Tuesday, February 7, 2012

ለብጹዕ አቡነ ፋኑኤል

  • ቤተ ክርስቲያን የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ አይደለችም፤ ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስ ናት” ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል
 READ IN PDF
ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ከአሜሪካ ድምጽ ሬድዮ ጋዜጠኛ ከአቶ አዲሱ አበበ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ በሀገረ አሜሪካን ስለምትገኘው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሁኔታ ግንዛቤ ለሌላቸው አድማጮች እውነት የሚመስሉ፤ ነገር ግን በመሬት ላይ ካለው እውነት ጋር ፍጹም የማይገናኙ  ትንታኔዎችን ሰጥተዋል:: “የደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ጵጵስና በተቀበሉበት ወቅት ለቅዱስ ሲኖዶስ እንዳስረከቡ መረጃዎች አሉን የሚሉ ወገኖች አሉ፤ ነገር ግን አሁንም ድረስ  ቤተ ክርስቲያኑ በእርሶ እጅ እንዳለ ይወራል” በማለት አቶ አዲሱ አበበ ላቀረበላቸው ጥያቄ ሲመልሱ “ቤተ ክርስቲያን የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ አይደለችም፤ ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስ ናት” ብለው ነበር:: ይህ አነጋገር በሰሜን አሪሜካ ስላለችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናን በቂ መረጃ ለሌላቸው ሰዎች እውነት ቢመስልም ሐቁ ግን ከዚህ የራቀ ነው::
 ለብፁዕ አባታችን አሁን ደግሞ እኛ አንድ ጥያቄ እናቅርብ እስኪ፤ እውነት በሰሜን አሜሪካን ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስ ናትን? 

የቤተ ክርስቲያናችን ቀኖና እንደሚያስረዳው ቤተ ክርስቲያን ከተመሠረተች ተመሠረተች እንጂ አትዘጋም:: በቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ የቤተ ክርስቲያን መሠረቷ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑንም ከእውነተኞቹ አባቶቻችን ተምረናል:: ነገር ግን በቤተ ክርስቲያን ስም እዚህ ሀገር ውስጥ የውንብድና ሥራዎች ሲሰሩ እናያለን እንሰማለን:: ብፁዕትዎ እንዳሉት ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስ ብትሆንማ የተለያዩ ግለሰቦዎች እንደፈለጉ ከፍተው አይዘጓትም ነበር:: እውነታው ግን ይህ አይደለም:: በአሜሪካ ቤተ ክርስቲያን ልክ እንደ ፕሮቴስታንቶቹ  አዳራሾች የግለሰቦች ንብረት ናት:: ለምሳሌ ያህል የዛሬ አራት ወር በሜሪላንድ ሲልቨር እስፕሪንግ አካባቢ የተከሰተው ድርጊት በቂ ማስረጃ ነው:: የተከሰተውን ድርጊት በዝርዝር እንየው፣ እንዲህ ነው::

አሁን ለሜሪላንድ ስቴት ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል እና የሰንበት ት/ቤቶች ኃላፊ አድርገው ብፁዕነትዎ የሾሟቸው መልአከ ሰላም ቀሲስ ሰብስቤ ጸጋዬ ኪዳነ ምሕረት ወአማኑኤል የሚል አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ነበራቸው:: ይህ አጥቢያ “የተከፈተው” ወይም ደግሞ በቤተ ክርስቲያናችን ቋንቋ የተመሠረተው በቀሲስ ሰብስቤ ነበር:: “ተከፍቶ” ለአንድ ዓመት ያህል አገልግሎት ከሰጠ በኋላ ከቀሲስ ሰብስቤ ጋር አብረዋቸው የነበሩ ሰዎች በጥቅም ተጣልተው ሌላ ኪዳነ ምሕረት ወአማኑኤል በማለት እዛው አጠገብ ሌላ አጥቢያ ከፈቱ:: የቀሲስ ሰብስቤ ኪዳነ ምሕረት ወአማኑኤል ቤተ ክርስቲያን ለሦስት ዓመታት ያህል ከቆየ በኋላ በዘንድሮ ጥቅምት ወር ላይ ተዘግቶ ቀሲስ ሰብስቤ ወደ ሌላ ስቴት ኮብልለው ነበር:: የመዘጋቱም ምክንያት ቀሲስ ሰብስቤ  ከቤተ ክርስቲያኑ የባንክ አካውንት ያለ ሒሳብ ሹም ፈቃድ ለሁለት ዓመታት ያህል ገንዘብ እያወጡ ለግላቸው ሲያውሉ በመቆየታቸው ነው:: በመጨረሻ የነቁት የአጥቢያው ምእመናን አስተዳዳሪው ቀሲስ ሰብስቤ ላይ አጥቢያውን በተመለከተ አንዳንድ ጥያቄ አነሱ:: ቀሲስ ሰብስቤ መልሳቸው “ቤተ ክርስቲያኑ የእኔ ነው፣ እናንተ ምን አገባችሁ” የሚል ነበር:: ምእመናኑም አስተዳዳሪውን ለመክሰስ የሕግ አማካሪ ጋር ሲሄዱ የቤተ ክርስቲያኑ ፈቃድ የተመዘገበው በቀሲስ ሰብስቤ ስም ብቻ መሆኑን ተረዱ:: እንዲሁም የአጥቢያው የባንክ አካውንት በቀሲስ ሰብስቤ ስም ነበር፥ ምእመናኑ ቢከሱም የትም ሊደርሱ እንደማይችሉ ተረዱ:: በመጨረሻም ቀሲስ ሰብስቤ ቤተ ክርስቲያኑ ዘግተው ጠፉ:: አንባቢያን “ታቦቱንስ የት አደረጉት” ትሉ ይሆናል፤ ይህ ደግሞ የእኛም ጥያቄ ስለሆነ መልስ ልንሰጣችሁ አንችልም::

