁ:: ያም ሆነ ይህ እርሶ የሚሰጡትኝን መልስ እየተጠባበኩ እኔና አብዛኛው ምዕመን እንደሚናምነው እና በተግባር እያየን ያለው ሁኔታ ግን እጂግ በጣም የሚያሳዝን: የሚያሳዝን ብቻ ሳይሆን ቤተ ክርስቲያን መሪ አላት ወይ የሚያስብል ሆኖ አግኝተነዋል:: አዎ ገዳማት ደግመው ደጋግመው በእሳት ሲጋዩ እያየን ነው: ለዘመናት በጥንቃቄ ተጠብቀው የኖሩት ንዋየት ቅዱሳን ወደአመድነት ሲቀየሩ እየሰማን እያየን ነው: ሀገራዊ እሴትነታቸውና ማህበራዊ ፋይዳቸው እጂግ የላቁ የቤተክርስቲያኒቷ ሀብቶች እንደዋዛ ሲወድሙ እያየን እየሰማን ነው:: የመነኮሳት የድረሱልን ጥሪ ድምጽ በቤተ ክህነት ጆሮ ዳባ ልበስ ሲባል እያየን እየሰማን ነው:…ወዘተ:: ሌላው ቢቀር አደጋ  ተፈጥሮ እንኳ እየታየ ምዕመናን ተረባርበው አደጋውን እንዲከላከሉ በቤተክህነት ጥሪ ሲቀርብ አይታይም:: ባጠቃላይ አመረርዎ ቤተ ክርስቲያኒቷን ችላ ያለ ይመስላል:: የቤተ ክርስቲያኒቷም ሕልውና የሚያሳስበው አይመስልም:: የምዕመናኑንም ድምጽ ለመስማት ፍላጎት ያለው አይመስልም:: አሁን አሁንስ ምዕመኑም ቢሆን በቤተ ክህነት ተስፋ የቆረጠ ይመስላል:: ብቻ…. “ይግባኝ ለክርስቶስ” አሉ የዋልድባው መነኩሴ የሚያደርጉት ነገር ሲያጡ:: እኔ በበኩሌ…

