Wednesday, May 23, 2012

ማ/ቅዱሳን ከሰ/ት/ቤቶች መምሪያ ሥር እንዲወጣና ራሱን እንዲችል ተወሰነ

የቅዱስ ሲኖዶስ ዐሥርኛ ቀን የቀትር በፊት ውሎ


· በፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ አራማጅ ግለሰቦች ላይ የቀረበውን ጥናታዊ መግለጫና የውሳኔ ሐሳብ ደግሞ ከሰዓት በኋላ በመነጋገር እንደሚያጸድቀው ይጠበቃል:: (READ THE DOCUMENT from HERE)

· ማኅበረ ቅዱሳን በአወቃቀሩ ከሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሥር ወጥቶ ለዋና ሥራ አስኪያጁ ተጠሪ እንዲኾን ቅዱስ ሲኖዶሱ ወስኗል::

· በእሳታዊው ዘመን ወደ እሳታዊው ቤተ ክህነት - ቀልጦ መቅረት ወይም ነጥሮ በመውጣት የተቋማዊ ለውጥ አብነት መኾን!!


(ደጀ ሰላም፤ ግንቦት 14/2004 ዓ.ም፤ May 22/ 2012/ READ THIS IN PDF)፦ የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በዛሬው ዐሥርኛ ቀን የቀትር በፊት ውሎው በስምንት የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ እንቅስቃሴ አራማጅ ድርጅቶች ላይ የብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት እና የሊቃውንት ጉባኤ አባላት ጥምር ኮሚቴ ያቀረበውን ጥናታዊ መግለጫ እና የውሳኔ ሐሳብ መርምሮ አጽድቋል፡፡

ምልአተ ጉባኤው በፕሮቴስታንቶች እየተደገፉ የቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ትምህርተ ሃይማኖት፣ ሥርዐተ እምነት፣ ክርስቲያናዊ ትውፊትና ታሪክ በኅቡእና በገሃድ ተደራጅተው ለማፍረስና ለማፋለስ እየተንቀሳቀሱ በሚገኙትና ይህም በማስረጃ በተረጋገጠባቸው ስምንት ድርጅቶች ላይ ያሳለፈው ውሳኔ አራት ዐይነት አፈጻጸሞችን የያዘ ነው፡፡ እነርሱም፡-
1) ቀኖናዊ ርምጃ በመውሰድ ውግዘት የሚተላለፍባቸው፤
2) በሕግ የሚጠየቁ፤
3) በኅትመት ውጤቶቻቸው ላሰራጯቸው እንግዳ ትምህርቶችና ክሕደት ማንነታቸው እየተጠቀሰ ይፋዊ ምላሽ የሚሰጣቸው፤ 4) ድርጅቶቹና መሪዎቻቸው ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያንን የማፍረስ ተልእኮ እንዳላቸው ማንነታቸው በተናጠል እየተጠቀሰ በብዙኀን መገናኛ የሚጋለጡ የሚሉ ናቸው፡፡

በውይይቱ መጀመሪያ ርእሰ መንበሩ አቡነ ጳውሎስ ጥናታዊ መግለጫውና የውሳኔ ሐሳቡ ሌላ ኮሚቴ ተቋቁሞ ድጋሚ እንዲጤንና በሐምሌው የቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ እንዲታይ አልያም በቋሚ ሲኖዶስ ተመርምሮ እንዲጸድቅ የሚሉ ሁለት የተለያዩ አማራጮችን ያቀረቡ ቢኾንም ከአባ ፋኑኤል በቀር የብዙኀኑን የምልአተ ጉባኤ አባላት ተቀባይነት አላገኙም፡፡

ጥናታዊ መግለጫውና የውሳኔ ሐሳቡ በጥቅምቱ ምልአተ ጉባኤ በተሠየመው የብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ኮሚቴ እና የሊቃውንት ጉባኤ አባላት ጥምረት የቀረበ መኾኑን ያስታወሱት የምልአተ ጉባኤው አባላት÷ ድርጅቶቹ ራሳቸው ያሰራጯቸው ማስረጃዎች በአግባቡ ተመርምረው ይህን የመሰለ ሰነድ ከቀረበ በኋላ ሂደቱን ወደ ኋላ መመለስ አስፈላጊ እንዳልኾነ አጽንዖት በመስጠት የርእሰ መንበሩን ሐሳብ ተቃውመዋል፡፡

ቀኖናው ርምጃውን ሊለውጠው የሚችለው በጥምር ኮሚቴው ጥናታዊ መግለጫና የውሳኔ ሐሳብ ላይ በማስረጃነት ቀርበው የተመረመሩት ሰነዶች “የእኛ አይደሉም›› የሚሉ አካላት ቀርበው ሲጠይቁ አልያም ሲያሰራጩት የቆዩትን ኑፋቄ ስሕተትነቱን በይፋ ሲያስተባብሉ መኾኑን የምልአተ ጉባኤው ውሳኔ ያስረዳል፡፡

