Wednesday, September 5, 2012

የተሀድሶያውያን ቀበሮ መነኩሴና በቤተክርስትያን ላይ የተካሄደ ዘረፋ


  • የመነኩሴ ነኝ ባዩ ሚስት የ4ወር ነፍሰ ጡር ናት
  • ከተለያዬ ገዳማት የተሰረቁ ሶስት ማህተብ ፤ ሁለት የመጾር መስቀል ፤ ሁለት መጽሀፍት እና ንዋየ ቅዱሳት በቤቱ ተገኝቷል፡፡
  • በአምስት የተለያዩ ስሞች አማካኝነትከገዳም ገዳም እንደሚንቀሳቀስ ታውቋል
(አንድ አድርገን ነሐሴ 28 2004 ዓ.ም)፡- አባ ይትባረክ የሚባል የተሀድሶ ቅጥር የዛሬ ወር ገደማ በደብረ ብርሀን ከተማ ቅድስት አርሴማ ቤተክርስትያን ሲያደርግ የነበረውን ስራ ገልጠን መጻፋችን ይታወቃል ፤ አባ ይትባረክ መጀመሪያ ጎንደር ይኖር የነበረ ከዚያም ደንጨት ዮሐንስ ገዳም ሲያገለግል የነበረ ሰው ሲሆን ከመንዝ አካባቢ እንደመጣ የጀርባ ታሪኩ ይናገራል በደብረብርሐን ከተማ በደብረ ማዕዶት ቅድስት አርሴማ ገዳም በመግባት ሲያገለግል እንደነበር እጃችን የገቡ መረጃዎች ያስረዳሉ፡፡ በቤተመቅደስ ውስጥ ድፍረትና ክህደት የተሞላበት የአማኙን እምነት የሚቀንስና ለትልቅ ድፍረት የሚያደፋፍር እንቅስቃሴዎች ሲያደርግ እንደነበር በስተመጨረሻም በወንድሞች ብርቱ ክትትል ስራው ተገልጦበት ደብረ ብርሀን አርሴማን በመልቀቅ ወደ ናዝሬት እንዳመራ ገልጠን በወቅቱ ጽፈን ነበር፡፡

ለዓመታት በሰላም በፍቅር ሲኖሩ የነበሩ መነኮሳት መሐል እሾህ ተክሎ ለመሄድ የእርስ በእርስ ግንኙነታቸውን ለማሻከር ወሬን ከአንድ ወገን ወደ ሌላ ወገን እያመላለሰ የውስጥ ሰላማቸውን ለማናጋት ስራ ሲሰራ እንደነበር አብረውት ከነበሩት ሰዎች ለማወቅ ተችሏል ቀድሞ እህቴ ነበረች ያላትን ወለተ መስቀል የተባለችውን መነኩሴ ነኝ ባይ በአደባባይ ባለቤቴ ናት በማለት በደብረ ብርሐን ከተማ አንዲት ክፍል ቤት በመከራየት አብረው ሲኖሩ እንደነበር ጉዳዩን በቅርብ ሲከታተሉ የነበሩ ሰዎች ይስረዳሉ ፡፡

