Tuesday, April 3, 2012

በዋልድባ ጉዳይ ብአዴን/ኢሕአዴግ የጠራው ስብሰባ ዘገባ (ክፍል ሁለት)


  • በዋልድባ ጉዳይ የጎንደር ወጣቶች ሊቀ ጳጳሱን አነጋገሩ::

  • በሊቀ ጳጳሱ አቋም ላይ ለመወያየት ቀጠሮ ተይዟል::
  • በዋልድባ ወጣቶች ወደ ፕሮጀክቱ አካባቢ እንዳይደርሱ በፖሊስ ታግደዋል::
  • የማኅበረ ቅዱሳን አጥኚ ቡድን ነገ ወደ ዋልድባ ያመራል::

 (ደጀ ሰላም፤ መጋቢት 24/2004 ዓ.ም፤ April 2/2012/ READ THIS ARTICLE IN PDF)፦ በሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት የጎንደር ከተማ ሰንበት ት/ቤቶች ጥምረትና የጥምቀት በዓል አከባበር ወጣቶች ማኅበራት ጥምረት ኮሚቴዎች፣ በማኅበረ ቅዱሳን የስድስቱ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ግቢ ጉባኤያት ሥራ አስፈጻሚዎች እንዲሁም የጎንደር ማእከል ሥራ አስፈጻሚ ጉባኤ አባላት ከሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ ጋራ መነጋገራቸው ተሰማ፡፡

ወጣቶቹ ከሊቀ ጳጳሱ ጋራ የተነጋገሩት የወልቃይት ስኳር ልማት ፕሮጀክት በዋልድባ ገዳም ህልውናና ክብር ላይ የጋረጠውን አደጋ በተመለከተ የከተማው ከንቲባ ጽ/ቤት በጎንደር ዩኒቨርስቲ ሳይንስ ዓምባ አዳራሽ ጠርቶት በነበረው ስብሰባ ላይ ብፁዕነታቸው ቀድሞ ከሚታወቀው አቋማቸው የተለየና ወጣቶቹን ያሳዘነ ንግግር በመናገራቸው ነው፡፡
መጋቢት 21 ቀን ከረፋድ እስከ ቀትር በሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት በተካሄደው ንግግር ሊቀ ጳጳሱ ምንም የአቋም ለውጥ እንደማያደርጉ ከመግለጻቸውም በላይ የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ወጣቶቹን “በሞተ ጉዳይ ነው የመጣችኹ” ሲሏቸው ተደምጠዋል፡፡ “ከሞተም እናነሣዋለን፤ ቤተ ክርስቲያን አትሞትምና” በማለት በደጅ ጥናት ወደ ውስጥ የገቡት የወጣቶቹ ተወካዮችም በብፁዕነታቸው ንግግር ከፍተኛ ቅሬታ የተሰማውን ወጣት ሊቀ ጳጳሱ በጉባኤ ተገኝተው የሚያረጋጉበት ሁኔታ እንዲመቻች መስማማታቸው ተገልጧል፡፡
