Wednesday, January 4, 2012

የዋሺንግተን ዲሲና አካባቢው ሀ/ስብከት ሥራ አስፈጻሚ የብፁዕ አቡነ ፋኑኤልን እንቅስቃሴ እየተቃወመ ነው


(ደጀ ሰላም፣ ታኅሣሥ 24/2004 ዓ.ም፤ January 3/2012/ READ THIS ARTICLE IN PDF)፦ ለዋሺንግተን ዲሲ እና አካባቢው ተመድበው ቢላኩም ሀ/ስብከቱን ማስተዳደር ያልጀመሩት አቡነ ፋኑኤልን በተመለከተ የተቀሰቀሰው ተቃውሞ ቀጥሎ ሀ/ስብከቱን እንዲያስተዳድር የተመረጠው ሥራ አስፈጻሚ “ሁሉ በአገባብና በሥርዓት ይሁን” 1ኛ ቆሮ 14፡40 በሚል ርእስ ኅዳር 29 ቀን 2004 ዓ. ም ባወጣው መግለጫ በሀ/ስብከቱ ያለው ዋነኛ ችግር “የውስጥ የቤተ ክርስቲያን ፈተናና እና ችግር  የሆነው የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት በማክበርና ባለማክበር፤ እውነታን በመናገርና ባለመናገር፤ የቤተ ክርስቲያንን ጥቅም በማስጠበቅና የግል ጥቅምን ከቤተ ክርስቲያን በማስቀደም፤ መዋቅርን በመጠበቅና ባለመጠበቅ፤ ጽኑ መንፈሳዊ አቋም በመያዝና ባለመያዝ መካከል” መሆኑን ጠቅሷል።


መግለጫው አክሎም “በዋሽንግተን ዲሲና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሥር የምንገኝ አብያተ ክርስቲያናት እያሳሰበን የመጣው የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ጠብቆና አስጠብቆ የመጓዝ ሁኔታ በመሆኑ በሀገረ ስብከታችን ያለውን አጠቃላይ ሁኔታ ለቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ከዚህ ቀደም ያሳሰብን ቢሆንም፤ እውነት ሊደበቅ ስለማይገባ ያለውን እና ተጨባጭ የሆነውን ጉዳይ ለቅዱስ ሲኖዶስና ለመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት በድጋሚ ማሳሰብ እንዳለብን በመረዳት ይህንን የአቋም መግለጫ አዘጋጅተናል” ብሏል።  

