Friday, June 22, 2012

በጀርመን የቅ/ሚካኤል በዓለ ንግሥ በመናፍቁ “ቄስ” በገዳሙ ደምሳሽ ምክንያት በውዝግብ አበቃ



(ደጀ ሰላም፤ ሰኔ 15/2004 ዓ.ም፤ ጁን 22/ 2012/ READ THIS NEWS IN PDF):- በደመቀ ሁኔታ ተጀምሮ የነበረው የቅዱስ ሚካኤል በዓለ ንግሥ ሆን ብለው ከረፈደ በቦታው በተገኙት መናፍቁ «ቄስ» ገዳሙ ደምሳሽ ምክንያት በውዝግብ አበቃ። በሀገረ ጀርመን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በኑፋቄያቸው ምክንያት በምእመናን ዘንድ ትልቅ ቁጣን እያስነሱ ያሉት መናፍቁ “ቄስ” በገዳሙ ደምሳሽ “ከልካይ የለኝም” በሚል መንፈስ በአካባቢያቸው የሚገኙ ደጋፊዎቻቸውን በአውቶብስ ጭነው ከአካባቢያቸው ወጥተው በአገልግሎት እንዳይስተፉ ብፁዕ አቡነ እንጦንስ የጣሉባቸውን እግድ በመተላለፍ እሑድ ሰኔ ፲ ቀን ፳፻፬ ዓ/ም በቅዱስ ሚካኤል ዓመታዊ ክብረ በዓል ላይ በመገኘት ብጥብጥ እንዲነሳ ምክንያት ሆነዋል።


ገዳሙ ከግብር አበሮቻቸው ጋር
በጀርመን በአራቱም አቅጣጫ ካሉት የኢ/ኦ/ተ አብያተ ክርስቲያናት በኮሎኝ ከተማ የሚከበረውን ዓመታዊውን የሊቀ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤልን የንግሥ በዓል ለማክበር ከዋዜማው ጀምሮ በታላቅ ቁጥር ተገኝተው የነበሩት ምእመናን በዓሉን በደመቀ ሁኔታ በማክበር ላይ ሳሉ ግለሰቡ እሑድ ጠዋት ግብር አበሮቻቸውን ይዘው በአገልግሎት ላይ ያሉ በሚመስል መልኩ ፈረጅያቸውን ለብሰው፤ ቆባቸውን አጥልቀው በቤተ ክርስቲያኑቱ የተገኙ ሲሆን ታቦተ ሕጉ ወጥቶ፤ ዑደቱ አብቅቶ፤ ምእመናኑ ቃለ ምእዳን የሚሰጥበት ቦታ በመሰባሰብ ላይ ሳሉ እኚሁ ግለሰብ ከካህናቱ ጋር ለመቆም ወደፊት ለመቅረብ በሚሞክሩበት ጊዜ በግለሰቡ በቦታው መገኘት በተለይም የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በግለሰቡ ላይ የጣሉት የእንቅስቃሴ እግድ አለመከበሩ ያቃጠላቸው ምእመናን በንዴት “፤ወደ ታቦተ ሕጉ አይቀርቡም አልተፈቀዶለትም” ብለው መንገድ ዘግተውባቸዋል። በዚህ ጊዜ በዋነኝነት መንገዱን ዘግተው ወደፊት አይሄዱም ብለው ከፊታቸው የከለከልዋቸውን ጎበዝ ምእመን ገፍትረው ለመሄድ በመሞከራቸው ረብሻ እንዲነሳ ምክንያት ሆነዋል።

ምንም እንኳን ግለሰቡ በበዓሉ በመገኘታቸው ምክንያት ከሚፈጠረው ግርግር እተርፋለው ብለው ያሰቡ ቢሆንም እንዳሰቡት ሳይሆን በተቃራኒው አጋጣሚውአብዛኛውን ምእመን ለቤተ ክርስቲያኑ ያለውን ቀናዒነት፤ ተቆርቋሪነት እና የመንፈስ አንድነት አሳይቶ አልፏል። ግለሰቡ ግርግሩን ካስነሱ በኋላ ተጎጂ በመምሰል ፖሊስ ለመጥራት ቢሞክሩም በቦታው የተገኙት ፖሊሶች ሁኔታውን በአግባቡ አገናዝበው ምእመኑም በግለሰቡ ላይ ለምን ቁጣ እንዳነሳ ተነግሯቸው ምንም የከፋ ነገር ሳይፈጠር ተመልሰዋል። ይልቁንም “ወደ ታቦተ ሕጉ አይቀርቡም” ብለው የከለከሏቸውን  ምእመን ከግለሰቡ ግብረ አበሮች መካከል አንዱ “ደምሽን ነው የማፈሰው” የሚል ዛቻ በመናገሩ ፖሊሶቹ በግለሰቡ ላይ ክስ መመሥረት የሚቻል መሆኑን አሳውቀዋል። 