መጋቢት 19 ቀን 2004 ዓ.ም አቶ ኣባይ ፀዬና አቶ አያሌው ጎበዜ ከዞኑና ሀገረ ስብከቱ ሓላፊዎች ጋራ በተገኙበት በፕሮጀክቱ አሉታዊ ተፅዕኖዎች ዙሪያ ተደርጎ በነበረው ስብሰባ ሊቀ ጳጳሱ ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ ፕሮጀክቱ በገዳሙ ህልውናና ክብር ላይ ጎጂ ተጽዕኖ እንዳለው ከቤቱ ሲቀርቡ የነበሩ ተቃውሞዎችን በማጣጣል “የላክናቸውን እንቀበላቸው እንጂ” በሚል ወደ ዋልድባ ስለ ሄደው ቡድን የቀረበውን ዘገባ ተሰብሳቢዎቹ በእምነት እንዲቀበሉ አሳስበው ነበር፡፡ በተወያዮች የተነሡ ተቃውሞዎችን የሌሎችን ጩኸት መልሰው ከሚጮኹ አካላት ጋራ በማመሳሰል “ዝም ብላችኹ የምታስተጋቡ፤ ዋልድባን የመሠረተው ክርስቶስ ነው፤ እነዚያን አራቱን [በግድብ ሥራው የሚፈርሱትን አራት አብያተ ክርስቲያን] ግን የወልቃይት ሕዝብ ነው የሰጣቸው” ሲሉ ተናጋሪዎቹን መውቀሳቸው ተገልጧል፡፡
በዕለቱ ስብሰባ መጠናቀቂያ ውይይቱን እንዲዘጉ በአቶ አያሌው የተጋበዙት ብፁዕነታቸው “ከዋልድባና ከገነት ማን ይበልጣል?” በሚል ጥያቄ ነበር ንግግራቸውን የጀመሩት፡፡ ከጥያቄያቸው በኋላ ለቤቱ ባሰሙት በጽሑፍ የተዘጋጀ ንባብ÷ እግዚአብሔር ገነትን አስቀድሞ ካዘጋጀ በኋላ አዳምንና ሔዋንን እንደፈጠረ አስረድተዋል፤ ወዲያውም ገነትን አራት አፍላጋት እንደሚያጠጧት በመጥቀስ ከዋልድባ ገነት እንደምትበልጥ ከዘረዘሩ በኋላ “ወደ ዋልድባስ ውኃ ቢፈስ ችግሩ ምንድን ነው?” ብለዋል፡፡ አያይዘውም “መነኰሳቱ ቋርፍ የሚያዘጋጁበት ስኳር የላቸውም እያላችኹ ከከተማ እየገዛችኹ ትወስዱ የለም ወይ? አምና እንኳ አራት ኩንታል ስኳር ሰዳችኹ የለ? ታዲያ ይኸው ስኳር እዚያው ቢመረት ችግሩ ምንድን ነው? ለምን ታምፃላችኹ?” በማለት ለገዳሙ ህልውና እና ክብር ተቆርቋሪ የሆኑ ምእመናንን አንገት አስደፍተዋል፡፡ አንድ የዐይን እማኝ እንደተናገሩት “ሊቀ ጳጳሱ እንዲህ እያሳዘኑን በነበረበት ሰዓት አዳራሹን ትቶ ለመውጣት ከቋፍ የደረሰው ተሰብሳቢ ቁጥር ጥቂት አልነበረም” ብሏል፡፡
ሌሎች የዜናው ምንጮች እንዳረጋገጡት፣ ቀደም ሲል ባቀረብነው ዜና ዘገባ እንዳስነበብነው ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ የገዳሙ ማኅበረ መነኰሳት ምልዓተ ጉባኤ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ የላኩት ጥያቄ በተሰማበት ሰሞን በከተማው አጥቢያ አብያተ ክርስቲያን ጸሎተ ምሕላ እንዲያዝ ደብዳቤ ጽፈው ነበር፡፡ ቤተ ክርስቲያን ማንም ሊገዳደረው በማይችል ሉዓላዊና ክህነታዊ ሥልጣኗ ያስተላለፈችውን ይህን የዐዋጅ ትእዛዝ እንደ ስጋት የተመለከቱ የዞን አስተዳደር ጽ/ቤት ሓላፊዎች መጋቢት አራት ቀን 2004 ዓ.ም ሊቀ ጳጳሱን፣ ሥራ አስኪያጃቸውንና ሌሎች የሀገረ ስብከቱን ክፍሎች ሓላፊዎች ስብሰባ ይጠራሉ፡፡
