Friday, February 22, 2013

ሰበር ዜና – አስመራጭ ኮሚቴው ለዕጩነት የለያቸው አምስት ሊቃነ ጳጳሳት ታወቁ !!


  • ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል እና ብፁዕ አቡነ ገብርኤል አልተካተቱም
  • ሁሉም የኮሚቴው አባላት በውሳኔው ስለመስማማታቸው አጠራጣሪ ኾኗል
  • የፓትርያሪክነት መመዘኛ መስፈርቱ ከዕጩዎች ማንነት ጋራ በአግባቡ ይረጋገጥ
  • ‹‹ዕጩዎቹን ስታውቅ ፓትርያሪኩን ታውቃቸዋለኽ››› /ሰሞንኛ አባባል/
የስድስተኛው ፓትርያሪክ አስመራጭ ኮሚቴ ለዕጩ ፓትርያሪክነት አጣርቶ የለያቸውን አምስት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ለቋሚ ቅ/ሲኖዶሱ ማቅረቡ ተሰማ፡፡ ከየካቲት ዘጠኝ ቀን ጀምሮ የዕጩዎች ልየታ ሲያካሂድ የቆየው አስመራጭ ኮሚቴው÷ ለፓትርያሪክነት ለመመረጥ ብቁ ናቸው ብሎ ያመነባቸው የአምስቱ ሊቃነ ጳጳሳት ስም ዝርዝር፡-
1)  ብፁዕ አቡነ ማትያስ – በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማት ሊቀ ጳጳስ
2)  ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ – የወላይታ ዳውሮ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ
3)  ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ – የባሌ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ
4)  ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል – የከፋ ሸካ ቤንች ማጂ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅ/ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ
5)  ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ – የሰሜን ጎንደር ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ናቸው፡፡


የአስመራጭ ኮሚቴው አጣርቶ ሊያቀርባቸው ከሚችላቸውና የቅድሚያ ግምት ከተሰጣቸው አባቶች አራቱ በኮሚቴው የዕጩዎች ዝርዝር ውስጥ መግባታቸው የሚጠበቅ ነው፡፡ ኮሚቴው በሚያቀርባቸው ዕጩዎች ውስጥ ያልተጠበቁ አባቶች ሊታዩ እንደሚችሉም አስቀድሞ የተገመተ ነበር፡፡
ነገር ግን በብዙ ሺሕ የካህናትና ምእመናን ድምፅ የተጠቆሙትና በፓትርያሪክ ምርጫ ሕግ አንቀጽ 5 የተዘረዘረውን የዕጩ ፓትርያሪክነት መመዘኛ መስፈርቱን ያሟላሉ ተብለው የታሰቡት ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል (ከ9000 ያህል ጠቅላላ ጠቋሚዎች 7200 አግኝተዋ)
እና ብፁዕ አቡነ ገብርኤል ከዕጩዎቹ ሳይካተቱ መቅረታቸው ጉዳዩን በቅርበት የሚከታተሉ አካላትን መስገረሙ አልቀረም፡፡ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል ቀድሞም ከዕጩዎች ዝርዝር እንዳይጨመሩ በአንዳንድ የአስመራጭ ኮሚቴው አባላትና በተለይም ‹‹መንግሥት የሚፈልጋቸውን ብፁዕ አቡነ ማትያስን እናስመርጣለን›› በማለት በመራጮች ላይ ሽብርና ስጋት ሲፈጥሩ በሰነበቱት÷ የእነ ንቡረ እድ ኤልያስ፣ ወ/ሮ እጅጋየሁ በየነ፣ መጋቤ ካህናት ኀይለ ሥላሴ ዘማርያም፣ ሊቀ ሊቃውንት ዕዝራ ተክለ ጊዮርጊስ፣ መ/ር አባ ገብረ መድኅን ኀይለ ጊዮርጊስ እና መ/ር ዕንቊ ባሕርይ ተከሥተ ቡድን ከፍተኛ ጫና ሲፈጠር መሰንበቱ ተዘግቧል፡፡
ኮሚቴው ዕጩዎቹን የለየበትን ሂደት ወደፊት በዝርዝር ለማወቅ የሚጠበቅ ቢኾንም ስለ ተግባርና ሓላፊነቱን አስመልክቶ÷ በአንቀጽ 6/ሐ – ጥቆማ ከቅ/ሲኖዶስ አባላት፣ ከካህናትና ምእመናን እየተቀበለ እንደሚሠራ፤ በአንቀጽ 6/ሰ – የዕጩዎችን ስም ዝርዝር ከትምህርት ደረጃቸው፣ ችሎታቸውና ልምዳቸው ጋራ ለ15 ቀናት ይፋ በማድረግ ጥያቄዎችንና አስተያየቶችን እንደሚቀበል፤ በአንቀጽ 6/ሸ – በተቀበላቸው ጥያቄዎችና አስተያየቶች መሠረት ዕጩዎቹን ከቅ/ሲኖዶስ ጋራ መርምሮና አጣርቶ የሚቀበለውን ከተቀበለ፣ የማይቀበለውንም ከጣለ በኋላ ለፓትርያሪክነት ለመመረጥ ብቁ ናቸው ብሎ ያመነባቸውን ዕጩዎች ስም ዝርዝር ከትምህርት ደረጃቸው፣ ችሎታቸውና ልምዳቸው ጋራ እንደሚያሳውቅ በግልጽ የተደነገገ በመኾኑ ቀጣይ አካሄዱ ከእኒህ በተጨባጭ መሸራረፍ ከጀመሩ አናቅጽ አኳያ የሚመዘን ይኾናል፡፡
ሐራዊ ምንጮች ከወዲሁ ስለኹኔታው ለመረዳት ባደረጉት ጥረት ሁሉም የኮሚቴው አባላት በውሳኔው ስለመስማማታቸው ጥርጣሬ ያላቸው ሲኾን ከዚህም በመነሣት ውሳኔውን በፊርማቸው ስለማረጋገጣቸውም አበክረው ይጠይቃሉ፡፡
‹‹ዕጩዎቹን ስታውቅ ፓትርያሪኩን ታውቃቸዋለኽ›› የሚለው ሰሞንኛ አባባል ቋጠሮው ሊፈታ እነኾ ቀኑ ቀርቧል፡፡

Source: http://haratewahido.wordpress.com/

የተዋሕዶ ቤተሰቦች በመላው ዓለም

No comments:

Post a Comment