Thursday, May 10, 2012

የጠ/ቤተ ክህነቱ ሠራተኞች “የዳኛ ያለህ! ለቤተ ክርስቲያኒቱ ዳኝነት ይታይላት” የሚል ጽሑፍ ለቅዱስ ሲኖዶስ አባላት አሰራጩ


·  አቡነ ጳውሎስ ሃይማኖትን በመበረዝ እና በሕገ ቤተ ክርስቲያን ጥሰት መጠየቅ እና መወገድ ነበረባቸው::
·  ሊቃነ ጳጳሳቱ “ሰማዕታት፣ ነውረኞች፣ ዘገምተኞች እና ጥቅመኞች” በሚል በአራት ተከፍለዋል::
·  አቡነ ጳውሎስ የቅዱስ ሲኖዶስን ሕግ እና ውሳኔ እየሻሩ የቅዱስ ሲኖዶስን ጉባኤ መምራታቸው ሊያሳፍራቸው እንደሚገባ ተነግሯቸዋል::
·  አቡነ ጳውሎስ የመጨረሻውን የቤተ ክርስቲያን ሥልጣን ይዘው ሊቃውንቱን በጡረታ በማግለልና በመርገጥ ሃይማኖት እየበረዙ፣ አዳዲስ መዋቅር እየከፈቱ ሀብቷ በዱርዬ ባለሥልጣናት እንዲወድም እያደረጉ መኾኑ ተገልጧል፡፡ ሰሞኑን በጠቅ/ቤተ ክህነቱ የተፈጸመውን የጡረታና ዝውውር ውሳኔ ቅዱስ ሲኖዶስ እንዲያጤነው ሠራተኞቹ ጠይቀዋል፡፡
·  ከጥበቃ መደብ በቀጥታ ተነሥተው የመምሪያ ሓላፊ የኾኑና ሴቶችን በማነወር ሥራ የተጠመዱ ሓላፊዎች እንዳሉ ተጠቁሟል::
·  የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ኮሚሽነር እና የቦርድ አባላት ያለሞያቸው በግል ወዳጅነት ተሰባስበው ኮሚሽኑን “እየመጠመጡት እና እየገደሉት ነው”::
 
(ደጀ ሰላም፤ ግንቦት 2/2004 ዓ.ም፤ May 10/ 2012/ READ THIS ARTICLE IN PDF)፦ ማክሰኞ በጸሎት የተከፈተው የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መደበኛ ስብሰባ ትናንት ግንቦት 1 ቀን 2004 ዓ.ም እንደሚጀመር ተጠብቆ የነበረ ቢኾንም እንዳልተካሄደ ታውቋል፤ ምክንያቱ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በዓለ ልደት ለማክበር በየአጥቢያው መሰማራታቸውና ከዚያም መልስ ፓትርያርኩ ለመሰብሰብ እንደማይችሉ በመግለጻቸው ነው ተብሏል፡፡ ስብሰባው ዛሬ እንደሚጀመር ተስፋ እየተደረገ ባለበት ኹኔታ ከሚያዝያ 30 ቀን ጀምሮ በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሠራተኞች እንደተዘጋጀ የሚገልጽና ለብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ውስጥ ለውስጥ በመሰራጨት ላይ የሚገኝ ጽሑፍ ለደጀ ሰላም ደርሷል፡፡


የጽሑፉ ይዘት በዋናነት በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ዐምባገነናዊ አስተዳደር፣ ሙስና እና ኑፋቄ ተሳስረውና ተመጋግበው የሚያደርሱትን ጥፋት የሚዘረዝር በሓላፊነትም አብዛኞቹን ጳጳሳት ተጠያቂ ያደርጋል፡፡ በተለይም “በነውረኛና ክፉ ፍቅር ተጠምደው ቤተ ክርስቲያኒቱን እያጠፏት ነው” ባሏቸው ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ እና አቡነ ገሪማ ላይ ያተኩራል፤ መላውን ጳጳሳት ሲገልጻቸው፡- ለቤተ ክርስቲያናቸው ሲሉ ራሳቸውን አሳልፈው የሰጡና ሰማዕት የኾኑ፣ አንገት የሚያስደፋ ተግባር ያለባቸውና ቤተ ክርስቲያናቸውን መከላከል የማይፈልጉ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን ችግር መረዳት የተሳናቸው የዋሃንና ዘገምተኞች፣ በልዩ ልዩ ጥቅም የተያዙ ለራሳቸውና ለቤተሰባቸው ቢዝነስ የሚሠሩ በማለት በአራት ከፍሏቸዋል፡፡