አባ ብርሃነመስቀል ምእመኑን ሲያረጋጉ
በአጠቃላይ በተፈጠረው ክስተት እጅግ የተቆጣውን አብዛኛውን ምእመን ደጉ የበርሊን ቅዱስ አማኑኤል ቤተ ክርስቲያን አባት አባ ብርሃነመስቀል ተድላ ከመካከላቸው በመገኘት ያረጋጉ ሲሆን የምእመናኑን ጥያቄ እንደሚረዱ፤ ከሌሎች አባቶችም ጋር ጉዳዩን እየተመለከቱት መሆኑን፤ ምላሹንም በቅርብ ጊዜ ውስጥ እንደሚያሳውቁ በመግልጽ ሕዝበ ክርስቲያኑ በሰላም ወደ ቤቱ እንዲመለስ አድርገዋል።

በዓሉ ከመከበሩ ሁለት ቀናት ቀደም ብሎ በነበረው የካህናት ስብሰባ እና በዋዜማው ጸሎት ላይ ያልተገኙት የቪዝባደኑ አለቃ እሑድ ረፋድ ላይ ማኅሌቱ አብቅቶ “አሐዱ አብ” ተብሎ ቅዳሴ ከተጀመረ በኋላ፤ መልእክታት ሲነበቡ ለመግባት ያመቸኛል ባሉበት፤ ምእመናንም በሰቂለ ኅሊና በነቂሐ ልቡና የቅዳሴውን ተሰጥዖ በመከታተል ላይ ሳሉ ድንገት ብቅ ቢሉም፤ ምእመናኑ ቅዳሴ ከተጀመረ በኋላ ቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ ጭቅጭቅ መፍጠሩ ተገቢ አለመሆኑን በመረዳት ወደውጭ እስኪወጡ ድረስ ጠብቀው አግባብ ነው ያሉትን ነገር አድርገዋል። የግለሰቡ አመጣጥ በእርግጥም ረብሻ እና ግርግር ለማስነሳት እንደሆነ ግልጽ የሚያደርገው በካህናት ስብሰባው እና በዋዜማ ጸሎቱ ላይ ሳይገኙ እሑድ ዘግይተው መገኘታቸው ሲሆን የጸሎቱን ሥነ ሥርዓት ከግማሽ ለመካፈል ከቪዝባደን ድረስ አውቶብስ ተኮናትሮ ከረፈደ የሚያስመጣ ሌላ ምን ምክንያት አለ ያሰኛል።  