በስብሰባው ላይ በአንዳንድ ሓላፊዎች ዘንድ የጸሎተ ምሕላው ትእዛዝ የተላለፈበት ደብዳቤ እንደማስረጃ ተይዞ ጸሎተ ምሕላው የዐመፅ ቅስቅሳ መሣርያ ተደርጎ ቀርቧል፡፡ ጸሎተ ምሕላ ለማወጅ ማንም ሊከለክላቸው እንደማይችል ለሓላፊዎቹ ግልጽ ያደረጉት ብፁዕነታቸው እንዲያውም የፕሮጀክቱ ቦታ ድረስ በመሄድ ግድቡ፣ የሸንኮራ ልማቱና የስኳር ፋብሪካው ገዳሙን አይነካም ስለሚባልበት ሁኔታ ከዚህ እስከዚህ ተብሎ ርግጡ እንዲነገራቸው እንደሚፈልጉ ቀጥተኛ ጥያቄ አቅርበው ነበር፡፡ ፕሮጀክቱ የሚሠራው ከክልሉ ውጭ ባለው የገዳሙ ክፍል (በትግራይ ክልል) በመሆኑ “እንኳን እኛ [ዞኑ] አያሌው [የክልሉ ፕሬዝዳንት] መጠየቅ አይችልም” የሚል ነበር የተሰጣቸው ምላሽ፡፡ ይህን ተከትሎ ብፁዕነታቸው በሰጡት አስተያየት “ዋልድባ ዓለም አቀፍ ገዳማችን ነው፤ የትግሬው ወይም የአማራው ብቻ አይደለም!!” ማለታቸው ተዘግቧል፡፡
እንግዲህ በሳይንስ ዓምባው አዳራሽ ብፁዕነታቸው የተናገሩት ቃል ከዞኑ ባለሥልጣናት ጋራ በተነጋገሩበት ወቅት ከነበራቸው ፈጽሞ ለመቃረኑየባለሥልጣናቱ ንግግር፣ ከዚያም ይልቅ ቀደም ሲል በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ስም የተሰጠው መግለጫና በስብሰባው ለመሳተፍ ወደ ጎንደር ከመጡት የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ም/ዋ/ሥራ አስኪያጅ የተፈጠረባቸው ከፍተኛ ጫና ሳይኖር እንደማይቀር በምክንያትነት ተጠቅሷል፡፡
የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ምንጮች እንደተናገሩት ም/ዋ/ሥራ አስኪያጁ አቶ ተስፋዬ ውብሸት እንደ ዋነኛ ተግባር የያዙት ለመንግሥት አቋም ብቻ ጥብቅና የቆመ ስምሪታቸው (መንግሥት በይፋ ያመነውን እንኳ በጭፍን እስከ ማስተባበል ድረስ) የብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጁ ይኹንታ ያላገኘ ነው፡፡ ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከተውና በንቡረ እድ አባ ገብረ ማርያም ገብረ ሥላሴ [ከዋልድባ ገዳም የተገኙ መነኮስ ናቸው] የሚመራው የገዳማት አስተዳደር መምሪያ የማያውቀው ወይም ተግባራዊ ተሳትፎው ያልተጠየቀበት ነው፡፡