ደጀ ሰላም የጽሑፉን ምንጭ ለማጣራት ባደረገችው ጥረት የጽሑፉ ዝግጅት በዋናነት ሰሞኑን በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ከተፈጸመው የዝውውር እና ጡረታ ውሳኔዎች ጋራ የተያያዘ ሲኾን ከጽሑፉ አዘጋጆች ጥቂት የማይባሉት በመምሪያ ሓላፊነት ደረጃ ያሉና የነበሩ እንደ ኾኑ ለማረጋገጥ ተችሏል፡፡ ለ30ው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ ጉባኤ ከቀረበው ሪፖርት ለመረዳት እንደሚቻለው ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ 18 መምሪያዎችና 403 ሠራተኞች ያሉት ሲኾን ከእኒህም ውስጥ 338 ቋሚ 65 ደግሞ የኮንትራት ሠራተኞች ናቸው፡፡


በቅርቡ በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ በሁለት ዙሮች በተላለፈው ውሳኔ በአጠቃላይ 26 ሠራተኞች በጡረታ እንዲገለሉ ተደርጓል፤ ከእኒህም ውስጥ በመቐለ፣ በሰላሌ - ፍቼ፣ በድሬዳዋ እና በኋላም በጠቅላይ ቤተ ክህነት የቤቶች አስመላሽ ኮሚቴ ሰብሳቢ እና በመጨረሻም የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን መጋቤ ካህናት በመኾን የካህናት አስተዳደር መምሪያ ሓላፊ የኾኑት መጋቤ ካህናት ኀይለ ሥላሴ ዘማርያም፣ የቁጥጥር አገልግሎት መምሪያ ሓላፊ የኾኑት በኵረ ትጉሃን ዓለም አታላይ የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ ምንጮቹ እንደሚናገሩት የቁጥጥር አገልግሎት መምሪያ ሓላፊው በኵረ ትጉሃን ዓለም አታላይ ዕድሜያቸው ለጡረታ አልደረሰም፤ ያለጊዜያቸው በጡረታ ሰይፍ የተቆረጡት አላግባብ የሚደረጉ ዕቃ ግዥዎችን፣ ሌሎች ብኩንነቶችንና ምዝበራዎችን በመቃወማቸው ነው፡፡

ሊቀ ማእምራን ኀ/ሥላሴ
የአቋቋም ሞያ ዐዋቂ፣ የወንበር መምህርና በየዐውደ ምሕረቱ ለአቡነ ጳውሎስ የሚዥጎደጎደውን የውዳሴ ዝናም በማስተባበር የሚታወቁት ሊቀ ማእምራን ኀይለ ሥላሴ ዘማርያም ይመሩት በነበረው የካህናት አስተዳደር መምሪያ በዋና ሓላፊነት የተተኩት በዋልድባ ገዳም ላይ የተነሡ አቤታቱታዎችን በሽሬ፣ በማይ ፀብሪ እና በጎንደር ከተማ በተደረጉ ስብሰባዎች ለማስተባበል ሲሟሟቱ በብዙኀን መገናኛ የታዩት ንቡረ እድ ተስፋይ ተወልደ ናቸው - ውለታ መኾኑ ነው?