ይህ ሰው ደስ ሲለው የአቡነ ተክለሃይማት ቆብና ቀሚስ በመልበስ የአባቶችን መስቀል በመያዝ የምንፍቅና ትምህርት በየጎጡ ሲሰጥ የነበረ ሲሆን አንዳንድ ጊዜ ቆብና ቀሚሱን በማውለቅ በጃኬት በሱሪና በኮት እየሆነ የተለያየ ገጽታን በመላበስ የምንፍቅና ትምህርቱን ሲያሰራጭ እንደነበር በቅርብ ሲከታተሉት ከነበሩ ወንድሞች ለማወቅ ተችሏል ፡፡
አሁን በደረሰን መረጃ መሰረት አባ ይትባረክ ደነባ በዓታ ለማርያርም አንድነት ገዳም ሐምሌ 12 2004 ዓ.ም አባ ገብረስላሴ በሚል አዲስ መጠሪያ በቅዳሴ መምህርነት መቀጠሩን ለማወቅ ችለናል ፤ የድቁና ስሙ እንዳልካቸው ወልዴ እንደሚባል የተቀጠረበት ማስረጃ ይናገራል ፤ ይህ ሰው እዚህ ገዳም መቀጠሩን የሰሙ ስለ ቤታቸው የሚቆረቁራቸው ወንድሞች ስለ ሰውየው ያላቸውን መረጃ በመያዝ ፤ ቀድሞ ከወር በፊት “አንድ አድርገን” ላይ የወጣውን መረጃ በማጠናቀር ገዳሙ ድረስ በማምራት አብረው ከሚሰሩት መነኮሳ ጋር ምክክር አድርገዋል ፤ ይህ ሰው አንድ ወር ከአንድ ሳምንት ያህል ጊዜ ከገዳሙ ካሳለፈ በኋላ የገዳሙን ንዋየ ቅዱሳን በመስረቅ ተጠርጥሮ ቅዳሜ 19/12/2004 ዓ.ም በፖሊስ አማካኝነት እስር ቤት ሊወርድ ችሏል ፤ ይህን ጉዳይ በማጣራት ላይ የነበረው ፖሊስ ከፍርድ ቤት የፍተሻ ፍቃድ በማውጣት ቤቱን በሚፈትሽበት ጊዜ እስከ ዛሬ የማጭበርበ ወንጀል ሲሰራበት የነበሩ ሰነዶች ፤ ማህተሞች ፤ ቲተሮች እና ከተለያዩ አብያተክርስቲያናትና ገዳማት የሰረቃቸውን መገልገያዎችን መያዝ ችሏል ፤ በአሁኑ ወቅትም በደነባ ፖሊስ ጣቢያ ውስጥ ይገኛል ፡፡ ከተያዙት ነገሮች ውስጥ …

