Wednesday, June 6, 2012

በደብረ ይድራስ ቅ/ጊዮርጊስ ተቃዋሚዎችን ለመበተን የተሰማራው ፖሊስ አስለቃሽ ጢስ ይዞ ቤተ መቅደስ ገባ


  • በአስለቃሽ ጢሱ ጸሎተ ቅዳሴው ታጉሏል፤ ሕፃናት፣ ምእመናንና አገልጋዮች ታፍነዋል::
  • ለውዝግቡ መፍትሔ ያፈላልጋል የተባለ ጥምር ኮሚቴ ተቋቁሟል::
  • ከ70 - 80 የሚደርሱ የደብሩ ሠራተኞችና ምእመናን እንደታሰሩ ናቸው::
  • ከንቲባ ኩማ ደመቅሳ ሊቀ ጳጳሱን በስልክ አነጋግረዋል::

(ደጀ ሰላም፤ ግንቦት 29/2004 ዓ.ም፤ ጁን 6/ 2012/ READ THIS ARTICLE IN PDF)፦ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ በሚገኘው ደብረ ይድራስ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ከይዞታ ማስከበር ጋራ በተያያዘ ትናንት፣ ግንቦት 27 ቀን 2004 ዓ.ም ጠዋት በአጥቢያው ምእመናን መካከል ግጭት ተቀስቅሷል፤ በግጭቱ የአንድ ፖሊስ ሕይወት አልፏል፤ ስድስት ፖሊሶችና በርካታ ምእመናንም ተጎድተዋል፤ ብዙዎቹን የደብሩ ሰበካ ጉባኤ አባላትንና ሌሎች ሠራተኞችን ጨምሮ በቁጥር ከ70 - 80 የሚሆኑ የአጥቢያው ወጣት እና አዛውንት ምእመናን ከየመንደሩ በፌዴራል ፖሊስ አባላት እየተሰበሰቡ መታሰራቸው ነው የተነገረው፡፡

ግጭቱ እየቀጠለ በነበረበት ኹኔታ ለጸሎተ ቅዳሴ የተሰበሰበውን ሕዝብ ለመበተን በሚል ፖሊስ ወደ ቤተ መቅደሱ ዘልቆ በመግባት አስለቃሽ ጭስ መጠቀሙ ተመልክቷል፤ በዚህም በመካሄድ ላይ የነበረው ጸሎተ ቅዳሴ ታጉሏል፤ ለቍርባን የተዘጋጁ ሕፃናት፣ ሌሎች ምእመናንና አገልጋዮችም በጭስ የመታፈን አደጋ ደርሶባቸዋል፡፡ የሕን ቤተ ክርስቲያኑ በሮችና መስኰቶች መንሥኤው ለጊዜው ባልታወቀ ኹኔታ የተበሳሱና የተሰባበሩ ሲሆን የደብሩ አስተዳደር ቢሮዎች፣ የጥምቀተ ክርስትና ቤትና ሌሎችም በሮች “የተደበቁ ሰዎችን ለማሰስ” በሚል መዝጊያዎቻቸው እየተሰበረ ፍተሻ እንደተካሄደባቸው ተገልጧል፡፡
ከንቲባ ኩማ ደመቅሳና ‹የፓትርያሪኩ ልዩ ሀገረ ስብከት› በሚል ከሚታወቀው የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የረዳት ሊቀ ጵጵስና ሓላፊነታቸው እየለቀቁ ያሉት ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ በጉዳዩ ላይ በስልክ መነጋገራቸው ተሰምቷል፤ በግጭቱ አንድ ፖሊስ መሞቱንና ሌሎች ስድስት አባላት መቁሰላቸውን የተናገሩት ከንቲባ ኩማ የታሰሩት ምእመናን እንዲፈቱ ብፁዕ ሊቀ ጳጳሱ ያቀረቡላቸውን ጥያቄ እንዳልተቀበሉ ተሰምቷል፡፡

በአሁኑ ወቅት የደብሩ የክብረ በዓል (ንግሥ) እና መስቀል ደመራ ፍራ የነበረውን ይዞታ የቀበሌ 06 ጽ/ቤት (የኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ) ለመከለል የጀመረው ሂደት እንዲቆም ተደርጎ ውዝግቡን የሚያጣራ ኮሚቴ መቋቋሙ ተነግሯል፡፡ ኮሚቴው ከደብሩ ሰበካ ጉባኤ፣ ከአጥቢያው ምእመናን፣ ከክፍለ ከተማው አስተዳደርና ከአዲስ አበባ ከተማ ፖሊስ የተውጣጡ አባላት የሚገኙበት ነው፡፡
ግጭቱ ትናንት ጠዋት ከመቀስቀሱ ቀደም ብሎ የአጥቢያው አስተዳደር፣ አገልጋዮችና ምእመናን በፖሊስ ታጅቦ የመጣውን ግብረ ኀይል በባንዲራው እያሉ ሲማፀኑ ነበር፤ እነርሱ ራሳቸው ይዞታቸውን ለማስከበር በተደጋጋሚ ሲያመለክቱበት የቆዩበትና አሁንም ከፓትርያኩ ጋራ እየተነጋገሩበት በመኾኑ ግብረ ኀይሉ ወደ ርምጃ ከመግባቱ አስቀድሞ ሁለት ቀናት እንዲሰጣቸው ሲጠይቁም እንደ ነበር ተዘግቧል፡፡