በዝውውር ውሳኔው ውስጥ ለብዙዎች አነጋጋሪ የኾነው በፊት የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ የነበሩትና በኋላ የገዳማት አስተዳደር መምሪያ ዋና ሓላፊ የኾኑት ንቡረ እድ አባ ገብረ ማርያም ገብረ ሥላሴ የሰሜን ምዕራብ ትግራይ - ሽሬ እንዳሥላሴ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ በማድረግ ከአዲስ አበባ እንዲርቁ መደረጋቸው ነው፤ በምትካቸው በመንበረ ፓትርያሪክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም ሰባክያነ ወንጌል አንዱና ማዕርገ ምንኵስና የሌላቸው / ሰሎሞን ቶልቻ የገዳማት አስተዳደር መምሪያ ዋና ሓላፊ ኾነው ተሾመዋል፡፡ አሁን የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ኾነው እየሠሩ ያሉት ንቡረ እድ ኤልያስ ኣብርሃ በቅኝት ስም በየአጥቢያው በመዞር እያፈሱት በሚገኘው የምእመናን ገንዘብ አገልጋይ ካህናትን እያስለቀሱ ነው፤ በየረር ቅድስት ሥላሴ እና በሌሎች የተለያዩ ቦታዎች የአብያተ ክርስቲያን መሬቶችን በግል ስማቸው እስከ ማዛወር መድረሳቸውም እየተነገረባቸው ነው፡፡ ንቡረ እዱ እንዲህ የሚያደርጉት ብቻቸውን አይደለም፤ አዲስ አበባ የቅዱስ ፓትርያሪኩ ልዩ ሀገረ ስብከት ነው በሚል በወር እስከ ብር 10,000 ‹ደመወዝፈሰስ እንደሚያደርጉላቸው ተጠቁሟል፡፡የሕዝብ ግንኙነት መምሪያ ምክትል ሓላፊ የነበሩት፣ በአሰቦትና ዝቋላ ገዳማት ቃጠሎ የተዛባ መግለጫ ሲሰጡ የቆዩት ሊቀ ኅሩያን ዳዊት ለፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ ‹ባጓደሉት ታማኝነት› ሳቢያ ፓትርያርኩ “መጋዘን አስገባልኝ” ብርቱ አገልጋዮችን ወደሚያገሉበት መንፈሳዊ ፍርድ ቤት (በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት) አባል ኾነው ተዘዋውረዋል፤ በእርሳቸው ምትክ የዜና ቤተ ክርስቲያን ጋዜጣ ምክትል አዘጋጅ መ/ር ካህሳይ ገብረ እግዚአብሔር የሕዝብ ግንኙነት ምክትል ሓላፊነቱን ቦታ እንዲይዙ ተደርጓል፡፡ በአሁኑ ወቅት በሠራተኛው ከፍተኛ የሙስና ሐሜት እየተሰማባቸው የሚገኙት የሕዝብ ግንኙነት መምሪያው ዋና ሓላፊ እስክንድር ገብረ ክርስቶስ፣ የብቃት ጥያቄና በአሿሿማቸውም የአሁኑ ቅዱስ ሲኖዶስ አጀንዳ እንደሚኾኑ የሚጠበቁት ምክትል ዋና ሥራ አስኪያጁ አቶ ተስፋዬ ውብሸት ሌሎቹ የሠራተኛው ጽሑፍ ዒላማዎች ናቸው፡፡


የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ምክትል ሓላፊ የነበሩትና ሕገ ወጦቹ እነ በጋሻው ደሳለኝ በበጎ አድራጎት ስም በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሊያካሂዱት ያቀዱት ‹ጉባኤ› እንዲታገድ የተንቀሳቀሱት ቀሲስ ሳሙኤል እሸቱ ከቦታቸው ተነሥተው በስዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ ማሠልጠኛ ኮሌጅ አስተዳደር ሓላፊ ኾነው እንዲሠሩ ተዛውረዋል፡፡ በእርሳቸው ቦታ የሰበካ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያ ምክትል ሓላፊ ተተክተዋል፡፡


ጡረታውም ዝውውሩም ቅንነት የጎደለው፣ መጥቀሚያና መበቀያ መኾኑን የሚናገሩት የቤተ ክህነቱ ምንጮች ዕድሜያቸው ለጡረታ ቢደርስም ፓትርያርኩ ለጡረታ አስወጪው ኮሚቴ በሰጡት ቀጥተኛ ትእዛዝ “እነርሱ አይውጡብኝ” ያሏቸው እንደ እነ ሊቀ ካህናት ብርሃኑ ገብረ ዐማኑኤል (የትንሣኤ ማሳተሚያ ድርጅት ሥራ አስኪያጅ) እና ልዩ ጸሐፊያቸው አሰፋ ሥዩም በሥራቸው እንዲቀጥሉ ከተደረጉት መካከል እንደሚገኙበት ይናገራሉ፡፡


የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሠራተኞች በአቡነ ጳውሎስ ላይ ሊጣራ ይገባል ያሉትን የሃይማኖት ሕጸጽ በመጥቀስ በሃይማኖት በራዥነትም ከሰዋቸዋል፡፡ በ1988 ዓ.ም “የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እምነት፣ ሥርዐተ አምልኮና የውጭ ግንኙነት” በሚል በታተመውና በወቅቱ በግፍ ከሊቃውንት ጉባኤ ሰብሳቢነታቸው የታገዱት አለቃ አያሌው ታምሩ በከፍተኛ ደረጃ የተቃወሙትን መጽሐፍ ቀዳሚ እትም ላይ “ሁለት ባሕርይና ሦስት መለኰት” ተብሎ የወጣውን ከባድ ሕጸጽ በመጥቀስ አቡነ ጳውሎስ እንደ ቤተ ክርስቲያን ሕግ መከሰስ እና መወገድ ይገባቸው እንደነበር ገልጸዋል፡፡ ይህ ባለመኾኑ ፓትርያርኩ “እመቤታችን ጥንተ ሰብሶ አለባት” ከሚሉት አባ ሰረቀ ጋራ እየተባበሩ ስለኾነ ቅዱስ ሲኖዶስ ጉዳዩን ተመልክቶ ይወስንበት ዘንድ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሠራተኞች “የዳኛ ያለህ” ብለዋል - በጽሑፋቸው፡፡