ፓሊስ በምእመኗ ላይ የዛተውን ግለሰብ ሲያነጋገሩ
ይህ ሁሉ ሲሆን ግን የግለሰቡን ብልጣብልጥነት ያላስተዋሉ ይልቁንም በየዋህነታቸው መጠቀሚያው የሆኑ አንዳንድ የቪዝባደን እና የፍራንክፈርት ምእመናን ጉዳዩን ከሃይማኖት አኳያ ማየት አለመቻላቸው ብዙዎችን አሳዝኗል። ገና ነገሩ እዚህ ደረጃ ሳይደርስ “ግለሰቡ እውነተኛ ማንነታቸውን በካባቸው ሸፍነው የገቡ መናፍቅ ናቸው” እየተባለ ከዓመታት በፊት በምእመናኑ በኩል አቤቱታ በሚቀርብበት ጊዜ ወገባቸውን ይዘው ለግለሰቡ ኦርቶዶክሳዊነት ሲከራከሩ የነበሩ ሰዎች፤ እንደውም የቀኝ እጃቸው ናቸው እስክመባል የደረሱ ዛሬ በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያናቸው ፈጽሞ የሉም። ያሉት በመናፍቃን አዳራሽ ነው። ለዚህም እንደ ማሳያ በዋነኛነት ከሚጠቀሱት ምእመናን መካከል አንዷ ወ/ሮ ጥሩወርቅ ፈለቀ ናቸው። እኚህ ወይዘሮ የቅዱስ ጊዮርጊስን ቤተ ክርስቲያን በቪዝባደን ካቋቋሙ ግለሰቦች መካከል  አንዷ ሲሆኑ በሰበካ ጉባኤ አባልነትም በአጥቢያው ያገለገሉ፣ ንዋያተ ቅድሳትን ከራሳቸው ገንዘብ እያወጡ ሳይቀር ሲያሟሉ የነበሩ ቅን ወይዘሮ ነበሩ። ወ/ሮ ጥሩወርቅ ዛሬ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ይቀበሉባት በነበረችው በተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናቸው የሉም። በእልቅና ካባ ከመቅደሳችን በገቡት መናፍቅ ምክንያት የመናፍቃኑን ጎራ ተቀላቅለዋል። ትናንትና ግለሰቡን “ፍጹም ኦርቶዶክሳዊ ነው” እያሉ እንዳልተከራከሩላቸው ዛሬ እሳቸው ራሳቸው የግለሰቡን እውነተኛ ማንነት በግልጽ በሚያሳይ መልኩ የሃይማኖት ቤታቸውን ጥለው ወጥተዋል። እዚህ ጋር አንባቢዎች ልብ እንዲሉ የሚገባው እኚሁ ወይዘሮ በራሳቸው ቃል “ሃይማኖትን ያስተማረኝ፤ ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር ያስተዋወቀኝ ቄስ ገዳሙ ነው” ብለው በመድረክ መናገር ብቻ አይደለም በቪዝባደን ከተማ በጀርመንኛ በሚታተም የአካባቢው ጋዜጣ ምስክርነት የሰጡ መሆናቸውንም ጭምር ነው።

ወሮ ጥሩወርቅ ከ«ቄስ» ገዳሙ ጋር
የወይዘሮ ጥሩወርቅ መውጣት በጀርመን ትልቅ መነጋገሪያ መሆኑና በእኩይ ሥራቸውም ላይ የፈጠረውን ተጽእኖ የተረዱት የቪዝባደኑ አለቃ፤ በመጀመሪያ “አንድ ግለሰብ ከቤተ ክርስቲያን ወጣ እና ምን ይፈጠር?” ሲሉ ከቆዩ በኋላ ጫናው ሲበረታባቸው ወይዘሮዋን ጎትጉተው አምና የደብረዘይት ዕለት “ወደ ቤተ ክርስቲያኔ ተመልሻለሁ” እንዲሉ ያደርጋሉ። በዕለቱም ድግስ ተደግሶ ወይዘሮዋ ንግግር እንዲያደርጉ ነገር ግን ማንም ጥያቄ እንዳያነሳ ለአስተያየት ብቻ ግን በአካባቢው ለሚታወቁ እና ለግለሰቡ ባላቸው ድጋፍ ታማኝ ለሆኑ ሰዎች እድሉ ተሰጥቶ “ቄስ” ገዳሙም “ወደ ቤቷ እንደምትመለስ ቀድሞ ራእይ ታይቶን ነበር” ብለው ነገሩን አደባብሰው ያልፋሉ። ብዙ አልቆየም፤ እንደ መምህራቸው ከልብ ያልሆነው መመለስ ለፕሮፓጋንዳ ፍጆታ ብቻ ስለነበር፤ ወይዘሮዋ ደግመው ወደ መናፍቃኑ አዳራሽ ከመሄዳቸውም ባሻገር ሌሎችን ወደዚሁ ስብስብ ጋባዥ ሆነዋል።

