Thursday, June 27, 2013

ዶ/ር አባ ኀይለ ማርያም መለሰ የጠቅ/ቤ/ክ ም/ሥራ አስኪያጅ ኾኑ፤ የመምሪያዎችና ድርጅት ሓላፊዎች ምደባም ተደርጓል

  • ለተመደቡበት ሥልጣን ፍጹም የማይመጥኑ ሓላፊዎች መካተታቸው ነጋገረ
  • ‹‹የተቋማዊ ለውጡን ሂደት ከአመስጋኝ አማሳኞች ድለላ መከላከል ይገባል፡፡››
Dr Aba Hailemariam Melese
ዶ/ር አባ ኀይለ ማርያም መለሰ
የጠቅ/ቤ/ክ ም/ሥራ አስኪያጅ
ቋሚ ቅ/ሲኖዶስ ዛሬ፣ ሰኔ ፲ ቀን ፳፻፭ ዓ.ም ባካሄደው መደበኛ ስብሰባ ለመንበረ ፓትርያሪክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ም/ዋ/ሥራ አስኪያጅነት በቀረቡት ዕጩ ላይ በመስማማት በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያሪኩ እንዲሾሙ አድርጓል፤ የልዩ ልዩ መምሪያዎችና ድርጅቶች ዋና ሓላፊዎች ምደባም ተካሂዷል፡፡


በዚህም መሠረት የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ምክትል ዋና ዲን የኾኑት ዶ/ር አባ ኀይለ ማርያም መለሰ የመ/ፓ/ጠ/ቤ/ክ ጽ/ቤት ምክትል ሥራ አስኪያጅ ኾነው እንዲሠሩ መሾማቸው ታውቋል፡፡ ዶ/ር አባ ኀይለ ማርያም የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ም/ሥራ አስኪያጅ እንዲኾኑ ለቋሚ ሲኖዶሱ በዕጩነት ያቀረቧቸው ዋና ሥራ አስኪያጁ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ ናቸው፡፡ ዶ/ር አባ ኀይለ ማርያም ቀደም ሲል የመ/ፓ/ጠ/ቤ/ክ ስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ዋና ሓላፊ ኾነው ሠርተዋል፤ በበርካታ የብዙኀን መድረኰችም ቤተ ክርስቲያንን በመወከል በሚያደርጉት ተሳትፎ ይታወቃሉ፡፡
ይኹንና በስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ የነበራቸውን የአገልግሎት አፈጻጸም እንዲሁም በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀ መዛሙርትና በአስተዳደሩ መካከል በቅርቡ በተጋጋለውና እስከ አሁን እልባት ያላገኘው ውዝግብ አጉልቶ ካወጣቸው ጥያቄዎች አንጻር፣ የምክትል ሥራ አስኪያጅነት ሹመቱን በጥንቃቄ የሚመለከቱ ወገኖች፣ የሙሉ ጊዜትኩረትንና ከፍተኛ አቅምን በሚጠይቀው የቤተ ክህነቱ የመዋቅርና አሠራር ለውጥ ዶ/ር አባ ኀይለ ማርያም ያላቸው የማስተባበር፣ መምራትና የውሳኔ ሰጭነት ክሂል የሚፈተንበት እንደሚኾን ይናገራሉ፡፡
ብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጁ ለጠቅላይ ቤተ ክህነቱ አምስት መምሪያዎች፣ ለቤቶችና ሕንጻዎች አስተዳደር ልማት ድርጅት እንዲሁም ለቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የመረጧቸው ዋና ሓላፊዎችም በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያሪኩ ፈቃድ እንዲመደቡ አድርገዋል፡፡
Ato Tesfaye Wubshet
አቶ ተስፋዬ ውብሸት