የጥቅምት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ከአዲስ አበባ ሰንበት ት/ቤቶች በቀረበለት ማስረጃ መሠረት የአባ ሰረቀ የእምነት ሕጸጽ እንዲጣራ በሊቃነ ጳጳሳት የሚመራ ኮሚቴ ካቋቋመ በኋላ አባ ሰረቀ (Left Picture“እውነትና ንጋት” በሚል ርእስ ባሳተሙት መጽሐፍ መሰል “ጥራዝ” አቡነ ጳውሎስ እ.አ.አ በ1988 በአሜሪካ ፕሪንስተን ቴዎሎጂ ኮሌጅ “Filsata: The Feast of the Assumption of the Virgin Mary and the Mariological Tradition of the Ethiopian Othodox Tewahedo Church” በሚል ርእሰ ጉዳይ የሠሩትን የዶክትሬት ጽሑፍ (ዲዘርቴሽን) ጠቅሰዋል፡፡
አባ ሰረቀ በእርሳቸው ላይ ያሉትን ትኩረቶች ለማስቀየስ በመጽሐፍ መልክ ያወጡት ጥራዝ በቤተ ክህነቱ ሠራተኞች ፍና ተሣልቆ “SerekeLeaks” - ሰረቀሊክስ (ሐሳቡ ከዊኪሊክስ የተወሰደ ይመስላል) የሚል ስያሜ የተሰጠው ሲኾን ዋነኛ ይዘቱ በሥራ ሓላፊነታቸው ወቅት የተጻጻፏቸው እና በሥራ ሓላፊነታቸው አማካይነት ያገኟቸው ዶሴዎች ናቸው፤ ከሥራ ሥነ ምግባር አኳያ አባ ሰረቀ ለግል ፍላጎታቸው ላሰቡት የሕዝብ ግንኙነት ፋይዳ የማይውሉና መጠበቅ የሚገባቸው ነበሩ፡፡


የኾነው ኾኖ አቡነ ጳውሎስ በዲዘርቴሽኑ መግቢያ ላይ እንዳሰፈሩት በነገረ ማርያም ላይ በዓለም ደረጃ (Ecumenical dialogue regarding Saint Mary) የአስተምህሮ አንድነት ለማምጣት (In search of a unifying Mariology) በማሰብ በሠሩት ጥናት (Academic project) ንጽሐ ጠባይ ያላደፈባት፣ ምንም ምን ነውር ያልተገኘባት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከአዳም በዘር ቍራኛ የተላለፈው የውርስ ኀጢአት እንዳለባት መጻፋቸውን በዋቢነት አንሥተዋል፡፡

በአንዳንዶች አስተያየት ጥናቱ ለአካዳሚያዊ ዓላማ በአካዳሚያዊ ተቋም ውስጥ የተሠራ ነው፡፡ ይኹንና አቡነ ጳውሎስ ከኦርቶዶክሳዊ ሃይማኖት ቀናዒነት አኳያ በየጊዜው በሚያሳዩት የላላ አቋም እና ግዴለሽነት ብዙዎች ሕጸጹ ከአካዳሚያዊ ተቋምና ዓላማ አልፎ የእምነት አቋማቸው እንዳደረጉት ያሳያል ይላሉ፡፡ ለምሳሌ፡- የኦሪየንታል ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያንና የሮም ካቶሊክ ተወካዮች በጥር ወር መጀመሪያ ላይ በአዲስ አበባ ንግግር ሲያካሂዱ በነበረበት ሰሞን በተከበረው የጥምቀት በዓል አከባበር ላይ በጃንሜዳ ባሕረ ጥምቀት ባሰሙት ንግግር በ451 ዓ.ም በኬልቄዶን በተደረገው ጉባኤ መለካውያን የተወገዙበትንና እነ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ከእነርሱም በኋላ እንደ እነርሱ ብዙዎች ቅዱሳን ሰማዕትነት የተቀበሉበትን ወሳኝ ዶግማዊ ልዩነት “ለ1500 ዓመት የኖረ ጭቅጭቅ” ሲሉ ማቃለላቸውን ይጠቅሳሉ፡፡