እንዲያው አባታችን የጀርመን ድምጽ ራዲዮ በቦታው የነበሩትን ምዕመናን ዋቢ አድርጎ ካቀረበው ዘገባ ቀንጨብ አድርጌ ቃል በቃል ልንገሮት ይስሙኝማ:: ”… የገዳሙ ባለቤትና ጠባቂ ጠቅላይ ቤተክህነት መሪዎች ችግሩን በቅርብ ተረድቶ ከኢትዮጵያ አየር ኃይልም ይሁን ከሌላ አካል ቃጠሎውን ለመከላከል እርዳታ ለማሰባሰብ ምንም ዓይነት ተነሳሽነት ያለማሳየታቸው ደግሞ በሕዝበ ክርስቲያኑ ዘንድ መነጋገሪያ ሆኗል:: ብፁዓን አባቶች ችግሩ አይመለከተንም ዓይነት አቋም መያዛቸው ብዙዎቹን አሳዝኗል:: በቅርብ ጊዜ ብቻ በጎንደር ጥንታዊ አቢያተ ክርስቲያናት: በደብረ ብርሃን ስላሴ ቅኔ ቤት የሀገሪቱ ጥንታዊያን ንዋየት ቅዱሳትና መጽሐፍት የሚገኙበት የመንበረ መንግስት ቤተ መድኃኔዓለም ጉባኤ አዳራሽ: የአሰቦት ገዳም ድን በ እሳት ቃጠሎ ሲወድሙ የቤተ ክርስቲያኒቷ መሪዎች ድምፅ አላሰሙም:: ከዚያ ይልቅ ጥያቄው ሲቀርብላቸው የለበጣ በሚመስል አነጋገር ‘መቼ ተቃጠለ? እንዴት አልሰማንም?’ የሚል ምላሽ ሲሰጡ ይሰማል:: በዝቋላ ለዘመናት የቆየውን ለአብነት የቀሩት አፀደ ገዳማት ሲነድም መንስኤው እንዲጣራ ደኑም የቤተ ክርስቲያኒቱ ብቻ ሳይሆን የሀገሪቱ ሀብት በመሆኑ ሕዝበ ክርስቲያኑ ተረባርቦ እንዲያጠፉ ጥሪ ሲያቀርቡ አለመሰማቱ በእጂጉ ማሳዘኑን ያሰባሰብነው መረጃ ያመለክታል::.. “ይላል::የዶቼዌሌ ራዲዮ እና አባታችን ሕዝቡ እንዲህ ነው እንግዴ አመራርዎን የሚገልጸው:: ሕዝቡ እንዲህ ነው እንግዴ በአመራርዎ ያዘነው:: ሕዝቡ እንዲህ ነው እንግዴ በአመራርዎ ግራ የተጋባው::……ወዘተ::  ግን ይህ ሁሉ ቸልታ  ለምን???????? እርሶ በዚህ ጉዳይ የሚሉትን እስክሰማ ይህን በዚሁ ላብቃና ወደሁለተኛ ጥያቄዬ ልግባ:: ከዚያ በፊት ግን አንድ ነገር ልበል:: አባታችን አሁን ለብዙ ነገር ጊዜው እጂግ የዘገየ ቢሆንም “ከመሞት መሰንበት” ይሻላልና ለምልክት የቀሩት የቤተ ክርስቲያኒቷ መተኪያ የሌላቸው ሀብቶች ወደነበር እንዳይቀየሩ ቤተክህነቱ ተገቢውን ጥበቃና ክትትል እንዲያደግላቸው በትህትና እንጠይቆታለሁ:: በቤተ ክርስቲያኒቷ መንፈሳዊ ዋጋቸው ከቁሳዊ ዋጋቸው እጂግ ይልቃሉ ተብለው የሚታሰቡ የቤተክስቲያኒቱ እሴቶች (እንደ ዋልድባ ገዳም ያሉ…) ተጠብቀው እንዲኖሩ ቤተክህነት ከሚመለከተው አካል ጋር በቅንጅት ለመስራት ያላለሳለሰ ጥረት እንዲያደርግ እንጠይቆታለሁ::

  • አቢይ ጉዳይ ሁለት

አባታችን በለፈው ዕለት የግብጽ ሙስሊም ማህበረሰብን ጭምር ያስደነገጠና የሳዘነ የብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ሽኖዳ 3ኛ ዜና እረፍትና የቀብር ስነስርዓትን ዜና በቢቢሲ እያየሁ እርሶን በስነ ስርዓቱ ላይ ለመካፈል ሄደው ከሌሎች አባቶች ጋር ቆመው አየሁዎት:: በርግጥ መሄድዎ የሚጠበቅ ነው:: ሁኔታውን እንዴት ተመለከቱት ግን? አቤት የሕዝቡ መሪር ሀዘን እንዴት ይገርማል? እንዴት ቢወዷቸው: ምን ቢያደርጉላቸው ምንስ ቢሰጧቸው ነው እንዲህ ያለ መሪር ሀዘን ግን? የአስከሬኑን ሳጥን ለመንካትና ለመዳሰስ የነበረው ግፊያ ሳጥኑን የተሸከሙትን ጳጳሳትና ካህናት አላንቀሳቅስ ነበር እኮ ያሉት:: የሕዝበ ክርስቲያኑ ብዛት ደግሞ አንድም ሰው እቤት የቀረ አይመስልም:: አቤት ፍቅራቸው ትንሹ ትልቁ ፓፓ ፓፓ….እያሉ እንደህፃን እዬዬ ሲሉ እጂግ በጣም ይገርማል:: ምስላቸውን አቅፈው እሪታቸውን ሲያቀልጡ አቤት ክብራቸው ያሰኛል:: ብቻ ከሊቅ እስከ ደቂቅ በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠር ሕዝብ እጂግ በጣም ከባድ ሀዘን ነበር ያዘነው:: ለነገሩ እሳቸውን ትንሽ ትንሽ የሚያውቅ የሀገራችን ሰውስ ከልቡ ያላዘነ ማን አለ?
አራት ሰው ሞተ ደረሰ እና ጥሪ
ደራሲ፣ ሰባኪ፣ ጳጳስ እና መሪ……..አለ ዲ/ን ዳኒኤል ክብረት::