  1. ሶስት የግርጌና የራስጌ ማህተሞች በፍተሻው ተገኝቷል ፡- እነዚህን ማህተሞች ከዓመታት በፊት ካገለገለባቸው ደብሮች በመስቀረቅ በርካታ ህገ ወጥ ስራዎችን በማህተቦቹ አማካኝነት በመጠቀም እንዳከናወነ ታውቋል ፤ የመጀመሪያው ማህተብ በሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት በላስታ ወረዳ አምባ ጽዮን ቤተክርስያንና ሁለተኛው ደግሞ የጣራ አንድነት ገዳም ማህተም መሆኑ ታውቋል ፤ ሌላ ሶስተኛ ማህተብም ከቤቱ ፖሊስ መያዝ ችሏል ፤ ይህ ሰው ከማህተም ጋር በተያያዘ የራሱ የሆነ አባ መምህር ገብረማርያም (ዋና አስተዳዳሪ) የሚልም ማህተም(ቲተር) በፍተሻው ወቅት በቤቱ ውስጥ ተገኝቷል፡፡ አኒህን በመሰሉ ሰዎች አማካኝነት ቤተክርስቲያንን ለማገልገል በቂ እውቀት የሌላቸው ሰዎች ጥቂት በመቶዎች የሚቆጠር ብር በመክፈል በጥራዝ ነጠቅ እውቀታቸው የቤተክርስትያኒቱን የአገልግሎት ማዕረጎች ድቁና ፤ ቅስና ፤ መጋቢ ሀዲስና ፤ የቅዳሴ መምህር እና መሰል ስሞችን በመውሰድ በየቦታው እንደሚገኙ በየጊዜው የሚደርሱን ማስረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ከዚህ በፊት ግዕዝ በአግባቡ ማንበብ የማይችል ሰው “መጋቢ ሐዲስ” የሚል ስም ጊዜው ደርሶ እስኪመልሰው ድረስ በገጸ በረከት መልኩ ከአንድ አባት መቀበሉ የሚታወቅ ነው ፡፡
  2. አምስት የተለያዩ የራሱ ስሞች የሚገኝባቸው ሰነዶች ተገኝተዋል፡- ይህ ማለት አንድ ሰው በአምስት የተለያየ ስም የተለያዩ አይነት የቤተክርስቲያኒቱ ማዕረግ ይገኙበታል ፤ ይህ ሰው ከሶስት ወር በፊት ደብረ ብርሀን ቅድስት አርሴማ ቤተክርስያን ሲቀጠር አባ ይትባረክ ይባል ነበር ፤ እኛም በወቅቱ አባ ይትባረክ ብለን ስራዎቹን መዘገባችን ይታወቃል ፤ አሁን ግን በደነባ በዓታ ለማርያም አንድነት ገዳም ውስጥ የተቀጠረበት ስም ደግሞ መምህር አባ ገብረስላሴ በሚል ነው ፤ ፖሊስ ቤቱን ሲፈትሽ ከነዚህ ሁለት ስሞች በተጨማሪ ሌላ ሶስት የተለያዩ የቤተክርስትያኒቱን የአገልጋዮች ማዕረግ በመጠቀም በአንድ አይነት ፎቶ አባ ሳሙኤል ፤ አባ ወልደ ገብርኤል ደርበውና አባ በረከት የሚል ከበፊቶቹ ሁለት ስሞች በተጨማሪ ሶስት ህጋዊ መሳይ ሰነዶች መያዝ ችሏል ፤ በጠቅላላ በተለያዩ ማዕረጎች አምስት ስሞች ያሉት ከፍተኛ መሰሪ የሆነ ሰው መሆኑ ታውቋል ፤
  3. ከሐይቅ እስጢፋኖስ ገዳም አባ ገብረስላሴ በሚል ስም የቅዳሴ መምህርነቱን የሚገልጽ ህጋዊ መሳይ የምስክር ወረቀት ተይዟል ፡- ይህ የምስክር ወረቀት ወደ ፊት ፖሊስ ትክክለኛ የገዳሙ ማስረጃ መሆኑን ተጨማሪ ምርመራ የሚያካሂድበት መሆኑ ታውቋል ፤ይህን ሰው ቀድሞ ዱካውን ሲከታተሉት የነበሩት ወንድሞች ማስረጃው እንደከዚህ ቀደሙ የተጭበረበረና የቤተክርስትያኒቱ እንዳልሆነ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
  4. አንድ ሞጣኢት በቤቱ ተገኝቷል ፡- ይህ ሞጣይት በደብረ ብርሀን ስላሴ ቤተክርስትያን አባ በረከት በሚል ስም እያገለገለ ሳለ ከገዳሙ የሰረቀው መሆኑን ለማወቅ ተችሏል ፤
  5. ሁለት ትላልቅ የመጾር መስቀሎች ተገኝተዋል ፡-እነዚህ መስቀሎች ከየትኛው ቤተክርስትያን ወይም ከየትኛው ገዳም መሰረቃቸው አይታወቅም ፤ ነገር ግን ወደፊት ፖሊስ በሚያደርገው ማጣራት መሰረት ከየት እንደሰረቀው የሚጠቁም ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል
  6. አንድ መጽሀፈ ግጻዌ ተገኝቷል ፡-ይህ መጽሀፍ በቤተክርስትያን የቅዳሴ ስነ-ስርዓት ምስባክ ማውጫ መሆኑ ይታወቃል ፤ ይህ መጽሀፍ ላይ ያለው ማህተብ እንደሚጠቆመው የመንዝ ጌራ ምድር ደብረ ሰላም ቅዱስ ዮሀንስ አንድነት ገዳም መሆኑን ይናገራል ፤ ስንት አብያተክርስትያናት በንዋየ ቅዱሳት እና በመጽሀፍት እጥረት አገልግሎታቸውን በአግባቡ ማድረግ የማይችሉበት በአሁኑ ጊዜ እንዲህ አይነት መሰሪ መነኩሴ መሳይ ሰው ምን ያህል ንብረቶቻቸው እየተዘረፉ መሆኑን ማሳያ ምልክት ነው ፤ እኛ ጥቆማ የደረሰን ተከታትለን የደረስንበት ሰው ይህን ያህል ጉዳት በቤተክርስትያኒቱ ላይ ያደረሰ ከሆነ ፤ ሌላውን አምላክ ይቁጠረው…
  7. አንድ ተዓምረ ማርያም በቤቱ ተገኝቷል፡- ይህ ተዓምረ ማርያምን በተመለከተ አንድ አባት ከእሳቸው እንደተሰረቀ በመናገር የኔ ነው ይመለስልኝ የሚል ጥያቄ አቅርበዋል ፡፡