ምክትል ዋና ሥራ አስኪያጁ መጋቢት 19 ቀን ተደርጎ በነበረው ስብሰባ በዋልድባ ማኅበረ መነኰሳት ተልከው ወደ አዲስ አበባ የመጡት አባቶች “መዋቅር ጠብቀው ከእኛ ጋራ ባለመገናኘታቸው አጥፍተዋል፤ ጉዳዩን አቅርቡልን ስንላቸውም አላመጡም” በማለት ወቅሰዋል፡፡ “ችግሩን የሰማነው የቤተ ክርስቲያን ሚዲያዎች ባልሆኑት ፍትሕ ጋዜጣ እና ደጀ ሰላም ነው” ያሉት አቶ ተስፋዬ “ከዚያ በኋላ በእኔ የሚመራ ልኡክ ወደ ስፍራው ሄደን አይተን ችግሩ አለመኖሩን አረጋግጠናል፡፡ እንዲያውም እኔ እንደ መሪነቴ መናገር ያለብኝ ኢሕአዴግ ለእኛ ያላደረገልን ነገር የለም፤ ደርግ የወሰደውን ንብረታችንን አስመልሶልናል፤ በጀታችን ተቀምቶ ነበር አስመልሶልናል፤ የቤተ ክርስቲያን መብቷ ተከብሮላት ነው ያለው፡፡ አሁንም አገሪቱ እያደገች ነው፤ የኑሮ ውድነት ተፈጥሯል፤ ምእመኑ ለሙዳየ ምጽዋት የሚሰጠው እያጠረው አብያተ ክርስቲያናት እየተቸገሩ ነው፤ ይህ የስኳር ፋብሪካ የልማቱ ውጤት. . .” እያሉ በመናገር ላይ ሳሉ ከቤቱ ጉርምርምታ በመሰማቱ በአቶ አያሌው ትእዛዝ ንግግራቸውን እንዲያቋረጡ ተደርጓል፡፡
የአቶ ተስፋዬን ሐሳብ በመደገፍ እንደሚናገሩ ያመለከቱት የሰሜን ምዕራብ ትግራይ - ሽሬ ሀ/ስብከት ሥራ አስኪያጅ ንቡረ እድ አባ ተስፋይ ተወልደ፣ “ቦታው [ለፕሮጀክቱ የሚቀርበው ገዳመ ዋልድባ] በእኛ ሥር ነው ያለው፤ በጎንደር ያለው ደልሽሐና ሰቋር አይደለም፤ ሄደን አይተነዋል፤ ሕዝቡ ስለማያውቅ ነው፡፡ አቤቱታ አቅራቢዎቹ መዋቅር አልፈው ነው የሄዱት፤ ሕገ ወጦች ናቸው” በማለት አሳጥተዋቸዋል፡፡ ነገሩ ከፋ ከቤቱ ለንቡረ እዱ የተሰጣቸው ምላሽ “ዋልድባ ለጎንደር ሕዝብ ይጠፋዋል ወይ? ይህን እርስዎ ሊነግሩን አይችሉም!!” የሚል እንደነበር ተመልክቷል፡፡
በኀይለ ቃል የታጀበውን ምልልስ የታዘቡ ወገኖች እንደሚሉት የገዳመ ዋልድባ ህልውና እና ክብር ተጠብቆ የመቀጠል አደጋ ምንጭ የፕሮጀክቱ አሉታዊ ተጽዕኖ ብቻ ሳይሆን ገዳሙ በትግራይም በአማራም ክልሎች መገኘቱን በሰበብነት የሚጠቀም ተቃርኖና መሳሳብ፤ ቤተ ጣዕማ እና ቤተ ሚናስ በሚል በማኅበረ መነኰሳቱ መካከል ተፈጥሮ የቆየና በአሁኑ ወቅት መዳከሙ የሚነገረው የነገረ መለኰት ልዩነት (በብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ አገላለጽ የሥላሴን አንድነት የሚያመለክተውን መለኰትን ለአካል ግብር ቅጽል አድርጎ በማቅረብ ሦስቱንም ወላድያን፣ ሦስቱንም ተወላድያን ሦስቱንም ሠራፅያን በማለት ግብርንና ስምን የሚያፋልስ፣ አንድነትና ሦስትነትን የሚያጠፋ የኑፋቄ ርዝራዥ) ዛሬ ስልታዊ መከፋፈያም የመሆኑ አሳሳቢ አካሄድ ነው - በአንድ መቅደስ (መድኃኔዓለም እና ኪዳነ ምሕረት) የሚቀድሱት የቤተ ጣዕማ ማኅበረ መነኰሳት ‹የልማቱ ደጋፊ› የቤተ ሚናስ ማኅበረ መነኰሳት ደግሞ ‹የፕሮጀክቱ ተቃዋሚ› ተደርገው ተፈርጅዋልና!!