ምእመናኑ የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ ይዘው ለሚያቀርቡት ተማኖ ቦታ ያልሰጠው ግብረ ኀይሉ ግን አጥሩን ወደ ማፈራረስና ችካል ወደ መቸከል ተግባር በመግባቱ ምእመናኑ ርምጃውን ድንጋይ በመወርወር ሲከላከሉ የአድማ ብተና ፖሊስ ደግሞ በቆመጥና በአስለቃሽ ጭስ ምእመናኑን ለመበተን መሰማራቱ ተገልጧል፤ ጥይትም ተተኩሷል፡፡ የችካል ምልክቱ የሚያርፍበት ቦታ ከዐውደ ምሕረቱ ያለው ርቀት ከኀምሳ ሜትር እንደማይበልጥ የዐይን እማኞች ተናግረዋል፡፡ የደብሩ አስተዳደር በዚህ ይዞታው ላይ በአንደኛ ደረጃ ት/ቤት ግንባታና በሌሎችም ትልሞች የራሱን የራስ አገዝ ልማት ዕቅዶች ለማካሄድ ሲንቀሳቀስ እንደ ነበር ለመረዳት ተችሏል፡፡

በአሁኑ ወቅት በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሚገኙ በርካታ አድባራትና ገዳማት የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ እንዳገኙ ተዘግቧል፡፡ በአንዳንዶቹም÷ ለአብነት ያህል በኮተቤ ደብረ ልዑል ቅዱስ ገብርኤል÷ የቤተ ክርስቲያን ይዞታ ለግለሰብ ጥቅመኞችና ለፕሮቴስንታቶች በመሰጠቱ የወረዳው ፖሊስ ጽ/ቤት የየካ ክፍለ ከተማ ችግር ከመፈጠሩ በፊት በጉዳዩ እንዲያስብበት ያቀረበው ጥያቄ ይገኝበታል፡፡

በደብረ ይድራስ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያንም የትናንቱ ችግር በተዘገበው ደረጃ እንዲባባስ ያደረገው አሁን እስከ ዐውደ ምሕረቱ የዘለቀው የይዞታ ነጠቃ ብቻ ሳይሆን የቀበሌው ጽ/ቤት ቀደም ብሎ የደብሩ ካህናት መኖሪያ ቤት ተሠርቶበት የነበረውን ቦታ በመውሰድ ኮንዶሚኒየምና የቀበሌ ጽ/ቤት ሲሠራበት በዝምታ በመታለፉ መሆኑን አስተየየታቸውን ለዜና ሰዎች የሰጡ የሰበካው ምእመናን ገልጸዋል፡፡

በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ (ከፍተኛ 24 ቀበሌ 14 59 ቁጥር ማዞርያ) አውግስታ ሸሚዝ ፋብሪካ አካባቢ የሚገኘው የደብረ ይድራስ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ከ23 ዓመት በፊት፣ በ1981 ዓ.ም የተመሠረተ ደብር ነው፡፡
ይድራስ የዱድያኖስ ጭፍሮች የሊቀ ሰማዕታት ቅዱስ ጊዮርጊስን ዐፅም አቃጥለውና ፈጭተው የበተኑበት ተራራ ስም እንደ ኾነ ይታወቃል፡፡

ቸር ወሬ ያሰማን፤
አሜን

የተዋሕዶ ቤተሰቦች በመላው ዓለም

3 comments:

  1. ጎበዝ እስከ መቼ ይሆን የመንግሥት አካላት ቤተክርስቲያን ላይ እንዲህ አይነት ሥራ ሲሰሩ እያየን ዝም የምንለው፣ ጽላቶቻችን እኮ ከመቅደሱ ወስደው ታስሯል ሊሉን ምንም አልቀራቸውም። እንባ አስመጪ ጭስ በመቅደስ ውስጥ??? እረ እስከ መቼ ነው ዝምታችን የሚቀጥለው፥ እስከ መቼ አድር ባይ ሆነን እንኖራለን ቀስ ብለው እኮ የቦሌ መድኃኒዓለም ለመንገድ ስራ ስለምንፈልገው ይፍረስ ሊሉን እኮ ይችላሉ፣ ወይም ማህተብ አስሮ ሕዝብ በተሰበሰበት መገኘት ክልክል ነው ልንባል እኮ እንችላለን አሁን ዝም ካልን
    እኔ አላማረኝም በበኩሌ እዛው መንግሥትንም ሆነ በቤተክህነት ውስጥ ያሉትን የመንግሥት ጉዳይ አስፈጻሚዎች እንደ አባ ጳውሎስ ወይም አባ ፋኑኤል አይነቱን አንድ ነገር ማድረግ እስካልቻልን ድረስ የነገው በጣም ያስፈራል . . . ልብ ያለው ልብ ይበል እንላለን

    ReplyDelete
  2. No words! Great sorrow! This is the latest open religious persecution in our church in the present day Ethiopia. God Bless our religion! Let's pray heartily!

    ReplyDelete
  3. ye ethiopia gebeze kidus giorges leke semaetate ante ferdune sete nea giorgies semeate eyesus kirstos o futune redete egzoooooooooooooo lejoro yekefale kedase be aslekjash chese sebetene adeheneneeeeeeeee

    ReplyDelete