ከዚህ አኳያ በአቡነ ጳውሎስ በኩል የቀረበውና ከድርጅቶቹ አንዱ የኾነው የአንቀጸ ብርሃን አባል በመኾን መሪጌቶችን፣ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶችን በመመልመል በመጽሐፎች፣ በጽሑፎችና በስልክ ሳይቀር ኑፋቄን በ‹ርቀት ትምህርት› እንደሚያስፋፋ በማስረጃ የተረጋገጠበት አሸናፊ መኰንን የተከሰሰበትን ኑፋቄ ሳይክድ ወይ ሳያምን “ቀርቤ ሳልጠቅ›› በሚል ብቻ የጻፈው ማመልከቻ ተቀባይነት አላገኘም፡፡ ውሎው ከእጅጋየሁ በየነ ጋራ በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የኾነው አሸናፊ በምን እንደሚጠየቅ፣ ምን የውሳኔ ሐሳብ እንደቀረበበት የሚያውቅ እንደመኾኑ መጠን በአቡነ ጳውሎስ ተጽዕኖ ሥር የመጠለል እንጂ የጻፈው ማመልከቻ ኑፋቄውን የመኰነን አልያም አምኖ የመከራከር ይዘት የሌለው እንደኾነ ታውቋል፡፡

ከዚህ አጀንዳ ቀደም ሲል በቀረበው የማኅበረ ቅዱሳንና የሰንበት ት/ቤቶች ማደረጃ መምሪያ ጉዳይ ምልአተ ጉባኤው መምሪያውን በሓላፊነት በሚመሩ ግለሰቦችና በማኅበሩ መካከል በየጊዜው እየተደጋገመ የሚቀርበውን ውዝግብ ከመሠረቱ ያስወግዳል፤ ማኅበረ ቅዱሳንንም በተለይም ካለፉት ድፍን ሰባት ዓመታት አስቸጋሪ መተጋገል በኋላ ለተጠናከረ አገልግሎትና ምናልባትም እርሱን ተከትሎ ለሚመጡ አዲስ ተግዳሮቶች የሚያዘጋጅ ነው የተባለ አዲስ ውሳኔ አሳልፏል፡፡

ይህም ውሳኔ ማኅበሩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ወጣቶችን በሰንበት ት/ቤቶች እንዲያደራጅና እንዲመራ ሓላፊነት ከተሰጠው ከሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሥር ወጥቶ ተጠሪነቱና የሥራ ግንኙነቱ ለመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ የሚያደርግ ነው፡፡

ይህ ውሳኔ ከመሰጠቱ በፊት ብፁዕ አባ ገሪማ በ1994 ዓ.ም ለሦስተኛ ጊዜ ተሻሽሎ በቅዱስ ሲኖዶስ የጸደቀው የማኅበሩ መተዳደርያ ደንብ ክፍተት እንዳሉበት በመጥቀስና በእነ አባ ሰረቀ ሲስተጋባ የቆየውን አቤቱታ በማስተጋባት በማኅበሩ ላይ ክስ ማሰማታቸው ተዘግቧል፡፡

“ይህ ማኅበር እየተበጠበጠ መኖር የለበትም›› በሚል ለክሱ ምላሽ የሰጡት የምልአተ ጉባኤው አባላት ማኅበሩ አንድም ቀን ደንቡ አይሻሻል በማለት ተከላክሎ እንደማያውቅ፣ እንዲያውም ጅምሩን በመውሰድ ማኅበሩ ከሚሰጠው አገልግሎት አንጻር ደንቡ ማሻሻያዎች እንዲደረጉበት መጠየቁን፣ አርቅቆና አጽድቆ የሰጠው ቅዱስ ሲኖዶሱ እስከ ኾነ ድረስም ከጊዜው አንጻር ቃኝቶ የማሻሻል ድርሻም የቅዱስ ሲኖዶስ መኾኑን መናገራቸው ተዘግቧል፡፡

በመኾኑም ከዛሬ፣ ግንቦት 14 ቀን 2004 ዓ.ም ጀምሮ የማኅበሩ ተጠሪነት ከሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሥር ወጥቶ ለብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጁ እንዲኾንና አገልግሎቱን ከብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጁ ጽ/ቤት ሥር በመኾን እንዲፈጽም፣ ይህን አዲስ መዋቅራዊ የተጠሪነት ለውጥ መሠረት በማድረግና ከዚሁ ጋራ በማስማማት ሌሎችም የሕግ ክፍተቶች ተፈትሸው የመተዳደርያ ደንቡ ማሻሻያ ረቂቅ ተጠንቶ ለጥቅምት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ እንዲቀርብ የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ወስኗል፡፡

ይህን ውሳኔ መሠረት በማድረግ የመተዳደርያ ደንብ ማሻሻያና ጥናት ይዞ የሚቀርብ ኮሚቴም በምልአተ ጉባኤው ተሠይሟል፡፡ የኮሚቴው አባላት የኾኑ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፡- 1)ብፁዕ አቡነ ገሪማ፣ 2)ብፁዕ አቡነ ገብርኤል፣ 3)ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፣ 4)ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ እና ማኅበረ ቅዱሳን የሚወክላቸው ሁለት ልኡካን ናቸው፡፡