እውነቱ ግን “በገዳማችን ላይ የተጀመረው የውኃ ግድብ፣ በከባድ መሣርያዎች የአባቶቻችንን የቅዱሳን ዐፅም ማፍለስና የጥርጊያ መንገድ ሥራ፣ የፓርክ መከለል ያልታሰበ ክሥተት ሆኖብናል፤ የልማት ተቃዋሚዎች አይደለንም፤ የመንግሥት አካላት ግን ወደ ማኅበራችን መጥተው ምንም ያሳወቁን ነገር የለም፤ የመንግሥት ዓላማና ዕቅድ አልገባንም፤ መንግሥት ኀዘናችንንና ጩኸታችንን ይስማ!” በማለት ታኅሣሥ 30 ቀን 2004 ዓ.ም በሦስት አበምኔቶች በተፈረመበትና የሦስቱም ማኅተም ባረፈበት ደብዳቤ ጥያቄ ያቀረቡት ግን፡- የዋልድባ አብረንታንት ገዳም ምክሆን ለገዳማተ ኢትዮጵያ ማኅበር ዘቤተ ሚናስ፣ የዋልድባ ሰቋር ኪዳነ ምሕረት ገዳመ ዋሊ ቅድስት ደቂቁ ለሳሙኤል ርእሰ ገዳማት ዘኢትዮጵያ አስተዳደር ጽ/ቤት፣ በዓዲ አርቃይ ወረዳ ቤተ ክህነት የዋልድባ ዳልሽሐ ኪዳነ ምሕረት አንድነት ገዳም በጋራ ሆነው ነው፡፡ አሁን ሙሉ በሙሉ እንደ ቆመ የሚነገረው ፓርክ የመከለል ዕቅድ በዓዲ አርቃይ ወረዳ - ሰሜን ጎንደር በኩል ነው፤ አቶ ኣባይ ‹አሉባልታ› ያሉት መንገድ የማውጣቱ አማራጭ ውጥን በዚሁ በኩል እንደሆነም ምንጮቻችን ያሳያሉ፤ ግድቡ የሚቆምበት የዛሬማ ወንዝ ደግሞ በወልቃይት ወረዳ - ምዕራብ ትግራይ በኩል የሚገኝ ነው፡፡
ማኅበረ መነኰሳቱ በደብዳቤያቸው እንደጠቆሙት፣ በጎንደሩ ስብሰባም ከቀረበው ዘጋቢ ፊልም ለመረዳት እንደተቻለው “የገዳማችን አፈር/መሬት የደማችን ያህል ይሰማናል” ሲሉ የተደመጡት መነኰሳቱ በልማት ዕቅዱ ዙሪያ ከመንግሥት አካላት ጋራ አልተወያዩም፡፡ ይህም አቶ ኣባይ ፀሃዬ በውይይቱ መግቢያ ላይ “ሕዝብ አወያይተን ነው ወደ ሥራ የገባነው” ካሉት ጋራ የሚጋጭ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ እርሳቸው የሚሉትን አምነን እንቀበል ቢባል እንኳ ውይይት የተባለው የተካሄደው በፕሮጀክቱ ከሚነሡት ወገኖች ጋራ እንጂ መነኰሳቱን አያካትትም፡፡
አቶ ኣባይ በሰጧቸው ማብራሪያዎች ከእውነታው ጋራ ተጋጭቶ የተገኘው ይህ ብቻ ሳይሆን÷ ለአፈር ምርምራ በሚል ወደ ገዳሙ ይዞታ የተገባው በዶዘር በማረስ መሆኑ፣ በገዳሙ ክልል ከተቀበሩቱ 27 ዐፅሞች በመንገድ ሥራው መነሣታቸው ሳያንስ መንግሥት ባልተሰጠው ሥልጣን “ቀባሪ ዘመድ የሌላቸው የድኾች ዐፅም እንጂ የቅዱሳን አይደለም” መባሉ ይገኙበታል፡፡
በስብሰባው ዕለት ለአቶ ኣባይ ፀሃዬ ቀርበው አሳማኝ ምላሽ ያላገኙ የተወያዮች ጥያቄዎች ለማስረጃም ለማገናዘብም ይጠቅማሉና እንደሚከተለው አጠቃለናቸዋል፡፡
  • በቴሌቪዥን ዜና ሰዓት በሰጡት መግለጫ ገዳማቱ ውስጥ የፖሊቲካ ተልእኮ ያላቸው መነኰሳት እንዳሉ በመጥቀስ ስለ አባቶቻችንንና ስለ ገዳሙ በድፍረት ተናግረዋል፡፡ አባቶቻችንም ገዳሙም እርስዎ እንዳሏቸው የፖሊቲካ ተልእኮ ያላቸውና የፖሊቲከኞች መናኸርያ አይደሉም፡፡ [አቶ ኣባይ ለዚህ ጥያቄ በሰጡት ምላሽ “እንዲህ ያልኹት የመነኰሳቱ አቤቱታ መዋቅር ጠብቆ ለጠቅላይ ሚኒስትሩም ይኹን ለክልሉ ሳይደርስ በውጭ ሚዲያዎች እንደቀረበልን ተደርጎ መነገሩ የመንግሥትን ስም የማጥፋት ዘመቻ ያለው የፀረ ሰላም ኀይሎች ፖሊቲካዊ ተልእኮ በመሆኑ ነው”  ማለታቸው ተዘግቧል፡፡ አቶ ኣባይ ይህን ቢሉም መልእክተኞቹ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢሮ ፊት ተነስቷቸው ከተመለሱ በኋላ አቤቱታቸውን የያዘውን ደብዳቤ በተለያየ መንገድ ለቢሮው መላካቸውን አልገለጹም፡፡]
  • በጀርመን ድምጽ ሬዲዮ የቀረቡ አንድ የመንግሥት ባለሥልጣን ብዙ የሚፈርሱ አብያተ ክርስቲያን እንዳሉ ተናግረዋል፤ ያረጋግጡልን?
  • 50,000 ሰው ይቀጠራል፤ 5000 ቤቶች ይሠራሉ” ብላችኋል፡፡ እንግዲያውስ ገዳሙ ከተማ መሆኑ ነዋ!! መነኰሳቱኮ እዚያ ድረስ የሄዱት ዓለምን ጥለው፣ ጥሞናን ሽተው ነው፡፡
  • 27 ዐፅም አንሥተናል ብላችኋል፤ እኒህ ወገኖች የተቀበሩት ቅዱሱ ቦታ ላይ ነው፡፡ እናንተ ግን “አቅም፣ ዘመድ የሌላቸው የድኾች አስከሬን ነው” አላችሁ፡፡ ኢትዮጵያውያን ቀባሪ አጥተው አያውቁም፡፡ እንኳን በዋልድባ በሌላ ቦታ እንዲህ ዐይነት ቀብር የለም፡፡ በዚህ ላይ ዐፅሞቹ የቅዱሳን ዐፅም አይደሉም ብላችኋል፡፡ ቤተ ክርስቲያን እንጂ እናንተ ይህን መወሰን ትችላላችኹ ወይ?
  • “ሕዝቡ ሲነሣ ማኅበራዊ ተቋሙ አብሮ ይነሣል” ብላችኋል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ማኅበራዊ ተቋም ውስጥ አለችበት ወይስ የለችበትም?
