Tuesday, June 4, 2013

ሰበር ዜና – ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የመ/ፓ/ጠ/ቤ/ክ ዋና ሥራ አስኪያጅ ኾነው ተመርጠዋል፤ ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የቅ/ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ኾነው ተሠይመዋል


የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በዛሬው ግንቦት ፳፯ ቀን ፳፻፭ ዓ.ም አምስተኛ ቀን ጥዋት የስብሰባ ውሎው የሰቲት ሁመራ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሉቃስን የቅ/ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ኾነው እንዲሠሩ ሠይሟል፤ የወላይታ ዳውሮ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስን ደግሞ የመንበረ ፓትርያሪክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ አድርጎ መርጧል፡፡
His Grace Abune Lukas
ብፁዕ አቡነ ሉቃስ
የቅ/ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ
በሕገ ቤተ ክርስቲያን አንቀጽ ፳፭ ንኡስ አንቀጽ ፩ እና ፬ መሠረት÷ ቅ/ሲኖዶስ በምልአተ ጉባኤውና በቋሚ ሲኖዶስ በየጊዜው በሚያደርገው ስብሰባ ላይ ሁሉ የሚነጋገርባቸውን ርእሰ ጉዳዮች የማዘጋጀት፣ ውሳኔዎቹን ሁሉ በተግባር ላይ መዋላቸውን የመከታተል ሥልጣንና ተግባር የብፁዕ ዋና ጸሐፊው ነው፡፡
በሕገ ቤተ ክርስቲያን አንቀጽ ፴ ንኡስ አንቀጽ ፱ መሠረት ብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጁ÷ ቅ/ሲኖዶስ ውሳኔዎን የማስፈጸም ሥልጣነ ክህነት፣ በቂ የትምህርት ደረጃና ችሎታ ያላቸውን ሦስት ሰዎች ለም/ሥራ አስኪያጅነት በዕጩነት ለቋሚ ሲኖዶስ አስቀርበው ቅ/ሲኖዶስ ሲስማማበት የማስመረጥና በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያሪኩ የማሾም ሥልጣን አላቸው፡፡ በዚሁ አንቀጽ ንኡስ ቁጥር ፲ መሠረት የመምሪያና የድርጅት ሓላፊዎችን እያጠኑና እያስመረጡ ፓትርያሪኩን በማስፈቀድ ይሾማሉ፡፡
His Grace Abune Mathewos
ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ
የመ/ፓ/ጠ/ቤ/ክ/ጽ/ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ
በሙሰኛና ጎጠኛ ቡድኖች ሤራ የምክነት ስጋት ያንዣበበት የተቋማዊ ለውጥ ዕቅዱ በሁለቱ ብፁዓን አባቶች አመራር የመስጠት ክሂልና የማስፈጸም ትጋት ከፍጻሜ ደርሶ የቤተ ክህነታችንን ትንሣኤ እንደሚያሳየን እናምናለን፡፡


ሁለቱ ብፁዓን አባቶች ለኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት መጽናትና መስፋፋት፣ ለቤተ ክርስቲያን ሀብትና ንብረት መጠበቅና መልማት፣ ለተቋማዊ ነጻነቷ መበከርና ለአንድነቷ መረጋገጥ እስከሠሩ ድረስ ሐራ ዘተዋሕዶ ከጎናቸው እንደምትቆም ትገልጻለች፡፡ለሁለቱ ብፁዓን አባቶቻችን መልካም የሥራ ዘመን እንመኝላቸዋለን!!
ተጨማሪ ዜናዎችን ይከታተሉ  



ምንጭ: ሐራ ዘተዋሕዶ
የተዋሕዶ ቤተሰቦች በመላው ዓለም

No comments:

Post a Comment