የቀድሞው የጠቅ/ቤ/ክ ም/ሥ/አስኪያጅ የነበሩት አቶ ተስፋዬ ውብሸት የቤቶችና ሕንጻዎች አስተዳደር ልማት ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅ ኾነው እንዲሠሩ የተመደቡ ሲኾን በድርጅቱ ዋና ሥራ አስኪያጅነት ሲሠሩ የቆዩት መልአከ ብርሃን ፍሥሓ ጌታነህ የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ምክትል ዋና ዲን ኾነው ተሹመዋል፡፡ አቶ ተስፋዬ ውብሸት ወደ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ጽ/ቤት ከመምጣታቸው አስቀድሞ በሓላፊነት በመሯቸው የቤቶችና ሕንጻዎች አስተዳደር ልማት ድርጅት፣ የትንሣኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት በተከተሉት ሞያዊና አሳታፊ አሠራር ተቋማቱን ውጤታማና ትርፋማ ማድረጋቸው ይነገርላቸዋል፡፡
በቀጣይ ዋና ሥራ አስኪያጁን፣ ቀደምት አባቶች ያቆዩዋቸውን ነባር የሕንጻዎችና ቤቶች ሕጋዊ ይዞታ በማረጋገጥና የኪራይ ተመናቸውን በወቅቱ የገበያ ዋጋ በማሻሻል በፊት ያስመዘገቡትን ከፍተኛ ገቢ በበለጠ የማሳደግ፣ በአዳዲስ ይዞታዎች ግንባታዎችን በማስፋፋት በአመዛኙ በሙዳይ ምጽዋትና በሰበካ ጉባኤ አስተዋፅኦ የተገደበውን የቤተ ክርስቲያኒቱን አቅም የማጠናከር ሥራ ይጠብቃቸዋል፡፡ በርክበ ካህናት ቅ/ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ስብሰባ ‹‹ሥልጣነ ክህነት የላቸውም›› በሚል ከጠቅ/ቤ/ክ ምክትል ሥራ አስኪያጅነት የተነሡት አቶ ተስፋዬ በቢዝነስ ማኔጅመንት የመጀመሪያ ዲግሪ፣ በማርኬቲንግና ተግባረ እድ ደግሞ ዲፕሎማዎች እንዳሏቸው ተገልጧል፡፡
በርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ውሳኔ እንዲፈርስ የተደረገው የሕዝብ ግንኙነት መምሪያ ዋና ሓላፊ የነበሩት አቶ እስክንድር ገብረ ክርስቶስ የዕቅድና ልማት መመሪያ ዋና ሓላፊ ኾነው ተመድበዋል፤ የዚሁ መምሪያ ዋና ሓላፊ የነበሩት ቀሲስ ሰሎሞን ቶልቻየመንበረ ፓትርያሪክ ቤተ መጻሕፍት ወመዘክርና ቅርስ መምሪያን በዋና ሓላፊነት እንዲያስተዳድሩ ተመድበዋል፡፡ በአንዳንድ ተቺዎቻቸው ዘንድ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን እንዳላጠናቀቁ የሚነገርባቸው የቀድሞው የሕዝብ ግንኙነት መምሪያ የአሁኑ የዕቅድና ልማት መምሪያ ዋና ሓላፊ አቶ እስክንድር፣ በጋዜጠኝነት ዲፕሎማ ያላቸው ሲኾን በአንድ የግል ኮሌጅ በማኔጅመንት የርቀት ትምህርት በመከታተል ላይ እንዳሉና በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ በርቀት የሚከታተሉትን የቴዎሎጂ ትምህርት በዘንድሮው ዓመት እንደሚያጠናቅቁ ተዘግቧል፡፡
የመንበረ ፓትርያሪክ ቤተ መጻሕፍት ወመዘክሩንና ቅርስ መምሪያውን ለረጅም ጊዜ ተቆጣጥረው የቆዩት ሊቀ ዲያቆን ዳንኤል ሰይፈ ሚካኤል የውጭ ግንኙነት መምሪያውን በዋና ሓላፊነት እንዲመሩ ተመድበዋል፡፡ ሊቀ ዲያቆኑ÷ በአኀት አብያተ ክርስቲያንና ሮም ካቶሊክመካከል በተለያዩ ዙሮች በተደረጉ ኢኩሜኒካል ውይይቶች የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን በመወከል ከሚነጋገሩ ልኡካን ጋራ ሲሳተፉ ቆይተዋል፤ ነገረ ቤተ ክርስቲያንን በሚመለከቱ የጥናት ጉባኤዎች ጽሑፎችን በማቅረብና በመንፈሳዊ ኮሌጆች በማስተማር፣ በዐደባባይ ክብረ በዓላትም ወቅት በቋንቋ ምለሳና መድረክ አመራር ይታወቃሉ፡፡