በተለይም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በጸሎተ ቅዳሴ ወቅት እንደ ሥርዐቱ ጀምረው የማይጨርሱበት ኹኔታም ይታያል፤ ነገሩ ከእርግና እና ሕመም በላይ ነው እየታየ ያለው፡፡ የአዘቦቱን ትተን ለአብነት ያህል በዐቢይ ጾም ወቅት በሆሳዕና እና በትንሣኤ ሌሊት በተከናወነው ጸሎተ ቅዳሴ በፓትርያርኩ ተጀምሮ በአቡነ ገሪማ ያለቀበትና ሌሎችም የድፍረት መተላለፎች የታዩበት ኹኔታ ተስተውሏል፡፡ ጉዳዩ ዛሬ በሚጀምረው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በዋነኛ አጀንዳነት ሊቀርብ እንደሚችል ተጠቁሟል፡፡
                                                                                   
ቸር ወሬ ያሰማን፤
አሜን፡፡

ከዚህ በታች የቀረበው የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሠራተኞች ከትናንት በስቲያ ማክሰኞ አንሥቶ ለቅዱስ ሲኖዶስ አባላትያሠራጩት ጽሑፍ ሙሉ ቃል ነው፡፡










                                        
                                             ሚያዝያ 27 ቀን 2004 ዓ.ም
ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን
ቅዱስ ሲኖዶስ አባላት
አዲስ አበባ

ብፁዓን አባቶች ሆይ፤
ከእግዚአብሔር በተሰጣችኹ አደራ መሠረት በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ ችግር እንዳይደርስ ልትከላከሉላትና ልትጠብቋት ግዴታ እንዳለባችኹ እኛ ክርስቲያኖች ሳንኾን ማንኛውም ኢትዮጵያዊ የሚያውቀው ጉዳይ ነው፡፡
እናንተ ግን፣ እናንተ ግን፣ እናንተ ግን!
ለመኾኑ በአሁኑ ጊዜ ቤተ ክርስቲያኒቱ የት ነው ያለችው የሚል ጥያቄ ቢነሣ መልሳችኹ ምን ይኾን?
. የት እንዳለች አናውቅም ብትሉ ሥራችኹ ምን ኾነና የሚል ጥያቄ አለ፡፡
. የት እንዳለች እናውቃለን ብትሉ ችግሯን እንዴት ፈታችኹት የሚል ጥያቄ አለ፡፡
. ብናውቅም አያገባንም ብትሉ ማንን ነው የሚያገባው የሚል ጥያቄ አለ፡፡
. ችግር የለም ብላችኹ ብትክዱ እውነቱን እውነት ሐሰቱን ሐሰት በሉ የሚለውን የእግዚአብሔር ሕግ መጣስ ይኾንባችኋል፡፡

ዓለም ግን ቤተ ክርስቲያኒቱ የት እንዳለች ከነችግሯ ያውቃታል፤ እናንተንም ያውቃችኋል፤ በበኩላችንም እንዴት እንደምታውቁት ከአሁን በፊት የገለጽንላችኹ ቢኾንም እንደገና ብናስታውሳችኹ አይከፋም፡፡ ይኸውም፤
1.              ከመካከላችኹ የሚያሳፍርና አንገት የሚያስደፋ ተግባር ስለአለባቸው በልበ ሙሉነት አፋቸውን ከፍተው ስለ ቤተ ክርስቲያናቸው ጉዳይ መናገር የማይችሉ የተወሰኑ ጳጳሳት መኖራቸው በትክክል ይታወቃል፡፡ እነዚህ ሰዎች ቤተ ክርስቲያን ስትቃጠል ቢያዩና የሚያቃጥሉትም አቡነ ጳውሎስ ከኾኑ መልካም ነው እያሉ ከሚያጨበጭቡ በስተቀር መከላከል አይፈልጉም፤ ስማቸውም እግዚአብሔር በፈቀደ ጊዜ ይጠቀሳል፤ ከነተግባራቸውም ይተረኩ ይኾናል፡፡
2.             መብላታቸውንና መተኛታቸውን እንጅ በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ ችግር ይኑር አይኑር በአጠቃላይ በአሁኑ ጊዜ ቤተ ክርስቲያኒቱ የት እንዳለች የማያውቁ የዋሃን አባቶች እንዳሉ የሚካድ ነገር አይኾንም፡፡ እነዚህ የዋሃኑ አባቶች ስለ ቤተ ክርስቲያን ጉዳይ የጦፈ ክርክር ቢነሣ የክርክሩን ሂደት አለማወቃቸው ብቻ ሳይኾን አጀንዳው ምን እንደ ኾነ የመገንዘብ አቅም የሌላቸው ናቸው፡፡ የሚያውቁት ነገር ቢኖር አባ ገሪማ እጃቸውን ሲያወጡና ሲያወርዱ እየተከታተሉ እጅ ማውጣትና ማውረድ ብቻ ነው፤ ማለትም የአባ ገሪማ እጅ መውጣት መውረዱን አጥብቀው ከመከታተል በቀር ከዘገምተኞች የሚሻሉበትን መመዘኛ በጭራሽ አላገኘንላቸውም፡፡ በመኾኑም የተደላደለ አእምሮ ያላቸው ሰዎች ሊቀመጡበት የሚገባው ወንበር ላይ እነዚህ ደመ ነፍሶች ተቀመጡበትና ቤተ ክርስቲያናችን ተጎዳች፡፡
3.             በልዩ ልዩ ጥቅም የተያዙ አባቶችም አሉ፡፡ እነዚህም ለራሳቸው እና ለቤተሰባቸው ቢዝነስ መሥራት እንጅ ስለ ቤተ ክርስቲያን ጉዳይ ቢያውቁም ምናቸውም አይደለም፡፡ በተለይም የተጠቃሚዎች መሪና አርኣያ የኾኑት አባ ገሪማ እንደ ማንኛውም ጳጳስ ሀገረ ስብከታቸው ላይ የማይገኙ ከመኾናቸውም በላይ መንበረ ፓትርያርክ ውስጥ ቁጭ ብለው በነጻ እንጀራ ይበላሉ፡፡ ጮማውና ውስኪው ሳይቀር ከአቡነ ጳውሎስ ጋራ መንበሻበሽና ሽርሽር ሲያስፈልግም በቤተ ክርስቲያናችን ገንዘብ በሀገር ውስጥም ኾነ በውጭ ሀገር እንደ ፈለጉ መዝናናትና መንከራተት ነው፡፡ ብቻ እነዚህ ሰዎች ምን ጉድ እንዳላቸው አይታወቅም እንጅ በጭራሽ ተለያይተው ማደር አይፈልጉም፡፡ “የቤተ ክርስቲያንን ሀብት አታባክኑ፤ የአግዚአብሔርን ሕግ አትጣሱ” ብሎ የሚቆጣ ሽማግሌም ጠፋ፤ ምን ይሻላል? በእውነቱ እነዚህ በልብስና በስም አባቶችን የሚመስሉ ሁለቱ ሰዎች ነውረኛና ክፉ በኾነ ፍቅር ተጠምደው ቤተ ክርስቲያኒቱን አጠፉ፡፡ በዚህ ክፉ ፍቅር የተነሣም አባ ጳውሎስ ሰው እንዲገደል መመሪያ ቢሰጡ አባ ገሪማ ሰውን ከመግደል ወደ ኋላ እንደማይሉ ሰው ሁሉ ሊያውቃቸውና ሊጠነቀቅባቸው ይገባል፡፡ እኛ ግን የቤተ ክርስቲያን አምላክ ይፍረድ፤ ታሪክም ይውቀስ፤ በሕዝብ ዘንድም መጋለጥ ይምጣ ከማለት በቀር ለጊዜው ዝም ብለናል፡፡
4.             በአንጻሩ ደግሞ ለቤተ ክርስቲያናችኹ ስትሉ ራሳችኹን አሳልፋችኹ የሰጣችኹ፣ እስከ መደብደብ ደርሳችኹ ሰማዕትነትን የተቀበላችኹ እውነተኞች አባቶች መኖራችኹን እናውቃለን፡፡

ብፁዓን አባቶች ሆይ፤
ቅዱስ ሲኖዶስ ሲባል ስብሰባውም ቅዱስ ነው፤ ውሳኔውም የሚደነግገው ሕግም ቅዱስ ነው፤ ቀኖና ነው ተብሎ በክርስቲያኖች ዘንድ ይታመናል፡፡ አቡነ ጳውሎስ ግን፡-
1.              የቅዱስ ሲኖዶስን ውሳኔና ሕግ እየሻሩ የቅዱስ ሲኖዶስን ጉባኤ እመራለኹ ሲሉ አለማፈራቸው ድንቅ ነገር ነው፡፡
2.             የቅዱስ ሲኖዶስ አባላትን ደብድበውና አስደብድበው ሽፍትነታቸው በግልጽ እየታወቀ የደበደቧቸውን አባቶች በጉባኤያቸው ላይ ቁጭ ብዬ ልምራቸው ብለው ሲያስቡ ምናልባት ‹እያንዳንዱን ገርፌዋለኹ፤ ዋጋውን ሰጥቼዋለኹ፤ አሁንም በላዩ ላይ ቁጭ ብዬ አፍህን ዝጋ እያልኹ አገዛዜን አሳየዋለኹ› የሚል ሐሳብ ይዘው ተነሥተው ከኾነ ከሃይማኖት አባቶች ሳይኾን ከማንኛውም ጉልበተኛ ወይም ሽፍታ የሚጠበቅ ነው ብለን እናልፈዋለን፡፡
3.             ጳጳሳትን መሾም፣ መሻርና ማገድ የቅዱስ ሲኖዶስ ሥልጣን እንደ ኾነ በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ 19/4፣ 22(1-3)፣ እና 23 የተደነገገው ሲታይ የሁሉንም ጳጳሳት መብት የሚመለከት ነው የሚመስለው፡፡ አቡነ ጳውሎስ ግን ሊያጠቋቸውና ሊበቀሏቸው የፈለጓቸውን ሊቀ ጳጳስ በየጊዜው ሲያግዷቸውና ሞራላቸውን እየነኩ ግፍ ሲፈጽሙባቸው አባቶች እያያችኹና እየሰማችኹ ዝምታ መምረጣችኹ አጠያያቂ እየኾነ ነው፡፡ ምናልባት እርስ በርሳችኹ እንዴት ነው? እናንተም ትመቀኛኛላችኹ እንዴ?
4.             እናንተ ባወጣችኹት ሕግ “ጳጳስ ጡረታ አይወጣም” ስለሚባል ምንም መስሎ አይታችኹ እንደ ኾነ እንጅ የመጨረሻውን ጥያቄያችንን እንድትመለከቱልን እንጠይቃለን፡፡ ይኸውም ከእናንተ መካከል ብዙዎቻችኹ እንደምታውቁት እኛ ዕውቀትን ለማሰባሰብ የዕድሜያችንን ግማሽ አባክነን ወደ ሥራ ዓለም ከገባን በኋላ ገና ሥራውን ሳንጠግበው ምክንያት እየተፈለገ በጡረታ ስም እየተባረርን ነው፡፡ አቡነ ጳውሎስ በአትሮንስ ሥር ያላደጉ ዱርዬዎቻቸውን እየፈለጉ በኮሚቴ አደራጅተው የጉባኤ ቤት ተማሪ ነበረ የሚባለውን ሰው ሁሉ እያሳደዱ፣ ብፁዕ አቡነ ፊልጶስንም እያስፈራሯቸው ስለሚፈርሙ ሊቃውንቱ ግማሾቹ በጡረታ እየተገለሉ፣ ግማሾቹ ዝቅ ብለው እንዲሠሩ እየተደረገ ነው፡፡ ዱርዬዎችና ጡረተኛ ወታደሮች ደግሞ የቤተ ክርስቲያኒቱን ቁልፍ ቦታና ሥልጣን የተባለውን ሁሉ በቁጥጥር ሥር አውለው በቤተ ክርስቲያናችን ላይ እየተጫወቱባት ነው፡፡
ለምሳሌ ያህል፡- ከጥበቃ መደብ ተነሥተው በመምሪየ ደረጃ የመላዋ ኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሠራተኞች ሓላፊ የኾኑት የዐሥር አለቃ ሁንዴሳ ጎሴ እና ከመዝገብ ቤት ተነሥተው የአስተዳደር መምሪያ ሓላፊ የኾኑት [ሊቀ መዝገብ] ዮሐንስ ኤልያስ መሰሎቻቸውን ዱርዬዎችና ሴቶች በማሰባሰብ የሊቃውንት መናኸርያ የነበረው ቤተ ክህነቱ ጥላውን ተገፎ “የሴተኛ አዳሪ ሰፈር” ከመምሰሉም በላይ መጠነ ሰፊ በኾነ መንገድ ሊቃውንቱ እየተገለሉና እየተረገጡ ነው፡፡ አባቶቻችን እናንተም ዝም አላችኹ፡፡ ለማን አቤት እንደምንልም አናውቅም፡፡ ዋስትና የሌላቸው ዜጎች ኾነናል፡፡ ምን ይሻለናል? ቤተ ክርስቲያናችንን እንርገማት እንዴ? አይኾንም፤ በውስጧ ቆመንና ተንበርክከን ሰዓሊ ለነ ቅድስት እያልን እመቤታችንን የተማፀንባትን ቤተ ክርስቲያናችንን አንረግምም፤ እናንተ ግን እግዚአብሔር ይይላችኹ እንላለን፡፡

ብፁዓን አባቶች ሆይ፤
ድምፃችን ቢሰማም ባይሰማም አቡነ ጳውሎስ ብፁዕ ወቅዱስ የሚል ማዕርግ እና የመጨረሻውን የቤተ ክርስቲያናችንን ሥልጣን ይዘው ሃይማኖታችንን እየበረዙና የቤተ ክርስቲያናችንን ሕግ እየጣሱ መኾናቸውን አሁንም እንጠቁማለን፡፡
1.              ቀደም ሲል በ1988 ዓ.ም ሁለት ባሕርይና ሦስት መለኰት ብለው መጽሐፍ በአስጻፉ ጊዜ እንደ ቤተ ክርስቲያናችን ሕግ ሳይከሰሱና ሳይወገዱ በመቅረታቸው በአሁኑ ጊዜም እመቤታችን “ጥንተ አብሶ አለባት” እያሉና የዚህ ዐይነት አቋም ካላቸው ጋራ እየተባበሩ ስለኾነ የዳኛ ያለህ እንላለን፡፡
2.             የጠቅላይ ቤተ ክህነት ምክትል ሥራ አስኪያጅ መመረጥ ያለበት በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ እንደ ኾነ በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ አንቀጽ 7(15)(ሐ) ተደንግጓል፡፡ አቡነ ጳውሎስ ግን ይህን ሕግ በመጣስ የትልቁን ድርጅት የኪራይ ቤቶችን ዋና ሥራ አስኪያጅነትና የጠቅላይ ቤተ ክህነቱን ምክትል ሥራ አስኪያጅነት ሁለቱንም ሥልጣናት አውዳሚ ለኾነ አንድ ጎረምሳ ሰጥተው የቤተ ክርስቲያኒቱን ሀብት እያባከኑ ነው፤ ሕጉንም እየጣሱ ነው፡፡
3.             የቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅር በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ አንቀጽ 28(4)(ከሀ-ሐ) በግልጽ በሚነበብ ኹኔታ ተደንግጎ እያለ አቡነ ጳውሎስ አዳዲስ መዋቅር እየከፈቱ ለዱርዬዎቻቸው ሥልጣንን እያደሉ ነው፡፡ ለምሳሌ፡-
ሀ. በቤተ ክህነቱ አንድ ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ
ለ. በልዩ ጽ/ቤታቸው አንድ የሕዝብ ግንኙነት መምሪያ
ሐ. በልዩ ጽ/ቤታቸው አንድ የመሐንዲስ መምሪያ
መ. በቤተ ክህነት አንድ የፕሮጀክት መምሪያ ከፍተው ለእኒህ ሁሉ መምሪያዎች ባለሥልጣናትን እስከነምክትላቸው መድበው የቤተ ክርስቲያኒቱን ሀብት እያባከኑ ነው፡፡
ሠ. ከዚህ በላይ እንደተጠቀሰው በተጨማሪም ቅዱስ ሲኖዶስ ሕግ መሠረት በጠቅላይ ቤተ ክህነት የተዋቀረና የኖረ የውጭ ጉዳይ መምሪያ እያለ አቡነ ጳውሎስ በልዩ ጽ/ቤታቸው ሌላ የውጭ ጉዳይ መምሪያ ከፍተዋል፤ ሕጉም ሙሉ በሙሉ እየተጣሰ ነው፡፡ ከዚህ በላይ አቡነ ጳውሎስ ተራ የኾነ ብልሃት ይዘዋል፡፡ ይኸውም ተሿሚዎች ቢገባቸውም ባይገባቸውም አዳዲስ ሠራተኞችንና አዳዲስ ጳጳሳትን እየሾሙ በባለውለታነት በአዲሶቹ ሹመኞች እየተደገፉ ብዙ የከፉ ተግባራትን መሥራት ስለሚፈልጉ ነው፡፡
4.             የልማት ኮሚሽን ኮሚሽነርና የቦርድ አባላቱ የሚመረጡት በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ እንደ ኾነ በሕገ ቤተ ክርስቲያኗ አንቀጽ 7(15)(መ) እና (ረ) መደንገጉ እየታወቀ ዶ/ር አግደው በግል ወዳጅነት ያለስጦታቸው ገብተው ኮሚሽኑን እየገደሉት ናቸው፡፡ ከቦርዱ አባላት መካከል በተለይ እነ (ዶ/ር) ቆስጠንጢኖስ የሚባሉት ለዘመናት ተተክለው የቤተ ክርስቲያኒቱን ኮሚሽን እየመጠመጡት ነው፡፡

ስለዚህ እባካችኹ አባቶች ለቤተ ክርስቲያኒቱ ዳኝነት እዩላት በማለት በእግዚአብሔር ስም እንማፀናለን፡፡
                                                    የአባቶቻችን በረከት አይለየን
                                                 የቤተ ክህነት ሠራተኞች

የተዋሕዶ ቤተሰቦች በመላው ዓለም

No comments:

Post a Comment