ጥቅምት 21 ቀን 2004 ዓ. ም ለቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት በ አቤቱታ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ጉዳዩን ተመልክቶ ውሳኔ እንዲሰጥበት፤ በሰሜን አሜሪካ የሚገኙ ካህናትና ምእመናን ያላቸው ስሜት ምን እንደሆነ በማስረዳት  የብፁዕ አቡነ ፋኑኤልን ምደባ መረጃን መሰረት ባደረገ መልኩ በመመልከት ወደ ሰሜን አሜሪካ ተመድበው የሚመጡ ከሆነ የቤተ ክርስቲያን መዋቅር በመጠበቅ እና በማስጠበቅ የሚያስከትለውን ጉዳት፤ በመልካም ጀምር እየታየ ያለውን በሀገረ ስብከቱ ሥር  የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናትን አንድነት አደጋ ውስጥ እንደሚያስገባው መመገለፁን የጠቀሰው መግለጫው የሀ/ስብከቱ አቤቱታ ከብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ጋር ባለ የግል ችግር ሳይሆን የቤተ ክርስቲያን ሥርዓትና መዋቅር እንዲጠበቅ፤ የተማረረው ሕዝበ ክርስቲያን የበለጠ ተማሮ ከቤተ ክርስቲያን እንዳይርቅ እና ተስፋ ወደ መቁረጥ እንዳይሄድ ማሳሰብ መሆኑን ያትታል
ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ከዚህ በፊት ባደረጓቸው ተግባራት የቤተ ክርስቲያንን መዋቅር አስከብሮ ለመሄድ  የነበራቸው አስተዋጽዖ አነስተኛ መሆኑንና ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን በመተላለፍ በፈጸሙት ተግባር የብዙዎችን ሊና የጎዱ መሆናቸውን  የሚጠቅሰው መግለጫው
1.      ከዚህ በፊት ያገለገሉበትና  አሁንም እየመጡ የሚያርፉበት የደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን መዋቅር  ማስገባት ሳይችሉ መቅረታቸውን
2.     ከዚህ በፊት በአሜሪካን እንዲያገለግሉ ቢመደቡም  በነበራቸው  ችግር ምክንያት  ከካህናትና ከምእመናን  ባላቸው አለመግባባት የተነሳ በቅዱስ ውሳኔ መነሣታቸውን
3.     የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት  በመተላለፍ  በተለያዩ አብያተ ክርስቲያናት በመገኘት  ሀገረ ስብከቱን  መዋቅር በመናቅ  ክህነት  መስጠታቸውንና  ቤተ ክርስቲያንም መባረካቸውን
4.     ከዚህ በፊት በሰሜን አሜሪካ በመዋቅር ሥር ባለ ቤተ ክርስቲያን እንዳላገለገሉ፣ ለእንግድነት ወደ አሜሪካም በመጡበት ጊዜ ሁሉ በሀገረ ስብከቱም ሆነ በሀገረ ስብከቱ ሥር ባሉ አብያተ ክርስቲያናት ተገኝተው እንደማያውቁ፣
5.      ከዚህ በፊት በሰሜን አሜሪካ በፈጸሙት ተግባር የብዙ ምእመናንና ካህናትን ሊና በመጉዳታቸው የአባትነት ክብራቸውን ማጣታቸውን በሰፊው ዘርዝሯል።  
አክሎም “የቤተ ክርስቲያንን  ችግር ለመፍታት የምእመናንን እና የካህናትን አቤቱታ በመስማት መፍትሔ መስጠት የሚችለው ቅዱስ ሲኖዶስ  የሚያስተላልፈው ውሳኔ  የምእመናንን ሐዘን የሚያስታግስ፤  አገልጋዮችን የሚያበታታ እና የቤተ ክርስቲያንን መዋቅር ለመስጠበቅ ከፍተኛ መስዋዕትነት የከፈሉ ካህናትና ምእመናን  የሚጽናና ይሆናል ብለን በማመን፤ በተጨማሪም በካህናትና በምእመናን ዘንድ  የአባትናት ክብራቸው ከቀነሰና ከጠፋ “ለመንጋው  ምሳሌ ሁኑ እንጂ ማኅበሮቻችሁን በኃይል አትግዙ” (1ኛ ጴጥ 5፡3)  በሚለው ቅዱስ ቃል መሠረት ምሳሌ የሚሆነን እና የቤተ ክርስቲያንን መዋቅር ጠብቆና አስጠብቆ የሚመራን አባት ይሰጠን ማለታችንና የሚተላለፉትንም ስህተታቸውን መናገራችን  አግባብነት ያለው ነው  ብለን እናምናለን” ይላል።  
ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል  የዋሽንግተን ዲሲና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ ሆነው እንዲያገለግሉ ከቅዱስ ሲኖዶስ መመደባቸው የታወቀ ቢሆንም የሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት የደረሰው ደብዳቤ አለመኖሩን መግለጫው ጠቅሷል። ይሁን እንጂ አቡነ ፋኑኤል ለአንዳንድ አብያተ ክርስቲያናት በጻፉት አንድ ደብዳቤ “ከዋሽንግተን ዲሲና ካሊፎርኒያ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት ማለታቸውን፣ አንድም ቀን  ሀገረ ስብከቱንም ሆነ በመዋቅር ሥር ያሉ አብያተ ክርስቲያናትን ሳይመለከቱ  ከመዋቅር በወጡ አብያተ ክርስቲያናት ሽፋን መቀመጥን መምረጣቸውን አስገንዝቧል
አቡነ ፋኑኤል አሜሪካ ከገቡም በኋላ ቢሆን በሚያደርጉት እንቅስቃሴ የሚከተሉት ዋና ዋና ችግሮች የሚታዩ መሆናቸውን ግንዛቤ እንዲወሰድልን እንፈልጋለን ሲል ቀጥሎ የሚከተሉትን ሐሳቦች ይዘረዝራል፦

1.    ቅዱስ ሲኖዶስ በሰጣቸው ኃላፊነት መሠረት ግዴታቸውን እየተወጡ አለመሆኑን
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ብፁዓን አባቶችን ወደ ሀገረ ስብከት ሲመድባቸው ቤተ ክርስቲያንን እና ቤተ ክርስቲያንን መዋቅር ጠብቀው እንዲያስጠብቁ የሚሰጣቸው ኃላፊነት ከፍተኛ ድርሻ እንዳለው የታወቀ ነው ።  በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ መሠረት  ተመድበው ሲመጡ ከሁሉ ነገር በፊት አስቀድመው  ሀገረ ስብከቱንና የሀገረ ስብከቱን ጽ/ቤት ማነጋገር ሲጠበቅባቸው ይህንን ጉዳይ ወደ ጎን በመተው ከዚህ በፊት በለመዱት አካሄድ ከቤተ ክርስቲያን መዋቅር ውጭ በሆነ አካሄድ  ግለጽነት በጎደለው መልኩ ከሀገረ ስብከቱ እና ቅዱስ ሲኖዶስ ከሰጣቸው ኃላፊነት መደበቅን መርጠዋል። የሀገረ ስብከትንና የአብያተ ክርስቲያናትን መዋቅራዊ አደረጃጀት ከመከተል ይልቅ የጉርብትና አኗኗርን መርጠዋል። የቤተ ክርስቲያንን መዋቅር ጠብቀው እንዲሄዱ ቅዱስ ሲኖዶስ የወከላቸው መሆኑን ከመግለጽ ይልቅ  የቤተክርስቲያናችን ቃለ ዐዋዲ በማይፈቅደው መልኩ መዋርንና ሥርዓትን ባላጠበቀ መልኩ መንቀሳቀስን መርጠዋል። የቤተ ክርስቲያን መዋቅር አንድ መሆኑን መግለጽ የማይችሉና የሚያፍሩበት ከሆነ መዋቅር ይጠበቅ አለበት ብለው አገልግሎታቸውን ከሚያከናውን አብያተ ክርስቲያናት ጋር  በእውነት ላይ ተማምኖ በጋራ መስራት የማይቻል  የጀመሩት አክሄድ አመላካች ሆኗል። ይህንን ስንመለከት ቅዱስ ሲኖዶስ በሰጣቸው ኃላፊነት መሰረት እየተጓዙ ባለመሆኑ ጉዳዩን  ቅዱስ ሲኖዶስ በመመልከት ውሳኔ ሊሰጥበት የሚገባ ጉዳይ መሆኑን አምነንበታል።

2.   የተቋቋመ የዋሽንግተን ዲሲና አካባቢው ሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት እያለ በራሳቸው ፈቃድ  የዋሽንግተን ዲሲና የካሊፎርኒያ ሀገረ ስብከት  ፤ በሚል  አዲስ ጽ/ቤት መስርተው እየንቀሳቀሱ በመሆኑ፤
ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል የተመደቡት ለዋሽንግተን ዲሲና አካባቢው ሀገረ ስብከት ከሆነ መስራት የሚገባቸው ከሀገረ ስብከቱ ጋር ነው ። የሀገረ ስብከቱን ጽ/ቤት ፤ የሀገረ ስብከቱን ሥራ አስፈጻሚ ጉባኤ እና በመዋቅር ስር የኒገኙ አብያተ ክርስቲያናት ጋር አብረው መስራት እንደሚገባቸው ሳያምኑ የሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ ሆነው ያገለግላሉ ማለት አስቸጋሪ ነው ። ከዚህ በፊት ብዙ ጥረት ተደርጎ የዋሽንግተን ዲሲና አካባቢው ሀገረ ስብከት በአሜሪካ መንግሥት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሕጋዊ መኪል መሆኑ ተረጋግጦ  እና ፈቃድ ተሰጥቶት እያለ ፤ ሕጋዊ እውቅና ያለውን ሀገረ ስብከት ሳያነጋግሩ ወይም ከቅዱስ ሲኖዶስን ፈቃድ ሳያገኙ ፤በራሳቸው አካሄደ “ የዋሽንግተን ዲሲና የካሊፎርኒያ ሀገረ ስብከት” በሚል ከዚህ ቀደም በሰውም ሆነ በሕግ የማይታወቅ  ጽ/ቤት አቋቁመው መንቀሳቀስ መጀመራቸው ብዙዎችን አስገረሟል። ይህ አካሄዳቸው ለእኛም የቤተ ክርስቲያን መዋቅር ለመጠበቅ የጸና አቋም የሌላቸው መሆኑንና እውነትን ለመሸከም ፈቃደኝነት እንደሌላቸው አመላካች ሆኗል ። በቅርቡም የተወሰኑ አብያተ ክርስቲያናትን ስብሰባ በጠሩበት ደብዳቤም በሀገረ ስብከቱ መዋቅር ስር የማይገኘውን የደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን አድራሻ በመጠቀም፤ በመቀመጫ እና ቋሚ አድረሻ የሌለውን ጽ/ቤት  የታወቀና አድራሻ ያለው ለማስመሰል ስብሰባዉንም  በሀገረ ስብከቱ መዋቅር ባተካተተው በዚሁ ቦታ ለማድረግ ተነስተዋል። ይህ ያለውን ሀገረ ስብከት  እንደሌለ የመቁጠርና በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ የተቋቋመውን የሀገረ ስብከቱን ህልውና በመናቅ ለቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ እና የበላይነት ያላቸውን አነስተኛ ግምት አሳይተዋል ።
3.   የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓትና ሕግ ለመጠበቅ ፍላጉትና አቋም እንደሌላቸው እየገለጹ በመሆናቸው
ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ለአንዳንድ አብያተ ክርስቲያናት ባሰራጩት ደብዳቤ እንደገለጹት በሰሜን አሜሪካ የሚገኙ በመንበረ እና ሀገረ ስብከት መዋቅር ያልተካተቱ  አብያተ ክርስቲያናት ያላቸው ደንብ እንዳለ እንዲቀመጥ ፍላጎታቸውንና ፈቃዳቸው መሆኑን በዚሁ ደብዳቤ ገልጸዋል። በሰሜን አሜሪካ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት በተለይም ከመዋቅር ውጭ ሆነው የሚገኙ የተለያየና ግራ የሚያጋባ መተዳደሪያ ደንብ እና መመሪያ  እንዳላቸው ቅዱስ ሲኖዶስ ግንዛቤ እንዲወስድ እንፈልጋለን። በአንዳንዶቹ  የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ስም በጭራሽ እንዳይነሳ ደንብ ያለበት   የሌሎች ደግሞ  የቤተ ክርስቲያንን ባለቤትነት ለተወሰኑ ሰዎች  የሰጠ ፤   ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ሆነ ከሀገረ ስብከት ጋር  መዋቅራዊ ግንኙነት እንደሌላቸው በግልጽ የተቀመጠበት ፤ በቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ሳይሆን ባዘጋጁት መተዳደሪያ ደንብ መሰረት የሚመሩ ፤ ቅዱስ ሲኖዶስ  ያለው የውሳኔ ድርሻ  የማይታይበት ፤ ካህናት በመሪነት የማያስተዳድሩበት እና ቦርድ የመጨረሻ ወሳኝ አካል የሆነበት እና የመሳሰሉ ጉዳዮቸ ያሉበት መሆኑ እየታወቀ ሁሉም እንዳለ እንዲቀመጥ ፈቃዳቸውን ገና ከጅምሩ ያላቸውን ፍላጎትና አቋም የሚያመላክት ነው ።  የቅዱስ ሲኖዶስን ውክልና ይዞ የሚመደብ ሊቀ ጳጳስ ይህንን ያህል ሕግ ይተላለፋል ብሎ መገመት ቢከብድም በብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ግን ተፈጽሟል።

4.   በቅዱስ ሲኖዶስ ጉዳዩ ታይቶ እንዲቆም የታዘዘውን የውጭ ግንኙነት ማስተባበሪያ ጽ/ቤት በራሳቸው ፈቃድ ብቻ እንዲንቀሳስ እያደረጉ በመሆኑ
የሀገረ ስብከቱ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ መስከረም 30 ቀን 2004 ዓ. ም በላከው ቃለ ጉባኤ ለቅዱስ ሲኖዶስ እንደገለጸው፤ ያለ ቅዱስ ሲኖዶስ ፈቃድና እውቅና ፤ የተቋቋመበትም ዓላማና ተግባር ግራ የሚያጋባ ው የውጭ ግንኙነት ማስተባበሪያ ጽ/ቤት አስፈላጊነቱ በአብያተ ክርስቲያናቱ ያልታመነበት መሆኑን በመግለጽ ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ እንዲሰጥበት ማሳሰቡ ይታወሳል። ቅዱስ ሲኖዶስ ጉዳዩን ተነጋግሮ ጽ/ቤቱ እንዲዘጋ መወሰኑንም መረዳት ችለናል። ጥናት ሳይደረግበት  ፤ ውይይት ስምምነት ሳይደረግ  አሁንም የቅዱስ ሲኖዶስን መመሪያ በመተላለፍ ይህ ጽ/ቤት በእርሳቸው ፈቃድ ብቻ እንዲንቀሳቀስ እውቅና እየሰጡ መሆኑን ተረድተናል ። ይህ ተግባር ቅዱስ ሲኖዶስን አለማክበርና ብዙዎችንም ለቅዱስ ሲኖዶስና ለቤተ ክርስቲያን ያላቸውን ክብር እንዲቀንስ የሚያበረታታ ሲሆን ይህ አካሄዳቸው ከመዋቅር ተለይተው በሚገኙ አብያተ ክርስቲያናትም ዘንድ ለትዝብት ዳርጓቸዋል።
በአጠቃላይ ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል የዋሽንግተን ዲሲና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ ሆነው እንዲያገለግሉ የተጣለባቸውን ኃላፊነት በመዘንጋት የሀገረ ስብከት ጽ/ቤትም ሆነ ሥራ አስፈጻሚ ጉባኤ በማያውቀው ሁኔታ በአዲስና እንግዳ በሆነ መዋቅር እየተጓዙ ፤ የሀገረ ስብከቱን ሕጋዊ አሰራር በመከተልና ትክክለኛ አቋም ማሳየት እስካልቻሉ ድረስ  የሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ ናቸው ብለን ለመቀበልና አብሮ ለመስራት አስቸጋሪነቱን አምነንበታል ። ስለዚህ ቅዱስ ሲኖዶስ ይህንን  አሳሳቢ ችግርና አካሄድ በመረዳት  በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የዋሽንግተን ዲሲና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እንዲመድብልን እየጠየቅን ለዚህ ጉዳይ ከቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ እስከሚሰጠን ደረስ የምናደርገውን የሥራ  እንቅስቃሴ ለመንበረ ፓትርያርክና ለቅዱስ ሲኖዶስ /ቤት በየጊዜው  የምናቀርብ መሆኑን  በታላቅ ትህትና እንገልጻለን።” ሲል ያጠቃልላል።

የመግለጫውን ሙሉ ቃል ማንበብ ከፈለጉ ይህንን ይጫኑ።

ቸር ወሬ ያሰማን፣
አሜን
የመላው ዓለም የተዋሕዶ ቤተሰብ

1 comment:

  1. We need to let Holy Sinod know what he is doing. Posting online only doesn't make positive change. All of our Holy Sinod members must be aware of his mission against our mother church.
    May God be with our mother church and all yetewahedo lijoch amen!

    ReplyDelete