በደብረብርሀን ከተማ ቅድስት አርሴማ ገዳምን ከወራት በፊት በተቀላቀለበት ወቅት ገዳም ሲገባ አብራውየመጣች ወለተ መስቀል(ወ/ሮ አበባ) የምትባል መነኩሴ የነበረች ሲሆን ፤ በከተማው ውስጥም ቤት ተከራይቶ ሲያኖራት ነበር ፤ በገዳሙ በነበረው ቆይታ ለገዳማውያን አገልጋይ ካህናትከአንድ እናት ማህጸን የወጣን እህቴነች” እያለ ሲያወራ ነበር ፤ በስተመጨረሻ ግን በራሱ አንደበት ሚስቱ መሆኗን መስክሮ ደብረ ብርሀንን ለቆ ወጥቷል ፤ ይህ በእንዲህ እያለ ይች ሴት ወ/ሮ አበባ እንደምትባልና በአሁኑ ሰዓት ከእሱ የ4ወር ነፍሰጡር መሆኗ የሀኪም ማስረጃዋ ይናገራል፡፡ ይህ ሰው ደነባ በዓታ ለማርያም አንድነት ገዳም በነበረበት የአንድ ወር ጊዜ በጾታ ትንኮሳ እንዳደረገም ገዳሙ አካባቢ ያሉ ሰዎች ተናግረዋል፡፡


ደብረ ብርሃን ከተማ ውስጥ በጃኬት በሱሪና በኮፍያ ከርቀት የተነሳው ፎቶ

ይህ ሁሉ ስራው ተደርሶበት አቶ በረከት ከታሰረ በኋላ ከደብረብርሀን ከተማ በርካታ ፕሮቴስታንቶች ወደ ታሰረበት ቦታ በመሄድ ጠይቀውት ነበር ፤ ሰው ሲታሰር መጠየቅ አግባብ ቢሆንም ይህ ሰው ከዚህ በፊት ከእነዚህ ሰዎች ጋር ያለውን የጠለቀ ግንኙነት የሚያሳይ ነገር ሊሆን ይችላል ፤ በነበረው ግንኙነትም የተነሳም መጀመሪያ የደረሱለት እነርሱ ነበር ፤ አቶ አበራ ከሚባል ሰው ጋር ቀድሞውንም ቢሆን ከፍተኛ ቁርኝነት የፈጠረ ሰው መሆኑ ተደርሶበት ነበር ፤ አቶ አበራ ማለት በግልጽ የፕሮቴስታንት እምነት ተከታይ ሲሆን አልፎ አልፎ በቤተክርስትያን አካባቢ ከሚያገለግሉ ሰዎች ጋር ከመገናኝት በተጨማሪም ቤተክርስትያን እንደሚመጣ ለማወቅ ተችሏል፡፡ አቶ በረከት ከፕሮቴስታንታዊ ተሀድሶ አራማጆች ጋር የጠበቀ ግንኙነት እንዳለው ታውቋል፡፡

በተለያዩ ቤተክርስትያን የሚመጡ ጸጉረ ልውጦችን ከቤተክርስትያኒቱ ሰበካ ጉባኤ በተጨማሪ እያንዳንዱ ምዕመን በግልጽም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ሰዎቹ ትክክለኛ ቤተክርስቲያን የወከለቻቸው ወንጌልን ለማስፋት የሚጥሩ ምንፍቅና እና ኑፋቄ ያልደረሰባቸው መሆናቸውን ማረጋገጥ ያስፈልገዋል ፤ያለፈው ስህተታችን ለወደፊት ትምህርታችን ሊሆነን ይገባል ፡፡

መቼም ይችን አንዲት ቤተክርስትያን ከእነዚህ አይነት ሰዎች ፀድታ ማየት የምንፈልግ ከሆነ የመረጃ ሰዎች መሆን መቻል አለብን ፤ ነገሮችን አጽንኦት ሰጥተን መከታተል መቻል አለብን ፤ አሁንም ውስጣችን አሉ ወደፊትም ይኖራሉ ፤ ያለመታከት ተከታትለን ስራቸውን ልንገልጥ ግድ ይለናል ፡፡ ሁላችንም እንደ አንድ ምዕመን ሃላፊነታችንን እንወጣ፡፡

የዚህን ሰው መጨረሻ ተከታትለን የምናቀርብ መሆኑን ለመግለጽ እንወዳለን ፤ እዚህ ጽሁፍ ላይ የተገለጹት ማስረጃዎችን እንዳስፈላጊነታቸው ስካን በማድረግ ሰው እዲያውቀው እናደርጋለን ፡፡

ቸር ሰንብቱ

የተዋሕዶ ቤተሰቦች በመላው ዓለም

1 comment:

  1. Egziabher Yimesgen negeroch eyelewetu new. Kale Hiwot Yasemalin. ቁርጠኛ የተዋሕዶ ልጆች Bertu Egziabher yirdachihu.

    ReplyDelete