Friday, July 13, 2012

የላስ ቬጋስ ኪዳነ ምሕረት ወቅዱስ ሚካኤል ቤተ ከርስቲያን ከአቡነ ፋኑኤል ጋር እንደማይሠራ በድጋሚ አረጋገጠ



  • የደብሩ ማኅበረ ካህናት የፈረሙበትን ደብዳቤ ተመልከቱ

(ደጀ ሰላም፤ ሰኔ 14/2004 ዓ.ም፤ ጁን 21/ 2012/ READ THISARTICLE IN PDF)፦ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ በምዕራብ አሜሪካ የካሊፎርኒያ ሀ/ስብከት ሥር የሚገኘው የላስ ቬጋስ ሐመረ ኖኅ ኪዳነ ምሕረት ወቅ/ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን “ከብፁዕ አቡነ ፋኔኡል ጋር እንደማንሠራ እና የሸቱትንም ሾመት የማንቀበል መሆኑን” እንገልጻለን ባለበት መግለጫው አቡነ ፋኑኤል “ከዚህ በፊት ለአህጉረ ስብከቱ ተመድበው አባታዊ መመሪያ እና ሐዋርያዊ አገልግሎት ይሰጡ ከነበሩት አባቶች በተለየ መልኩ በመጓዝ ካህናት እና ምዕመናንንን በማሳዘን ለመናፍቃን በር የሚከፍት የቤተ ክርስቲያን መዋቅር እና ሥርዓት ባልጠበቀ እና ባልተከተለ መንገድ መመሪያ በመስጠት እና በተግባርም በመፈፀም የግል ጥቅምን ብቻ በሚያስጠብቅ አካሄደ በመጓዛቸው በሚሠጡት የተሣሣተ እና ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን የወጣ አመራር ጋር አብሮ መጓዝ ተገቢ ባለመሆኑ ከዚህ በፊት ያለንን አቋም/ አቋማችንን እንገልጻለን” ብሏል።


ሊቀ ጳጳሱ መግለጫዎቻቸውን እና መመሪያዎቻቸውን ጸረ ተዋሕዶ በሆኑ ብሎጎች/ የጡመራ መድረኮች ላይ ማውጣታቸውን በጽኑዕ የነቀፈው መግለጫው “የብፁዕነታቸው ማንኛውም መልዕክት ያለ እሳቸው ፈቃድ ነው የወጣው እንዳይባል ምንም ዓይነት የጽሑፍ ማስተባበያ ያልሰጡ በመሆናቸው እና ይህንና ይህንን በመሳሰሉት የቤተ ክርስቲያን ችግሮች ምክንያት ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ለቤተ ክርስቲያን አንድነት ማምጣት ሳይሆን መለያየት ምክንያት ከመሆናቸው በተጨማሪ ለቤተ ክርስቲያን ክብር እና መቆርቆር እንደሌላቸው ከዚህ ተግባራቸው ተረድተናል። ስለዚህ … ቤተ ክርስቲያናችን አብራ የማትሠራ መሆኑን እና የፈፀሙትንም ተግባር የምንቃወመው መሆኑን ለሚመለከተው አካላት ሁሉ መግለፅ አስፈልጎናል። በአጠቃላይ የብፁዕነታቸው አካሄድ፦ 1. ቤተ ክርስቲያን የእግዚአብሔር ቤት መሆኑን የዘነጋ፣ 2. የቀደሙ ቅዱሳን አባቶቻችን በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ያስቀመጡትን የቤተ ክርስቲያን ቀኖና ቀስ በቀስ የሚሸረሽር በመሆኑ … ከብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ጋር አብሮ ለመሥራት የማንችል መሆኑን እና ለቤተ ክርስቲያናችን አስተዳዳሪ ለመላከ ኪዳን ቀሲስ ሳሙኤል ደጀኔ እና ለዲ. ስዩም ወ/አረጋዊ የተሠጠውን ሹመትም የማንቀበል መሆኑን እናስታውቃለን” ይላል።

የመግለጫውን ሙሉ ቃል ለማንበብ ይህንን ይጫኑ።

በተያያዘ ዜና አቡነ ፋኑኤል ወደ ሲያትል እንደሚሄዱ እና በእዛው ካሉ ሦስቱ ቤተክርስቲያናት ውስጥ የሚገኙ ምዕመናን በብርቱ እየታመሱ መሆኑን ከአካባቢው የሚገኙ ምዕመናን ገልጸውልናል። በሲያትል ከሚገኙት አብያተ ክርስቲያናት የአማኑኤል ቤተክርስቲያን፣ የቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን እንዲሁም የቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን ሊቀ ጳጳሱን ተቀብለው እንደሚያስተናግሩ ተገልጿል። በተለይ የአባኑኤል ቤተክርስቲያን እና የቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ከዚህ በፊት የነበሩትን አቡነ ኤውታጢዎስ ጋር ከፍተኛ የሆነ አለመግባባት እንደነበረባቸው የታወሳል። ነገር ግን በአሁን ሰዓት አቡነ ፋኑኤል የዋሽንግተን እና የካሊፎርኒያ አካባቢ ሊቀ ጳጳስ ነኝ ብለው በመጡ ጊዜ እነዚህ ቤተክርስቲያናት ተቀብለዋቸው እንደሚያስተናግዷቸው ከወዲሁ ተገልጿል፥ ነገር ግን በምዕመናኑ ከፍተኛ ተቃውሞ እንደሚገጥማቸው ይጠበቃል በተለይ የመምጣታቸው ዜና ከተሰማበት ጊዜ ጀምሮ በሲያትል የሚገኙ ወጣቶች በከፍተኛ ደረጃ ዝግጅት እያደረጉ እንደሆነ ይነገራል። አቡኑም ወደ ሲያትል በሚሄዱበት ወቅት የሃገረ ስብከቱን ስራ አስኪያጅ ለማስተዋወቅ እቅድ እንዳላቸውም ተያየዞ ተነግሯል በዚህም የተነሳ የአካባቢው ምዕመን ይበልጡኑ ቁጣውን የጨመረው የኃይለጊዮርጊስ ጥላሁን ከርሳቸው ጋር ወደአካባቢው የሚያደርገው ጉዞ እንደሆነ ይገመታል። ለነገሩ የአቡነ ፋኑኤልም ጉዞ ሲጀመር የኃይለጊዮርጊስን አብሯቸው መጓዝ እርሳቸውም ጨምሮ ፍቃዳቸው አልነበረም ይበላል፥ ነገር ግን የአቡነ ጳውሎስን ትዕዛዝ አክብረው በሚሄዱበት ሁሉ ይዘው በመሄድ የጉባኤ አርድዕትን ምስረታ፣ የአክሱምን ቤተ-መጽሐፍት ወመዘክር ግንባታና የገንዘብ ማሰባሰብም ወደ አካባቢው ለመውሰድ ቀድሞ የተወጠነ እንደሆነ ውስጥ አዋቂዎች ይናገራሉ።
ቸር ወሬ ያሰማን

የተዋሕዶ ቤተሰቦች በመላው ዓለም

No comments:

Post a Comment