ከዚህ በፊትም ቀሲስ ሰብስቤ በተመሳሳይ ሁኔታ በዳላስ ቴክሳስ የከፈቱትን ቤተ ክርስቲያን ዘግተው ነበር ወደ ሜሪላንድ ስቴት የመጡት:: የሜሪላንዱም ሆነ የቴክሳሱ አጥቢያዎች “የተባረኩት” በራሳቸው በቀሲስ ሰብስቤ ነበር:: አስተዳዳሪውም ራሳቸው ነበሩ:: ሁለቱንም አጥቢያዎች ከፍተው የዘጓቸው ቀሲስ ሰብስቤ ናቸው:: እና ታድያ በብፁዕ አቡነ ፋኑኤል አባባል እነዚህ የቀሲስ ሰብስቤ አጥቢያዎች የክርስቶስ ነበሩ ማለት ነውን? እውነተኛ አባት የተሰበሰቡ በጎቹን በትኖ ይጠፋልን? እኒህ ግለሰብ አሁን በብፁዕ አቡነ ፋኑኤል የተሰጣቸው ሹመትስ ይገባቸዋልን? መልሱን ለአንባቢ እንተወው::

በሀገረ አሜሪካ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት እንዴት እና በማን ይመሠረታሉ? የአጥቢያዎች አመሠራረት የተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ቀኖና የጠበቀ ነውን? የአጥቢያዎቹ የይዞታ ባለቤነት የማን ነው? እንግዲህ የእነዚህን ጥያቄዎች መልስ ሊሰጡ የሚችሉ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናቱን የመሠረቱት ሰዎች ብቻ ናቸው:: በዚህ ሀገር እንደየስቴቶች ሕግ አጥቢያዎች ሲከፈቱ ሁለት ዓይነት ሕጎች ይኖሯቸዋል:: የመጀመርያው ሕግ መተዳደርያ ደንብ የሚባለው ሁሉም ምእመን የሚያውቀው ሲሆን አንዳንድ አጥቢያዎችም በድረ ገጾቻቸው ላይ ያስቀምጡታል:: ሁለተኛው ሕግ ደግሞ ከመሥራች ግለሰቦች ውጪ ማንም የማያውቀው፤ ይህም ሕግ “አርቲክል ኦፍ ኢንኮርፖሬሽን (article of incorporation) ላይ የሚቀመጥ ነው:: በአርቲክል ኦፍ ኢንኮርፖሬሽን የሚቀመጡ ሰዎች በዚህ ሀገር ሕግ ኢንኮርፖሬተር ይባላሉ:: እንደየስቴቱ የሰዎቹ ቁጥር ብዛት ይለያያል:: አርቲክል ኦፍ ኢንኮርፖሬሽን ላይ የሚቀመጠው  “ኢንኮርፖሬተሮቹ” (መሥራቾቹ) እንደሚፈልጉት አድርገው የሚያስቀምጡት ገዢ ሕግ ነው።: በአጥቢያው አባላት መካከል አለመግባባት ሲመጣ (ልክ እንደ ቀሲስ ሰብስቤ) ዘግተው እስከመጥፋት ሊደርሱ ይችላሉ። ምክንያቱም አርቲክል ኦፍ ኢንኮርፖሬሽን ላይ የሚቀመጠው ሕግ ባለቤት ስለሚያደርጋቸው:: ታድያ ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ይህንን ሁሉ እያወቁ (እርሳቸውም የግላቸው የሆነው የቅ/ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን እንዳላቸው  ያስታውሷል) አሜሪካን አገር ያለችው ቤተ ክርስቲያን እንዴት የክርስቶስ ናት አሉ?? ግለ ሰቦች እንደ ፈለጉ ከፍተው ሲበቃቸው የሚዘጓት ቤተ ክርስቲያን እንዴት የክርስቶስ ልትሆን ቻለች?

የዲሲ ደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን በባለቤትነት ወይም “article of incorporation” ከተመዘገቡት ሦሥት ግለሰቦች መካከል አንዱ ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ናቸው:: የዚህ አጥቢያ እስከ አሁን (Feb 15, 2011 ዓ/ም) የተሠራው የቤተ ክርስቲያኑ ታክስ መታወቂያ እንደሚያመለክተው ባለቤትነቱ በአባ መላኩ ጌታነህ ስም ነው፤ ነገር ግን ለይስሙላ አስተዳዳሪው አባ እስጢፋኖስ ናቸው:: ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል  አሁንም ለየስቴቱ ሹመት የሰጧቸው ሰዎች አንዳንዶቹ እንደ ብፁዕነታቸው በስማቸው የራሳቸው አጥቢያ ያላቸው፣ አንዳንዶቾ ደግሞ ቤተ ክርስቲያን ከፍተው የዘጉ፤ አንዳንዶቹ ደግሞ አጥቢያ እንኳን የሌላቸው ተዘዋዋሪ ካህናት ናቸው:: እንግዲህ ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል በሰሜን አሜካሪካ ከቀጣፊዎች ጋር በመተባበረ ቤተ ክርስቲያናችን የበለጠ ውስብስብ የሆነ ችግር ውስጥ ሊያስገቧት እንዳቀዱ ይህ ሹመት ምስክር አይሆንምን?

በዋሽንግተን ዲሲ እና አካባቢ ያሉ አጥቢያዎች ዝርዝር ለማየት ይህንን ይጫኑ::

ይቆየን::
ከአሐቲ ተዋሕዶ የተወሰደ
የመላው ዓለም የተዋሕዶ ቤተሰብ

1 comment: