Friday, May 11, 2012

የቅ/ሲኖዶስ መደበኛ ስብሰባ የመጀመሪያ ቀን ውሎ

  • ሰባት አባላት ያሉት የአጀንዳ አርቃቂ ኮሚቴ ተመርጧል:: 
  • ቋሚ ሲኖዶስ ባለ 15 ነጥብ ሐሳቦችን ለአጀንዳ አርቃቂው ኮሚቴ አቅርቧል:: 
  • የገዳማት፣ የዕርቀ ሰላም ንግግር፣ የሃይማኖት ሕጸጽ ስላለባቸው ሰዎች፣ ስለ ልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን፣
  • ስለ ማደራጃ መምሪያና ማኅበረ ቅዱሳን የተመለከቱ ጉዳዮች ይገኙበታል ተብሏል::
  •   ፓትርያርኩ የጳጳሳት ሹመትንና ሕገ ቤተ ክርስቲያንን ማሻሻልን በድጋሚ አጀንዳነት አስይዘዋል::
ሙሉ ዘገባውን የወሰድነው ከደጀ ሰላም ብሎግ ነው::
 የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ስብሰባ ዛሬ፣ ግንቦት 2 ቀን 2004 ዓ.ም ጠዋት በጽርሐ መንበረ ፓትርያርክ ተጀምሯል፡፡ በስብሰባው በሰሜን አሜሪካ ከቀሩት የጉጂ ሊበን ቦረና ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ኤዎስጣቴዎስ፣ የኒውዮርክና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዘካርያስ፣ የደቡብ አፍሪካ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ያዕቆብ እንዲሁም ሌሎች ሁለት ጳጳሳት በእርግና ምክንያት ካለመገኘታቸው በቀር የመደበኛው ስብሰባ ምልአተ ጉባኤ ተሟልቶ ቅዱስ ሲኖዶሱ ሥራውን ቀጥሏል፡፡



በስብሰባው መግቢያ ፓትርያርኩ ሰፊ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉ ሲኾን የንግግራቸው ትኩረት ከወጣቶች ጉዳይ እስከ ታላቁ ሕዳሴ ግድብ እና የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ የሚነካካ እንደነበር የስብሰባው ምንጮች አመልክተዋል፡፡ ከመክፈቻው ንግግር በኋላ የአጀንዳ አርቃቂ ኮሚቴ አባላትን ለመምረጥ የተደረገው ጥረት ያልተለመደ ገጽታ አስተናግዷል፡፡ ይኸውም የምልአተ ጉባኤው ርእሰ መንበር ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በአጀንዳ አርቃቂ ኮሚቴ ውስጥ “እኔም መግባት አለብኝ” በሚል አቋም መያዛቸው ነው፡፡ ከእርሳቸው ቀደም ብሎ በኮሚቴው ውስጥ ለመካተት በአቡነ ገሪማ፣ አቡነ ሳዊሮስና አቡነ ፋኑኤል መካከል የታየው አንዳቸው ከሌላቸው ጋራ ብቻ የመደጋገፍ ኹኔታ ያሳሰባቸው አባቶች “በአጀንዳ አርቃቂ ኮሚቴ ውስጥ መግባት አለብኝ” የሚለውን የፓትርያርኩን  አቋም በጥንቃቄ ተከላክለዋል፡፡
ፓትርያርኩ ርእሰ መንበር በመኾናቸው ይህን አቋም መያዝ እንደማይገባቸው ቢነገራቸውም ሰበብ ያደረጉት እርሳቸው በሰብሳቢነት በሚመሩት ቋሚ ሲኖዶስ ቀደም ብሎ የራሱን አጀንዳ አዘጋጅቶ አለመቅረቡን ነው፤ በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ አንቀጽ 12(4) መሠረት ከቋሚ ሲኖዶሱ ሥልጣንና ተግባር አንዱ ቅዱስ ሲኖዶስ በየጊዜው በሚያደርገው ጉባኤ የሚነጋገርባቸውን አጀንዳዎች ማዘጋጀት ነበር፡፡ ነገሩ በአጀንዳዎች ላይ ተጽዕኖ ለማሳደር ይኹነኝ ተብሎ እንደተደረገ ቤቱ የተረዳ ቢሆንም ረዘም ካለ ሙግት በኋላ የቋሚ ሲኖዶሱ አባላት እንደ አካል (ፓትርያርኩን ጨምሮ ጸሐፊውን ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤልንና ዋና ሥራ አስኪያጁን ብፁዕ አቡነ ፊልጶስን ጨምሮ ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ፣ ብፁዕ አቡነ ኢሳይያስ፣ ብፁዕ አቡነ ኤልያስ፣ ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ) የአጀንዳ አርቃቂ ኮሚቴው አባል እንዲኾኑ ተደርገዋል፡፡ በምልአተ ጉባኤው የተመረጡ የአርቃቂ ኮሚቴው አባላት አምስት ሲኾኑ እነርሱም ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፣ ብፁዕ አቡነ ዳንኤል፣ ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ፣ ብፁዕ አቡነ ገሪማ እና ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ናቸው፡፡
የቋሚ ሲኖዶሱ አባላትና በእነርሱ ላይ የተጨመሩት አምስቱ አባቶች የአጀንዳ ረቂቅ ለምልአተ ጉባኤ እንዲያቀርቡ ጊዜ ተሰጥቷቸው የተጠበቁ ቢኾንም የታሰበው ሊኾን እንዳልቻለ ነው ምንጮቹ የሚናገሩት፤ የዚህም ምክንያቱ ፓትርያርኩ ስብሰባውን ካልመራኹ በማለታቸውና ብዙኀኑም ይህን እንደማይችሉ በመቃወማቸው የተነሣ በተፈጠረ መካረር ከስምምነት ሳይደርስ በመበተኑ ነው፡፡
እስከ ምሳ ሰዓት በነበረው ውሎ በዚህ መልክ የቆየው ምልአተ ጉባኤው ከምሳ ሰዓት በኋላ ቋሚ ሲኖዶሱ ጊዜ ተሰጥቶት የአጀንዳ ረቂቆችን እንዲያቀርብ ይተወዋል፡፡ ቀደም ሲል በመረጣቸው አምስት የአርቃቂ ኮሚቴ አባላት ላይ ተጨማሪ ሁለት አባቶችን (ብፁዕ አቡነ ማቲያስንና ብፁዕ አቡነ ማቴዎስን) አክሎ እነርሱ በቋሚ ሲኖዶሱ የሚሰጧቸውንና የራሳቸውን ይዘው ሲያበቁ ለምልአተ ጉባኤው እንዲኾን አጣርተው በነገው ዕለት ለምልአተ ጉባኤው የመነጋገርያ አጀንዳ ረቂቅ እንዲያቀርቡ በመወሰን የዕለቱን ውሎውን አጠናቋል፡፡
ማምሻውን በደረሰን መረጃ መሠረት በፓትርያርኩ ሰብሳቢነት የሚመራው ቋሚ ሲኖዶሱ ባለ 15 ነጥብ የአጀንዳ ሐሳቦችን ሰባት አባላት ላሉት የአጀንዳ አርቃቂ ኮሚቴ አባላት አቅርቧል፤ እነርሱም፡- የተጨማሪ ኤጲስ ቆጶሳት ሹመት፣ ሕገ ቤተ ክርስቲያኑን የማሻሻል፣ ስለ ዕርቀ ሰላም ንግግር፣ ስለ ማኅበራት፣ የሃይማኖት ሕጸጽ ስላለባቸው ሰዎች፣ ስለ ሰንበት ት/ቤቶች ማ/መምሪያ እና ማኅበረ ቅዱሳን፣ ስለ ቅዱስ ላሊበላ ደብር እና ሰባት ወይራ ሆቴል ጉዳይ እንዲሁም በላሊበላ ስለተፈጠረው ችግር፣ ስለ ልማት እና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን፣ ስለ ሕፃናትና ቤተሰብ ጉዳይ ድርጅት፣ ስለ ቤቶችና ሕንፃዎች አስተዳደር፣ ስለ ገዳማት አስተዳደር እና አብነት ት/ቤቶች፣ ስለ ስብከተ ወንጌል፣ ስለ ቃለ ዐዋዲው ማሻሻያ ሐሳቦች እንዲሁም ስለ ሐዋሳ ሀ/ስብከት ችግር የሚሉ እንደ ኾኑ ተጠቁሟል፡፡
በነገው ዕለት ጠዋት ከእኒህ ሐሳቦች መካከል ተመርጠውና በአጀንዳ አርቃቂው ኮሚቴ ተጨምረው ወይም ተጠናክረው ለምልአተ ጉባኤው የሚቀርቡ ሌሎች አጀንዳዎች በቤቱ ጸድቀው ውይይቱ እንደሚቀጥል ይጠበቃል፡፡
የዋልድባና ሌሎችም ገዳማት ጉዳይ የሚታይበት አጀንዳ ረቂቅ በቋሚ ሲኖዶሱ መያዙ ተገቢ ነው፤ በሌላ በኩል ግን ከሰሜን አሜሪካ የዋሽንግተን ዲሲና አካባቢው ሀገረ ስብከት በአቡነ ፋኑኤል ላይ የቀረቡ አቤቱታዎች፣ በጥቅምቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ታይተው አፈጻጸማቸውና የውሳኔ ሐሳቦቻቸው ቀርበው ሊከናወኑ የሚገባቸው ጉዳዮች የመሳሰሉት ሊዘነጉ እንደማይገባ የጉባኤው ተከታታዮች ያሳስባሉ፡፡
ቸር ወሬ ያሰማን፤
አሜን፡፡
የተዋሕዶ ቤተሰቦች በመላው ዓለም

No comments:

Post a Comment