Tuesday, January 15, 2013

ሰበር ዜና – በውጭ ለሚገኙት ብፁዓን አባቶች ጥሪ ተደርጎ ምርጫው እንዲካሄድ ተወሰነ

አርእስተ ጉዳይ፡-
His Grace Abune Natnael
ዐቃቤ መንበረ ፓትርያሪክ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል
  • የዕርቀ ሰላሙ ሂደት ከፓትርያሪክ ምርጫው ጎን ለጎን ይቀጥል ተብሏል
  • በውሳኔው ያልተስማሙት የቅ/ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ስብሰባውን ጥለው ወጡ!
  • የዐቃቤ መንበሩ አቋም በዕርቀ ሰላም እና ምርጫ መካከል ሲዋዥቅ ውሏል
  • ዐቃቤ መንበሩ ለምርጫው በቶሎ መፈጸም የፌዴራል ጉዳዮች ሚ/ርን እገዛ ጠይቀዋል
  • መንግሥት አስቸኳይ ስብሰባው በቶሎ እንዲፈጸም ይሻል
  • የምልአተ ጉባኤው አስቸኳይ ስብሰባ ነገ ያበቃል፤ ጋዜጣዊ መግለጫም ይሰጣል
በከፍተኛ ጥበቃ ሥር የተከናወነው የቅ/ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ አስቸኳይ ስብሰባ በውጥረት ተጀምሮ በውጥረት ለመጠናቀቅ ተቃርቧል፡፡ በስብሰባው ዋዜማ ባስነበብነው ዘገባ እንደተመለከተው÷ የፓትርያሪክ ምርጫው እና ዕርቀ ሰላሙ በተጓዳኝ እንዲካሄድ፣ ለምርጫው በሚደረግ ዝግጅትም በውጭ ለሚገኙት ብፁዓን አባቶች በሙሉ ጥሪ እንዲደረግላቸው ከፍተኛ ውዝግብ ከታየበት የምልአተ ጉባኤው ውሎ በኋላ ውሳኔ ላይ የተደረሰ መስሏል፡፡

‹‹የዕርቀ ሰላሙን ፍጻሜ ታግሠን የፓትርያሪክ ምርጫውን በውጭ ከሚገኙት አባቶች ጋራ በአንድነት እናካሂድ››
 በሚለው አቋማቸው የጸኑት የቅ/ሲኖዶሱ ዋና ጸሐፊ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል ስብሰባውን ትተው መውጣታቸው ተዘግቧል፡፡ እንደ አንዳንድ ምንጮች ጥቆማየስብሰባው ርእሰ መንበር ዐቃቤ መንበረ ፓትርያሪክ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል÷ በአንድ በኩል፣ ከብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቡነ ፊልጶስ ጀምሮ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ከፍተኛ ሓላፊዎች÷ የምርጫውን ሂደት በአግባቡ እንዳያከናውኑና በሌሎች አስተዳደራዊ ጉዳዮች ዕንቅፋት እየፈጠሩባቸው መኾኑን በመግለጽ መንግሥት ጣልቃ እንዲገባ ለፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር በጻፉት ደብዳቤ የጠየቁ ሲኾን በሌላ በኩል ደግሞ በምልአተ ጉባኤው ስብሰባ ላይ በዐቃቤ መንበርነታቸው የመቆየትና ከምርጫው በፊት የዕርቀ ሰላሙን ፍጻሜ የመጠበቅ ዝንባሌ በሚያሳዩ አቋሞች መካከል ሲዋዥቁ መዋላቸው ተገልጧል፡፡
ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል
የቅ/ሲኖዶሱ ዋና ጸሐፊ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል
ከኾነ ዋና ጸሐፊው ስብሰባውን ትተው በሚወጡበት ወቅት የልዩነት አቋማቸውን ለብዙኀን መገናኛ ይፋ እንደሚያደርጉ በግልጽ ተናግረዋል/ዝተዋል ተብሏል፡፡
ስብሰባው በነገው ዕለት ረፋድ ላይ መግለጫ በመስጠት እንደሚጠናቀቅ ተነግሯል፡፡ ስለ ስብሰባው ለብዙኀን መገናኛ የሚሰጠውን ጋዜጣዊ መግለጫ እንዲያዘጋጁ ሦስት ብፁዓን አባቶች ማለትም ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ፣ ብፁዕ አቡነ ገብርኤል እና ብፁዕ አቡነ አብርሃም ተመድበዋል፡፡
በውጭ ከሚገኙትና በዚህ ስብሰባ ላይ እንደሚካፈሉ ተጠብቀው ከነበሩት ዐሥር ያህል ብፁዓን አባቶች ስድስቱ (ብፁዕ አቡነ ማቲያስ ዘኢየሩሳሌም፣ ብፁዕ አቡነ ታዴዎስ – የካሪቢያን፣ ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል የዋሽንግተን ዲሲና ካሊፎርኒያ፣ ብፁዕ አቡነ ያዕቆብ የደቡብ አፍሪካ፣ ብፁዕ አቡነ ዘካርያስ የኒውዮርክ እና ብፁዕ አቡነ ኤዎስጣቴዎስ) ከአገር ውስጥም እንደ ብፁዕ አቡነ እንድርያስ እና ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ ያሉት አባቶች አለመገኘታቸው ታውቋል፡፡
ለቤተ ክርስቲያን ሰላምና አንድነት የሚበጅ በመኾኑ ለዕርቀ ሰላሙ ቅድሚያ እንዲሰጥ ከሚሰማው የአገልጋዮችና ምእመናን ተማኅፅኖ፣ ይህም በአብዛኞቹ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ተደግፎ ሳለ÷ የዕርቀ ሰላም ሂደቱ እንዲቀጥል የምርጫውም ዝግጅት እንዲጀመር፣ ለዚህም በውጭ ለሚገኙት አባቶች ጥሪ እንዲተላለፍ ቅ/ሲኖዶስ መወሰኑ በርካታ ጥያቄዎችን ያለመልስ የሚተው፣ የቤተ ክርስቲያናችንን ሰላምና አንድነት ለከፋ የመከፋፈል አደጋ የሚዳርግ ነው፡፡
ወዲያውም ደግሞ ከዋና ሥ/አስኪያጁ ለአስመራጭ ኮሚቴው አባላት የተጻፈው ደብዳቤ አስመራጮቹ ጥር 8 ቀን 2005 ዓ.ም በቅ/ሲኖዶሱ ጽ/ቤት ተገኝተው ሥራቸውን እንዲጀምሩ ያሳስባል፡፡ ማሳሰቢያውን በመቀበልና ባለመቀበል በያዟቸው አቋሞችና ውልውሎች የተመናመኑትና የሚዋልሉት የኮሚቴው አባላት የምልአተ ጉባኤው አስቸኳይ ስብሰባ በሚያበቃበት ነገ ጥር 8 ቀን በቁጥራቸው ተሟልተው ሥራቸውን ይጀምሩ ይኾን?
ተጨማሪ ዜናዎችን ይከታተሉየተዋሕዶ ቤተሰቦች በመላው ዓለም

No comments:

Post a Comment