አባታችን እርሶ ሁኔታውን እንዴት ነበር ያዩት? በትዕይንቱስ ምን ተሰማዎት?       

 እኔን ምን እንደተሰማኝ ያውቃሉ? ቁጭት: ቅናት እና ሀዘን:: መቼም ለምን ብለው እንደማይጠይቁኝ እገምታለሁ:: ከጠየቁኝም ያ ያየሁት ትዕይንት የፈጠረብኝ ቅናት: ቁጭትና ሀዘን እውነቱን እንዳልናገር ደንቃራ ሆኖብኝ የኖረውን የይሉኝታና የፍርሃት ድባብን ገፎልኛልና እነግርዎታለሁ:: ደግሞ በቁጭት: በቅናት እና በሀዘን እየተብሰከሰኩ ከመኖር እውነቱን ተናግሮ ዕድል መሞከር ይሻላል ብዬም ስለማምን ዛሬ የሚሰማኝን ነገር ነግሬዎት ዕድሌን ለመሞከር ወደድኩ:: እርሶም ይሰሙኛል ይቀበሉኛል ብዬ አስባለሁ::

አባታችን በብጹዕ አቡነ ሽኖዳ 3ኛ ያየሁት ትዕይንት ወደራሳችን ተመልሼ እራሳችንን እንዳይ አደረገኝ:: እናም ያው ከሞት የሚያመልጥ የለምና እርሶን በርሳቸው ቦታ አድርጌ በዓይነ ሕሊናዬ ለማየት ሞከርኩ:: እውነቴን ነው የምሎት ደስ አላለኝም ብቻ ሳይሆን ዘገነነኝ:: በግብጽ ያሉ ሕዝበ ክርስቲያን በሙሉ ለማለት በሚቻል ሁኔታ እጂግ በጣም እንዳዘኑ ይነገራል:: ያየነውም ያንን የሚያመለክት ነው:: እና ይህ ክስተት እኛ ሀገርስ ቢሆን ስንቱ ይሆን እንዲህ የሚያዝነው ብዬ አሰብኩ:: እናማ አሁን ባለው ግንኙነት ማለትም በሕዝበ ክርስቲያንና በእርሶ መካከል ባለው ግንኙነት በእርሶ ዙሪያ ለስጋዊ ጥቅም ከተሰበሰቡት ከጥቂት ጥቅመኞች ውጭ አንድም ሰው ያዝናል የምል ግምት የለኝም:: እነዚህ ጥቅመኞችም ቢሆኑ አብዛኞቹ ጥቅማችን ቀረ ብለው ካልሆነ በስተቀር ከልባቸው የሚያዝኑ አይመስለኝም:: መቼም እኔ የማስበውና የምለው ያክል ባይሆንም እርሶም ይህንን የሚያውቁ ይመስለኛል:: በተለያዩ አጋጣሚዎችም ይህንን አይተውታል ብዬ አስባለሁ:: በዚህ በእኛ(ሕዝበ ክርስቲያን)ና በእርሶ መካከል ባለው የሻከረ ግንኙነት ደስተኛ የሆነ ሰው ያለ አይመስለኝ:: ምክንያቱም ሁላችንም ጥሩ አባትና ጥሩ ግንኙነት እንዲኖረን ስለምንፈልግ:: እና አባታችንን ይህንን ሳስብ ነው እንግዲህ ቁጭቱ: ቅናቱ እና ሀዘኑ የሚመጣብኝ:: ለምን እላለሁ? እኛ ከግብጾች በምን አናንሳለን እያልኩ እራሴን እጠይቃለሁ:: መልሱ ግን ግልጽ ነው:: መልሱ እርሶ ከሕዝቡ ጋር ያሎት ግንኙነት በጣም ሻካራ ስለሆነ: ሕዝብን ስለማይሰሙ: ከምዕመናን ይልቅ በዙሪያዎ ለሚያንዣብቡ ጥቅመኞች ቅድሚያ ስለሚሰጡ: በቤተ ክስርቲያኒቱ ጉዳዮች በጣም ቸልተኛ ስለሆኑ:: ከቤተ ክርስቲያን ክብር ይልቅ የራስዎን ክብር ስለሚያስቀድሙ: አስተዳደርዎ በብልሹ አመራር ስለተዋጠ: በአጭሩ በአመራርዎ አምባገነን ስለሆኑ:: ይህ ባይሆን ግን እኛም እንደግብጾች በታደልን ነበር:: እኛ በእርሶ እንኮራ ነበር እርሶም እኛ ለማስተማርና ቤተክርስቲያንን ከመጠበቅ አይደክሞትም ነበር::