የቅዱስ ሲኖዶስ የመዋቅራዊ ተጠሪነት ለውጥ ውሳኔ አስመልክቶ አስተያያቸውን እንዲሰጡ የተጠየቁ የጉዳዩ ተከታታዮች በአጠቃላይ በአንድ ጉዳይ ይስማማሉ፤ በሌላው ጉዳይ ደግሞ ስጋትና ተስፋ ያሰማሉ፡፡

የስምምነታቸው ነጥቦች፡- ማኅበረ ቅዱሳን በተማረው ትውልድ መካከል የቤተ ክርስቲያን እጅ ለመኾን ከ20 ዓመት በፊት ግንቦት ወር በራሱ ምርጫና ጥያቄ፣ በቅዱስ ሲኖዶስ መልካም ፈቃድና ቡራኬ ከተደራጀበት ከሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሥር 20 ዓመቱን እያከበረ በሚገኝበት ሰሞን መሠረተ ህልውናውን ጭምር ጥያቄ ውስጥ ካስገባው ውዝግብና ከመምሪያው ሤረኛ ሓላፊዎች ክፋት በመነጠል እንዲገላገል የመደረጉ ታሪካዊነት ነው፡፡

ሌላው ስምምነታቸው ደግሞ የርክበ ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ውሳኔ መነሻ መምሪያውንና በመምሪያው ሥር የተደራጁ ሰንበት ት/ቤቶችን ዕድገት ለመምራት የማይመጥኑት ሓላፊዎች ተደጋጋሚ ክስ ቢኾንም÷ ማኅበሩ ከሁለት ዐሥርት የመንፈሳዊ ተጋድሎና የድል ዓመታት በኋላ የበርካታ ብፁዓን አባቶቹን ልባዊ ድጋፍና አለኝታነት በማትረፍ ይዞት ከተነሣው ዓላማ አኳያ የደረሰበትን ከፍተኛ ደረጃ የሚጠቁም መኾኑ ነው፡፡

ይኸውም የምልአተ ጉባኤው ውሳኔ ማኅበሩ የተማረውን ትውልድ ኦርቶዶክሳዊ መሠረትና ማንነት በማጠናከር ትምህርተ ወንጌልንና ስብከተ ወንጌልን በተለያዩ መንገዶች ማስፋፋቱ፣ በሞያዊ አበርክቶው በገዳማት፣ አድባራትና የአብነት ት/ቤቶች ዙሪያ በሚተገብራቸው ፕሮጀክቶቹ ተቋማቱ የዘመኑን ተግዳሮች እንዲሻገሩ መርዳቱ፣ በጥናትና ምርምር ማእከሉ ባሳያቸው የሥራ ፍሬዎቹና በያዛቸው ዕቅዶቹ ተስፋ ሰጪ እንቅስቃሴዎች ማድረጉ በመንበረ ፓትርያርኩ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ካሉት የአስተዳደር መዋቅሮች መካከል የራሱ ተልእኮዎችና ሓላፊነቶች ያሉት አንድ አካል የሚያደርገው መኾኑ ነው፡፡

ስጋቱ ግን ማኅበረ ቅዱሳን ይህን የመዋቅር ተጠሪነት ለውጥ የሚመጥን የአገልግሎት ስትራቴጂና የአገልግሎት ዝግጁነት አለው ወይ?” የሚል ነው ይህ ስጋት አዘል ጥያቄ በአራት ዓመት የስትራቴጂያዊ ዕቅድ ክንውን ግምገማና የቀጣይ ዓመት ስትራቴጂያዊ ዕቅድ ዝግጅት ሂደት ላይ እንደሚገኝ ያስታወቀው የወቅቱ የማኅበሩ አመራርና ከአገር ዓቀፍ እስከ ዓለም አቀፍ የሚገኙ በብዙ ሺሕ የሚቆጠሩ አባላቱ የቤት ሥራ ነው፡፡



ለማኅበረ ቅዱሳን 20 ዓመት አከባበር በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ስብከተ ወንጌል አዳራሽ በተካሄደው ጉባኤው ላይ የመድረክ እንግዳ ኾነው የቀረቡት የአትላንታ ጻድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ አስተዳዳሪ ቀሲስ ዕርገተ ቃል በሰው ባሕርያዊ የዕድሜ እርከኖች ምሳሌ ይህን ተናግረዋል - “ያለፉት 20 የአገልግሎት ዓመታት ማኅበረ ቅዱሳን በብላቴናነት የተፋጠነባቸው ነፋሳዊ ዘመናት ናቸው፤ መጪዎቹ 20 ዓመታት ግን ማኅበሩ በእሳት የሚፈንባቸው እሳታዊ ዘመናት በመኾናቸው ጠንክሮ መገኘት ይኖርበታል፡፡

በእሳታዊው ዘመን ወደ እሳታዊው ቤተ ክህነት - ቀልጦ መቅረት ወይም ነጥሮ በመውጣት የለውጥ አብነት መኾን!!

ተጨማሪ ዜናዎችን ይከታተሉ፤

ቸር ወሬ ያሰማን፤

አሜን፡፡
የተዋሕዶ ቤተሰቦች በመላው ዓለም

No comments:

Post a Comment