ይኹንና ሊቀ ዲያቆን ዳንኤል÷ በሥራ አጋጣሚ በእጃቸው የገቡ ቅዱሳት ሥዕላትንና ድርሳናትን በድጅታይዚንግ መሰነድ (በቅርስ ጥናትና አጠባበቅ) ሰበብ የግል ጥቅማቸውን በማካበት በእጅጉ ይታማሉ፤ አመቺ መስሎ በታያቸው ወቅት ሁሉ ከፅልመታዊው ሙሰኛና ጎጠኛ ቡድን ጋራ አብሮና ተባብሮ ድጋፍ በመስጠት እንዲሁም ሁሉን ካልያዝኹ በሁሉ ካልተቀመጥኹ በሚለው ንፉግነታቸውም ክፉኛ የሚተቿቸው ጥቂቶች አይደሉም፡፡
የአስተዳደር መምሪያ ዋና ሓላፊ የነበሩት አቶ ተስፋ ጊዮርጊስ ኀይሉ ወደ ቊሉቢ ንዋያተ ቅድሳት ማደራጃ ሓላፊነት ተዛውረዋል፤ የማደራጃው ሓላፊ የነበሩት መዝገበ ጥበብ ቀሲስ ዮሐንስ ኤልያስ ደግሞ ቀድሞ በፈቃዳቸው ወደለቀቁት፣ ከሞያዊ ልምዳቸውና ከትምህርት ዝግጅታቸው አንጻር ፈጽሞ ወደማይመጥኑበት የአስተዳደር መምሪያ ዋና ሓላፊነት መመለሳቸው ተዘግቧል፡፡ እንደ መንበረ ፓትርያሪኩ የታመኑ ምንጮች ጥቆማ፣ አቶ ተስፋ ጊዮርጊስ ኀይሉ የተግባረ እድ ዲፕሎማ እንዳላቸው ሲጠቆም መዝገበ ጥበብ ዮሐንስ ግን የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን እንኳ በቅጡ አላጠናቀቁም፤ መዝገበ ጥበብ ያሰኛቸውም በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ዋና መዝገብ ቤት ለረጅም ጊዜ በሓላፊነት መቆየታቸው ነው፡፡
በዛሬው የቋሚ ቅ/ሲኖዶሱ ስብሰባ የተሰጠውን ሹመትና የተደረጉትን ምደባዎች በተመለከተ አስተያየታቸውን የተጠየቁ የመንበረ ፓትርያሪኩ ምንጮች፣ ባለፈው ሳምንት አዲሱን ዋና ሥራ አስኪያጅ እና የቅ/ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ከጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ሠራተኞች ጋራ ለማስተዋወቅ በተካሄደው መርሐ ግብር ላይ በሠራተኛው የቀረቡ ጥያቄዎችና ጥቆማዎች አስፈላጊው ትኩረት ተሰጧቸው እንደኾን ይጠራጠራሉ፡፡ ሠራተኛው በመርሐ ግብሩ ላይ ለቅ/ሲኖዶሱ ውሳኔዎች የሰጠው ድጋፍና ለተግባራዊነቱም ያሳየው ዝግጁነት ተገቢ ክብደት እንዲሰጠውም ያሳስባሉ፡፡
ሠራተኛው፡-
  • ቤተ ክርስቲያን÷ በአስተዳደራዊ መዋቅሩ ሥር ነቀል ለውጥ በማምጣት የታሰበውን ዕቅድ ለማሳካት የሚያስችል፣ በዕውቀት ዝግጅት ይኹን በሞያ ብቃት ተኣምር የሚሠራ፣ ሃይማኖታዊ እምነቱን ጠብቆ፣ ሥርዐተ እምነቱን አጽንቶ ይዞ ከቴክኖሎጂው ምጥቀት ጋራ የሚያራምዳት በርካታ የሰው ኀይል እንዳላት ያለውን መተማመን ተናግሯል፡፡ ዘመኑን ለዋጀው ወጣት ኀይል ዕድል መስጠት፣ አቅሙን በየደረጃው በስፋት ማደራጀትና ማንቀሳቀስ እንደሚገባ መክሯል፤ ራሱ ሠራተኛውም በብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጁ አመራር የሚጠበቅበትን ለመፈጸም ያለውን ዝግጁነት ገልጧል፡፡ ታዲያ የዛሬው ሹመትና ምደባ ሁሉ ያ ተኣምር ሠሪ አቅም/ሠራዊት በርግጥ መኖሩን አመላካች ነውን?