አባታችን መቼም መልካም አባት መሆን ምን ያህል ፍቅርና ክብር እንዳለው በግብጹ ትዕይንት በደንብ ያዩት ይመስለኛል:: እናም ያንን መንፈስ ወደ እኛይቱ ቤተ ክርስቲያን እንዲመጣ ሳይመኙ ወይም ሳያስቡ የቀረ አይመስለኝም:: እኛም ቢሆን ያንን በጽኑ እንፈልገዋለን:: ትጉህ እረኛ: ትጉህ መካሪ: እንፈልጋለን:: ስለዚህ አባታችን ያለፈው ጥፋትዎ ይብቃዎት:: መልካም ነገር እንዲመጣ ሰላምም በቤተ ክርስቲያን እንዲሰፍን የአባትነትዎን ድረሻ ለመወጣት ቁርጠኛ አቋም ይዘው አመራርዎን ያስተካክሉ:: እግዚአብሔር ለኢትዮጵያ ሕዝብ ከሰጣቸው ጸጋ ቂም ያለመያዝ ዋነኛው ጸጋ ነውና እርሶ ዛሬ ችግርዎትን ቢያስተካክሉ ሕዝቡ ነገ ጠዋት አባታችን አባታችን እያለ እንደሚከብዎች ጉልበትዎን እንደሚስም አልጠራጠርም:: ይመኑኝ አባታችን ይህንን ካደረጉ የግብጾች አራት እጥፍ በሆነ ሕዝብ ልብ ውስጥ ለመቀመጥ አንድ ሐሙስ አያልፍም:: በዙሪያዎ ካሉ ጥቅመኞች ይልቅ ሕዝብን ይመኑ: ይስሙ: ያክብሩ:: እራስዎን በራስዎ ከሚያከብሩት በላይ በሕዝብ መከብር ትልቅ ክብር ነውና ሕዝበ ክርስቲያኑን ያክብሩ ይውደዱ:: ያኔ ፍቅርና ክብር እጥፍ ድርብ ሆኖ ይመጣልና አሁኑኑ ተግባራዊ ለማድረግ ቆርጠው ይነሱ:: እኛም ይቅር ለማለት ዝግጁ ነን::
አምላከ እስራኤል ይርዳን::
ደጀኔ

የመላው ዓለም የተዋሕዶ ቤተሰብ

3 comments:

  1. Ayekochehim wondeme ye dereshahin tewotehal!

    ReplyDelete
  2. JORO ALACHEW BILEH NEW???????

    ReplyDelete
  3. His holines, Aba Paulos

    I strongly advise u to read the note time and Again. two benefits will follow.
    1. you will regain love of people and GOD
    2. the church will benefit out of it

    ReplyDelete