  • የግድቡ ውኃ ወደ ገዳሙ አይሄድም” በሚል ገዳሙ አልተደፈረም ብላችኋል፤ “ኀጢአት አይሻገርብሽ” ሲባልኮ የገዳሙን ወገብና እግር ትቶ ጭንቅላቱን ሲነካ ብቻ አይደለም፡፡ ውኃው የሚያርፍበት፣ ዐፅሙ የሚነሣበት ቦታ የገዳሙ ይዞታ ነው፡፡
  • በመዘጋ በኩል የመነኰሳቱ የአትክልትና ቋርፍ ማዘጋጃ ቦታዎች ይነሣሉ፤ መነኮሳቱ ምን እየበሉ እንዲኖሩ ነው?
  • ደርግ ቤተ ክርስቲያንን አፍርሶ አያውቅም፤ እናንተ ግን በልማት ቤተ ክርስቲያን እያፈረሳችኹ ነው፡፡
  • ቤተ ሚናስ ማኅበረ መነኰሳትን እያስፈራራችኋቸው ነው፡፡ ይህ መቆም የለበትም?

የሚሉ ናቸው፡፡
በሌላ በኩል በስብሰባው ላይ “ወደ ዋልድባ በሄደው የሀገረ ስብከቱ ልኡካን ቡድን ውስጥ የማኅበሩ ጎንደር ማእከል ተካቶ ሳለ ለምን አብሮ አልተጓዘም” በሚል ለቀረበው ጥያቄ የሀገረ ስብከቱ መልአከ ሕይወት ቀለም ወርቅ ስለ ገዳሙ የሚነሣውን ጥያቄ ወደ ማኅበረ ቅዱሳን በመግፋት “በመኪና እጥረት የማእከሉን ተወካዮች ይዘን መሄድ አልቻልንም” የሚል ለማንም መስሎ ያልታየ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ የሀገረ ስብከቱ ልኡክ ተቀባይነት እንዳይኖረው ካደረጋቸው አካሄዶች አንዱም የማኅበሩ አባላት እንዲካተቱ አለመደረጉ መሆኑ ከተሳታፊዎቹ ተነግሯቸዋል፡፡
በተያያዘ ዜና ማኅበረ ቅዱሳን ለሀገረ ስብከቱና ለሚመለከተው የመንግሥት አካል ደብዳቤ ጽፎ ባገኘው ፈቃድ አምስት አባላት ያሉት አጥኚ ቡድን ወደ ፕሮጀክቱ አካባቢ ልኮ ይፋዊ ሪፖርት እንደሚያቀርብ ተጠቁሟል፡፡ ከማኅበሩ ዋናው ጽ/ቤት፣ መቐለ እና ጎንደር ማእከላት የተውጣጡ አባላት የሚገኙበት ይኸው አጥኚ ቡድን በነገው ዕለት ወደ ስፍራው እንደሚንቀሳቀስ የሚጠበቅ ሲሆን ለቤተ ክርስቲያንም ለአገርም ጠቃሚ የሆነ ሪፖርት እንደሚያቀርብ ይጠበቃል፡፡
ማኅበረ ቅዱሳን ከዓመታት በፊት (በ1990 ዓ.ም) ከገዳሙ ማኅበረ መነኰሳት ጋራ በመተባበር ለዘመናዊ ወፍጮ ተከላ፣ ለመጠጥና መስኖ ውኃ ልማት የአምስት ሚልዮን ብር የልማት ፕሮጀክት ቀርጾ ለሰሜን ምዕራብ ትግራይ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት አቅርቦ እንደነበር ተገልጧል፡፡ ፕሮጀክቱ ቀደም ሲል በተመለከተው የቤተ ጣዕማ - ቤተ ሚናስ ልዩነት ሳቢያ አንዱ ቤት ሲቀበል ሌላው ቤት በመቃወሙ ሳይተገበር መቅረቱ ተዘግቧል፡፡ የቡድኑ ጉዞ በዚሁ የልማት ዕቅድም ላይ ያለውን መሳሳብ በማስወገድ አንድ መግባባት ላይ ለመድረስ እንደሚያስችል ተስፋ ተደርጓል፡፡