ታዲያ በአካባቢው ሕዝበ ክርስቲያን ላይ በዚህ ዓይነት ቀልድ አይሉት ድራማ በሚመስል ሁኔታ ሲሳለቁበት “በአጥቢያው ያሉት ምእመናን ምነው መንቃት አቃታቸው?” ያሰኛል። እንደ አንድ ምሳሌ እኚህ ወይዘሮ ተጠቀሱ እንጂ ሌሎች በርካታ የግለሰቡ የቅርብ ወዳጆች የሆኑ ግለሰቡን “በባህል እና በአሮጌ ልማድ ከተተበተበች ከኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ያወጣን ታላቅ ወንጌላዊ ነው፤ በቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሆኖ የሚሠራው ሥራ ቀላል አይደለም” እያሉ የሚያሞካሹ ቤተ ክርስቲያናቸውን ክደው የወጡ ጥቂቶች አይደሉም። የግለሰቡ ደጋፊዎች የሆኑቱ ይህን ሁላ እየተመለከቱ፤ ጌታም በወንጌሉ “ሐሰተኛ መምህራንን ከፍሬአቸው ታውቁአቸዋላችሁ” ብሎ እንደተናገረው እዛው ከመካከላቸው ለ«ቄስ» ገዳሙ በጣም ቅርብ የሆኑ፤ “መጽሐፍ ቅዱስን ከሳቸው ተማርን” የሚሉ፤ የሐሰተኛ መምህራቸው የገዳሙ ደምሳሽ ፍሬ የሆኑትን ሰዎች አንድ በአንድ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ሲወጡ እያዩ፤ ማስተዋል በጎደለው መልኩ ለግለሰቡ ጥብቅና መቆማቸው በእውነትም ብዙዎችን አሳዝኗል።

በሌላ በኩል በጀርመን የሚገኘው የምእመናን ኅብረት ከቀደመው ጊዜ በተለየ መልኩ በመጠናከር ጉዳዩን ለሚመለከታቸው አካላት በሙሉ እያሳወቀ ሲሆን በቅርቡ በጉዳዩ ዙሪያ ጠንካራ ይዘት ያለው ደብዳቤ ለሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ መላኩ ታውቋል። የዚህኑ ደብዳቤ ግልባጭም ከጠቅላይ ቤተ ክህነት አንስቶ በጀርመን ለሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት አስተዳዳሪዎች በሙሉ ልኳል። “ጠባቂ እረኛችን ይሆኑ ዘንድ በላያችን የተሾሙ ካህናት በጎቻቸው የምንሆን ምእመናን ለቀሳጢ ተኩላ ተላልፈን ስንሰጥ እስከመቼ ይሆን ዝም የሚሉት? ከበቂ በላይ ማስረጃ የተያዘባቸው ግለሰብ እውነተኛ ማንነታቸውን ጮኸው የሚናገሩ መጻሕፍቶቻቸውን በአደባባይ እየቸረቸሩ፤ ሐሰተኛ ትምህርታቸውን ምንም በማያውቁ በየዋህነት በተሰበሰቡ ምእመናን ላይ ሲረጩ፤ በቀን ፀሐይ በጎቻቸውን ከመንጋቸው እየነጠቁ ሲወስዱ ለምን ይሆን በዝምታ የሚታለፉት? በእውነት ይህ የሚሆነው እስከ መቼ ነው?” ሲል ለሊቀ ጳጳሱ ያሳሰበው ኅብረቱ “ትእግስታችንም ተሟጦ አልቆ የራሳችንን እርምጃ ከመውሰዳችን በፊት ለችግራችን የበኩልዎን አስቸኳይ መፍትሄ ይሰጡን ዘንድ ለመጨረሻ ጊዜ አንድ በምታደርገን፣ ጌታችን እና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደሙ በዋጃት በቅድስት ቤተክርስቲያናችን ስም በልጅነት መንፈስ እና በታላቅ አክብሮት እንጠይቅዎታለን” በማለት ለመጨረሻ ጊዜ ነው ያለውን ጥያቄውን አቅርቧል።

ከዚህ በተጨማሪም በጀርመን የሚገኙ ኦርቶዳክሳዊ ምእመናንን በጠንካራ ሁኔታ እያስተባበረ ሲሆን ምእመናኑም ጉዳዩን በሚገባ ተገንዝበው የማያወላዳ አቋም እንዲይዙ፤ ቤተ ክርስቲያናቸውንም የመጠበቅ ኃላፊነት እንዳለባቸው በማሳሰብ በራሪ ወረቀት በጀርመን በሚገኙ አድባራት አሰራጭቷል፤ የኅብረቱን ወቅታዊ እንቅስቃሴዎችም እንዲከታተሉ የሚረዳ Yememenan Hibret የሚል የፌስቡክ ገጽ በመክፈት መረጃዎችን እያስተላለፈ ይገኛል።
ለብፁዕ አቡነ እንጦንስ የተላከውን ደብዳቤ እና በራሪ ወረቀቱን ለመመልከት እዚህ  ጋር ይጫኑ። 
ቸር ወሬ ያሰማን፤
አሜን፡፡
የተዋሕዶ ቤተሰቦች በመላው ዓለም

No comments:

Post a Comment