Monday, December 31, 2012

የኢትዮጵያ መንግሥት ዓላማውን ግልጽ አድርጓል፤ እኛም አውቀናል


  • የመንግሥት ደጋፊ የጡመራ መድረኮች “አስታራቂ ኮሚቴው” ላይ ዘምተዋል፤
  • ከጳጳሰቱ መካከል የዕርቁ እንቅፋት የሆኑት አባቶች በግልጽ ታውቀዋል፤ ስማቸውን ከማውጣታችን በፊት አሁንም ሐሳባቸውን ይቀይሩ እንደሆነ እንጠብቃቸዋለን፤
  • ጉዳዩን ያቀነባበሩት የአዲስ አበባው ልዑክ አባል የሆኑት ን/ዕድ ኤልያስ አብርሃ ናቸው ተብሏል፤
  • የአዲስ አበባው ልዑክ አባቶች ዲሲ ኢትዮጵያ ኤምባሲ ከተጠሩ በኋላ ተገደው እንዲፈርሙ ተደርገዋል፤
(ደጀ ሰላም ታኅሣሥ 20/2005 ዓ.ም፤ ዲሴምበር 29/2012/ PDF)፦ በቤተ ክርስቲያን ጉዳይ ጣልቃ አልገባኹም በሚል ሰሞኑን መግለጫ የሰጠው የኢትዮጵያ መንግሥት ለዕርቁ ጉዳይ ከቅ/ሲኖዶስ ጋር ለመነጋገር ወደ አዲስ አበባ የሄዱትን የሰላምና አንድነት ጉባኤውን አባል ሊቀ ካህናት ኀ/ሥላሴ ዓለማየሁን አስሮ ወደ አሜሪካ ከላካቸው ወዲህ ለዕርቁ ያለው የተስፋ ደጅ መዘጋቱ እሙን ሆኗል። መንግሥት የዕርቁ ድርድር ለይስሙላ እንጂ “ከምር” እንዲሆን አልፈለገም ነበር።
ነገሩ ከምር ሲሆን ግን “የጭቃ ጅራፉን” መምዘዝ ይዟል። ለዲፕሎማሲ ይጠቅመኛል ብሎ የፈቀደው ዕርቅ መሰካት ሲጀምር ከዲፕሎማሲው ከማገኘው ትርፍ በሩን መዝጋት ይሻለኛል ያለ መስሏል። የራሱን ፓርቲ አባል በፓትርያርክነት ለማስቀመጥ በጠራራ ፀሐይ ወረራውን ቀጥሏል።  

በተያያዘ ዜና አስታራቂ ጉባኤው አውግዘው መግለጫ እንዲሰጡ የተገደዱት የአዲስ አበባው ልዑክ አባላት ሐሳባቸውን በግድ እንዲቀይሩ የተገደዱት ወደ ኢትዮጵያ ኤምባሲ ከተጠሩ በኋላ መሆኑ ሲታወቅ ደብዳቤውን ያዘጋጁት ንቡረ ዕድ ኤልያስ አብርሃ ከኤምባሲው ሰዎች ጋር በመሆን እንደሆነ ምንጮቻችን ገልጸዋል። ሦስቱ ብፁዓን አባቶች ደብዳቤውን ያለውድ በግድ እንዲፈርሙ ሲገደዱ ሐሳባቸውን ላለመቀየር ያንገራገሩት ብፁዕ አቡነ አትናቴዎስ በብዙ ማግባባት ፊርማቸውን እንዲያኖሩ ተደርገዋል ተብሏል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ መግለጫው ከወጣበት ጊዜ ጀምሮ ኢላማ የተደረገው አስታራቂ ጉባኤ በመንግሥት ደጋፊ የግል ጦማሪዎች ሳይቀር በመወገዝ ላይ ይገኛል። “መጀመሪያውኑም ገለልተኛ አልነበረም” የተባለው አስታራቂው ቡድን ከመ-አርዮስ የታየበት ምክንያት ዕርቁን ከግብ ለማድረስ በመቃረቡ ነው።

ቸር ወሬ ያሰማን፣ አሜን።

የተዋሕዶ ቤተሰቦች በመላው ዓለም

No comments:

Post a Comment