በተያያዘ ዜና ባለፈው ሳምንት ዓርብ፣ መጋቢት 21 ቀን 2004 ዓ.ም፣ ወደ ዋልድባ ገዳም ያመሩት በጎንደር የስድስት ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ግቢ ጉባኤያት አባላት የሆኑ ተማሪዎች ዛሬ ማምሻውን ወደ ጎንደር ከተማ መመለሳቸው ታውቋል፡፡ ተማሪዎቹ መጋቢት 27 በአብረንታንት መድኃኔዓለም የሚከበረውን በዓል በማዘከር፣ የክልሉ ፕሬዝዳንት በሳይንስ ዓምባው አዳራሽ ስብሰባ “ሄዳችሁ እውነታውን ማረጋገጥ ትችላላችኹ” በማለት የሰጡትን ማረጋገጫም መሠረት በማድረግ ነበር ወደ ገዳሙ ያመሩት፡፡
ተማሪዎቹ ከቦታው ደርሰው የዋልድባ ገዳም መሥራች የሆኑትን የጻድቁ አቡነ ሳሙኤል (ሳሙኤል ፀሐይ ዘዋሊ) መቃብርና የመድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ተሳልመዋል፤ የማኅበረ መነኰሳቱ ምልዓተ ጉባኤ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ የላኩትን ደብዳቤ ተመልክተዋል፡፡
በደብዳቤው ላይ በተዘረዘረው መሠረት ገዳማውያኑ በፕሮጀክቱ ምክንያት ስለሚነሡት አብያተ ክርስቲያን፣ የሙዝ ተክላቸውና ቋርፍ የሚያዘጋጁባቸው ቤቶች በሚካሄደው እርሻ ስለሚጠፋበት ሁኔታ፣ ስለሚፈርሱት የገዳሙ አብነት ት/ቤቶችና ይህን ተከትሎ ስደት ስለሚጠብቃቸው መምህራንና ተማሪዎች በዝርዝር እንዳስረዷቸው ተገልጧል፡፡ በተለይ የሙዝ ተክሉ ከተነሣ መነኰሳቱን በስፍራው የሚያቆያቸው ድርጎ ባለመኖሩ ይኸው ጉዳይ በማይ ፀብሪው ስብሰባ በተነሣበት ወቅት ባለሥልጣናቱ “በስድስት ወር የሚደርስ ሙዝ እንሰጣችኋለን” የሚል ምላሽ እንደሰጧቸው ገዳማውያኑ መናገራቸው ተጠቅሷል፡፡
ከዚህ በመቀጠል ፕሮጀክቱ ከገዳሙ ጋራ ወደሚገናኝበት ስፍራ መጓዛቸውን የተናገሩት ተማሪዎቹ በፖሊስ ኀይል ከመንገድ እንዲመለሱ መደረጋቸውን ገልጸዋል፡፡ “በማንኛውም አቅጣጫ ወደ ገዳሙ መግባት እንደሚቻል ይኹንና በተለይ በፕሮጀክቱ በኩል ከገዳሙ መውጣት የተከለከለ ነው” ስለመባላቸው ያስረዱት ተማሪዎቹ በቋንቋ እንኳ ከፖሊስ ኀይሉ ጋራ መግባባት እንዳልቻሉ ጠቁመዋል፡፡ ይህም ኾኖ ከገዳሙ ወጥተው ወደ ጎንደር በሚመለሱበት ወቅት በርካታ ምእመናን መጋቢት 27 ቀን ለሚከበረው የመድኃኔዓለም በዓል ወደ ገዳሙ እየተጓዙ መመልከታቸውን ጠቁመዋል፡፡

 ር ወሬ ያሰማን
 አሜን፡፡
የመላው ዓለም የተዋሕዶ ቤተሰብ

No comments:

Post a Comment