  • ቀጣዩ ዘመን÷ የቤተ ክርስቲያናችን ዋነኛ ተልእኮ በኾነው የስብከተ ወንጌል አገልግሎታችን መዳከምና የአደረጃጀት ውጤታማነት ማነስ ሳቢያ ባለፉት ኻያ ዓመታት ወደሌላ የኰበለሉ ከ7 – 10 ሚልዮን ምእመናን ወደ በረት የምንመልስበት፣ ያሉትን በዕውቀትና በእምነት የምናጠናክርበት፣ የተዘጉ አብያተ ክርስቲያን የሚከፈቱበትና ልማትየሚስፋፋበት እንደኾነ ሠራተኛው ያለውን ተስፋ ገልጧል፡፡ ለዚህም በቂ በጀት እንዲመደብና በሠለጠነ የሰው ኀይል የተደራጀ አቅም እንዲገነባ ጠይቋል፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያሪኩም ቤተ ክርስቲያን ትልቁን በጀት መመደብ ያለባት ለስብከተ ወንጌል ሥራ እንደኾነ ያላቸው እምነት አስታውቀዋል፡፡ እውን የዛሬው ሹመትና ምደባው ይህ የሠራተኛው ተስፋ ይደርስ ይፈጸም ዘንድ የሚያስችል ነውን?
  • የቤተ ክህነታችን መሠረታዊ ችግር የአስተሳሰብም የሥርዐትም እንደኾነ ሠራተኛው አስቀምጧል፡፡ ይኸውም በአንድ በኩል ሠራተኛው÷ በትምህርት ዝግጅቱና ሞያዊ ብቃቱ ላይ በመተማመንና በዚያ ላይ በመመሥረት የሚቀጠርበትና ስኬት የሚያስመዘግብበት ሳይኾን በየጊዜው በሚለዋወጡ ሓላፊዎች ላይ ለመንጠልጠል የራሱን ዘዴ ሲፈልግ፣ አማላጅ ሲልክና ሲለማመን የሚስተዋልበት ነው፡፡ በሌላ ወገን ደግሞ ተቋማዊ አሠራሩ ድርሻቸውን በሚገባ ለሚወጡ ሓላፊዎች ማበረታቻና ዋስትና የሚሰጥ፣ ከተወላጅነት ተዋፅኦ አንጻር እንኳ አድልዎ የገነነበትና ስብጥር የማይታይበት ነው፡፡ የሠራተኛው ጥቆማ እንደሚያሳየው፣ ከጠ/ቤ/ክህነቱ 18/19 መምሪያዎችና ድርጅቶች በ16ቱ ላይ ያለው የዋና ሓላፊዎች ምደባ ይህን አቤቱታ በጉልሕ የሚያረጋግጥ ነው፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያሪኩ አንድን ግለሰብ በሞያውና በሥራው እንጂ በማንነቱ (ተወላጅነቱ) እንደማይመዝኑ በተደጋጋሚ ተናግረዋል፤ ብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጁም በትውውቅ መርሐ ግብሩ ላይ በትክክል እንዳስቀመጡት፣ ‹‹በቤተ ክርስቲያን ሥርዐት ከተጠራን አገልግሎታችን በመጠኑም ቢኾን የተሻለ መኾን አለበት፤ የሚያዝዘን ሥርዐታችንና ሕጋችን እንጂ ሥልጣናችን አይደለም፤›› ብለዋል፡፡
  • ከዚህ አኳያ የሚዘረጋው ተቋማዊ ሥርዐት÷ የአገልጋዩ ሹመትና ምደባ በትውፊታዊው የጉባኤ ቤትና በመንፈሳዊ ኮሌጅ እንዲሁም በዘመናዊ ሞያ ባደረገው ዝግጅት የሚመዘንበት፣ የካህኑ ‹‹መስቀልና ሥራ የሚከበርበት››፣ ሥራውና ሠራተኛው የሚገናኝበት፣ የተገለሉ/የተበደሉ ሊቃውንት የሚካሱበት፣ የተወላጅነት ስብጥሩም ተጠብቆ ‹‹ወንዝ ለወንዝ ቀላይ ለቀላይ የሚሄደው›› የጎጠኝነት አስተሳሰብ የሚጠፋበት እንዲኾን ጠይቋል፡፡ የዛሬው ሹመትና ምደባ ይህን በተጨባጭ የሚያሳይና በቀጣይም ተስፋ የሚሰጥ ይኾን ወይስ ሠራተኛው እንዳሳሰበው ‹‹አለባብሰው ቢያርሱ. . .››?
