Friday, December 7, 2012

የዕርቀ ሰላም ውይይቱ በመልካም ሁናቴ ቀጥሏል


(ደጀ ሰላም ኅዳር 27/2005 ዓ.ም፤ ዲሴምበር 6/2012/ READ THIS NEWS IN PDF)፦በአሜሪካዋ የቴክሳስ ግዛት ዳላስ ከተማ በመካሔድ ላይ የአባቶች ዕርቀ ሰላም ውይይት በመልካም ሁናቴ በመካሔድ ላይ መሆኑን ምንጮቻችን ገልጸውልናል። ትናንት የተጀመረው ጉባኤ በመጀመሪያ ቀን የጠዋት ውሎው በጸሎተ ኪዳን ጉባኤውን ጀምሯል።  ጸሎተ ኪዳ ብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ መሪነት ከተካሔደ በኋላ “ የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት በመልአከ መንክራት ቀሲስ አንዱዓለምይርዳው ተሰምቷል።


ጉባኤው ቀጥሎ  ከዚህ ጉባኤ ምን እንደሚጠበቅ ባለ አምስት ነጥብ ማብራሪያ  በአስታራቂ ኮሚቴው አባል በቆሞስ አባ ጽጌ ደገፋው የቀረበ ሲሆን  የሰላምና  አንድነት ጉባኤው አባላት ትውውቅ አድርገዋል። አስከትሎም ሁለት መልእክቶች በተከታታይ ቀርበዋል።  ብፁዕ አቡነ ገሪማ ባቀረቡትየመግቢያ መልዕክት ስለ ኢትዮጵያ  መጽሐፍ ቅዱስ የተናገረውን በመዘርዘር ኢትዮጵያ ገረ እግዚአብሔር መሆኗን አብራርተው ቤተ ክርስቲያን ለአገር ያበረከተችውን አስተዋጽኦ ዘርዝረው በተለያዩ ጊዜዎች ፈተና  እንደገጠማትና እንደተወጣችው  አብራርተዋል:: ሰላም ማምጣት  አስፈላጊ መሆኑንና ባፋጣኝ እንዲፈጸም እንደሚገባ አስረድተዋል::  ብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅባቀረቡት ተመሳሳይ መልዕክት ታራቂዎችም አስታራቂዎችም እኛ ነን ብለዋል::

 ጉባኤው ውይይቱን ቀጥሎ ከኢትዮጵያው ሲኖዶስና  ከሚገኙት አባቶች በኩል የቀረቡትን ሁለት የመወያያ አጀንዳዎች በማጣጣም  በሰላምና  አንድነት ጉባኤው የቀረቡ ስድስት  የዕርቀ ሰላሙ የውይይት አጀንዳዎች እና  የመወያያ ደንብ ስለማጽደቅ የሚገልፀው ሑፍ በንባብ በመርሐ ግብር መሪው  ተነቦ ጉባኤው አጀንዳውን አጽድቋል::

ከሰዓት በ ሊቀ ካህናት ኃይለ ሥላሴ ዓለማየሁ መድረክ መሪነት በታካሔደው ውይይት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ ከሥልጣናቸው እንዴት ሊወርዱ እንደቻሉ በአገር ውስጥም በውጪውየሚገኙት አበው ልዑካን የታሪክ ምስክርነታቸውን በወቅቱ ሰጥተው ውይይቱ በሰላምና በፍቅር ቀጥሎ የዋለ ሲሆን በአሁኑ ሰዓት የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስ ወደ ኢትዮጵያ  መመለስ አስመልክቶ ሰፊ ውይይት ተደርጎ በይደር ተጠናቅቋል። ውይይቱ ሐሙስም ቀጥሎ የዋለ ሲሆን ዝርዝሩን እንደደረሰልን ለማቅረብ እንሞክራለን።

በተያያዘ ዜና በአገር ሽማግሌዎች ምክር አቡነ መርቆርዮስን መመለስ አስመልክተው ደብዳቤ የጻፉት ፕሬዚዳንት ግርማ ደብዳቤያቸውን ከሳቡ ወዲህ ጉዳዩ ትልቅ የመነጋገሪያ አጀንዳ ሆኖ እንደቀጠለ ነው። የአሜሪካ ድምጽ ሬዲዮ ዛሬ ያነጋገራቸው የፕሬዚዳንቱ ልዩ አማካሪ አቶ አሰፋ ከሲቶ ደብዳቤው በደብዳቤ እንደሚሻር ገልጸው አዲሱ ደብዳቤ “አቡነ መርቆርዮስ ከፈለጉ ተመልሰው ለፕትርክና መወዳደር እንደሚችሉ” የሚያትት ሐሳብ እንዳለው ተናግረዋል።

በእርግጠኝነት ይህ ሐሳብ የፕሬዚዳንቱ እንዳልሆነ መገመት ይቻላል። እንኳን በኦርቶዶክስ እምነት ውስጥ ለሚኖር ሰው የሰለጠነ ዓለማዊ ፖለቲካ የሚመራ ሰው እንኳን “ተርሙ ያለቀ መሪ” ድጋሚ ይወዳደር አይባልም። ኢትዮጵያን በፕሬዚዳንትነት የመራ ሰው ጊዜ ገደቡን ሲጨርስ ሥልጣኑን ለሌላ ሰው አስረክቦ በጡረታ ይገለላል እንጂ ድጋሚ ልወዳደር አይልም። መንፈስ ቅዱስ አንድ ጊዜ ፓትርያርክ ያደረጋቸውን ሰው ለሌላ ፓትርያርክነት ተወዳደሩ ማለት ምን ማለት ነው? ፕሬዚዳንት ግርማ ደግሞ ይህንን ስለሚያውቁ “እንዲህ ይላሉ” ብለን አንጠብቅም። ነገር አሳምር ያለ የመንግሥት ሰው ያመጣት ሐሳብ መሆን አለባት። አሁንም ቢሆን፣ በዚያም ይሁን በዚህ፣ እጃችሁን ከቤተ ክርስቲያን ላይ አንሡልን፤ ቤተ ክርስቲያን የራሷን ጉዳይ ለማስተናበር አታንስም።

ለማንኛውም የአሜሪካ ድምጽ ሬዲዮን ዘገባና ቃለ ምልልስ አዳምጡ።
                                                                        

“ጸልዩ በእንተ ሰላመ ቤተ ክርስቲያን - ስለ ቤተ ክርስቲያን ሰላም ጸልዩ”።

ቸር ወሬ ያሰማን፤
አሜን፡፡

የተዋሕዶ ቤተሰቦች በመላው ዓለም

No comments:

Post a Comment