  • ቤተ ክህነቱ ከውጭ በሙስና ተገምግመው የተባረሩ ግለሰቦች የሚቀጠሩበት ‹‹የሙስና ምሽግ›› ኾኖ እንደቆየ ሠራተኛው በምሬት ተናግሯል፡፡ አሁን በሙስናና ብልሹ አሠራር ላይ የተያዘው አቋም ለዓመታት የተገፉ ካህናትና ሊቃውንት እምባ የሚታበስበት፣ በተበደሉበት እውነት ኣርነት የሚወጡበት ነው ብሎ እንደሚያምን አመልክቷል፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያሪኩ ሙስናና ብልሹ አሠራርን በመጸየፍ ከቤተ ክህነቱ ተጠራርጎ መጽዳት እንዳለበት የሰጡት መግለጫ መላውን ካህናትና ምእመናን እንዳስደሰተ ሠራተኛው በመርሐ ግብሩ ላይ መስክሯል፡፡ እነ አባ ሠረቀ ብርሃን ወልደ ሳሙኤል ሳይቀሩ፣ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያሪኩ በመንበረ ፕትርክናው ከተቀመጡበት ጊዜ ጀምሮ የሚያስተላልፏቸው መልእክቶች ‹‹ወቅታዊና እጅግ ወርቃማ›› መኾናቸውን አልሸሸጉም፡፡
  • በአንጻሩ ደግሞ እንዲህ ያሉ የአድርብዬ አመስጋኞች  በለውጡ አተገባበር ሂደትአማሳኞች  እንዳይኾኑ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያሪኩና ብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጁ እንዲነቁባቸው ሠራተኛው የቅድሚያ ማስጠንቀቂያ ሰጥቷል፡፡ ለራሳቸው ምቾትና ድብቅ ዓላማ ሲሉ የለውጡን ሂደት ከማምከን ወደኋላ የማይሉ አማሳኞች መኖራቸውን በውል የተረዳ የሚመስለው የብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጁ የማጠቃለያ መልእክትም‹‹የዛሬው መተዋወቅ ሆሳዕና ኾኖ በቀጣዩ ዕለተ ዐርብ እንዳይኾን ለሁላችሁም አደራ እላችኋለኹ፤›› የሚል ነበር፡፡ እንዴት ነው ታዲያ የዛሬው ሹመትና ምደባ የብፁዕ ዋና ሥራ አስኪያጁን ስጋት የሚያስቀር ነውን? እንደ መዝገበ ጥበብ ዮሐንስ ኤልያስ ያሉ የለየላቸው አማሳኞች ለዚያውም በአስተዳደር መምሪያ ዋና ሓላፊነት ደረጃ የተካተቱበት አይደለምን? ከሹመቱ ተገቢነትና ከሥራው ውጤታማነት ይልቅ ለተሿሚው ምንዳና ምቾት ቅድሚያ የምንሰጥበት ሥር የሰደደ ስሕተታችን ይታረም ይኾን?
ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያሪክ አቡነ ማትያስ ለዜና ቤተ ክርስቲያን መጽሔት በሰጡት ቃለ ምልልስ እንዳሉት፣ ለውጡ ቀስ በቀስ ደረጃ በደረጃ እንጂ በአንድ ቀን ማምጣት እንደማንችል ይታወቃል፤ ለውጡን ለመጀመር በምናደርገው ዝግጅት ግን በትክክለኛው ጎዳና ላይ መኾናችንን ማረጋገጥ ያስፈልገናል፡፡
ከሠራተኛው ጋራ በተደረገው የትውውቅ መርሐ ግብር ላይ ዋና ሥራ አስኪያጁ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ ያደረጉት ንግግር ከሚያስተላልፈው ጠቃሚ መልእክት አንጻር ሙሉ ቃሉን በቀጣይ እናቀርበዋለን፡፡ ይከታተሉን፡፡
ምንጭ: ሐራ ዘተዋሕዶ
የተዋሕዶ ቤተሰቦች በመላው ዓለም

No comments:

Post a Comment