Tuesday, June 16, 2015

ሰበር ዜና - ከእዚህ በፊት በሰጣቸው ትምህርቶቹ በርካታ ጥያቄዎች የተነሱበት በጋሻው ደሳለኝ ሉንድ፣ስዊድን ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሌላ ትልቅ ውዝግብ ፈጠረ።።''በጋሻው ስዊድን የገባው በአውሮፓ የምትገኘውን፣በሀገር ቤትም ሆነ በውጭ አባቶች የምትመራውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያንን ለማወክ ያለመ ተልኮ ይዞ ነው'' አውሮፓ የሚኖሩ አባቶች እና ምዕመናን።(የደብዳቤ እና የፎቶ ቅጅዎች ተያይዘዋል)



           አቶ በጋሻው ዛሬም የውዝግብ ማዕከል ሆኗል
 


  • ወደ ሉንድ፣ስዊድን የገባበት ሰነድ በራሱ አወዛጋቢ ሆኗል፣
  • ሉንድ፣ስዊድን የሚገኘው ቴዎሎጂ ዩንቨርስቲ የግለሰቡን ወደ ስዊድን መምጣት እንደሚያውቅ ተደርጎ የተገለፀውን ደብዳቤ ሐሰት መሆኑ እየተነገረ ነው፣
  • ዩንቨርስቲው ስለጉዳዩ እንደማያውቅ ለማወቅ ተችሏል፣
  • በአውሮፓ የሚኖሩ በሀገር ቤትም ሆነ በውጭ አባቶች ስር የሚገኙ አጥብያ አብያተ ክርስቲያናት ጥንቃቄ እንዲያደርጉ የበጋሻውን አወዛጋቢ የሀገር ቤት ታሪክ የሚያውቁ አባቶች እና ምዕመናን በብርቱ እያስጠነቀቁ ነው፣
  •  ''ከሀገር ቤት አቡነ ማትያስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ እና ቋሚ ሲኖዶስ እንዳስተምራችሁ ፍቃድ ሰጥተውኛል'' በጋሻው ለሉንድ፣ስዊድን ምዕመናን የነገራቸው።
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በበርካታ የቤተክርስቲያኒቱ ጉባኤያት ላይ ሁከት በመፍጠር፣በአደባባይ የቤተ ክርስቲያኒቱን አባቶች በማጥላላት እና በአስተማራቸው ትምህርቶች አፅራረ ቤተ ክርስቲያን ይዘት ከሐዋሳ እስከ ጎንደር ከአዲስ አበባ እስከ ሐረር ባሉ አያሌ አጥብያ አብያተ ክርስቲያናት በሚገኙ  አባቶች ከመድረክ ላይ እንዳያስተምር በሀገረ ስብከት ሊቃነ ጳጳሳት፣የደብር አለቆች እና ምዕመናን የታገደው በጋሻው ደሳለኝ ስዊድን፣ሉንድ አንድ ሰንበት በተጭበረበረ መንገድ መድረክ በግድ ነጥቆ ማስተማሩ ምእመናንን በእጅጉ አስቆጥቷል።

በጋሻው መድረኩን በጉልበት ከነጠቀ በኃላ መድረክ ላይ ቆሞ 

ሉንድ፣ስዊድን ደብረ ምጥማቅ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ከሁለት ሳምንታት በፊት የግንቦት 21 የደብረ ምጥማቅ የቅድስት ድንግል ማርያምን በዓል ለማክበር ዝግጅት ይጀምራሉ።በእዚህ መሰረት ከስዊድን እና ኖርዌይ የሚገኙ አባቶች በአቡነ ኤልያስ ተመድበው ለአገልግሎት ይሄዳሉ።ጉባኤው ሲካሄድ ቀደም ብሎ በጋሻው በቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ በማገልገል ላይ በሚገኘው ዲ/ን ያሬድ አማካይነት የግብዣ ደብዳቤ ተልኮለት ስዊድን ገብቶ ነበር።ሆኖም ግን ምእመኑን በመፍራት በዕለቱ በቦታው ዝር ሳይል ይቆያል።

በሳምንቱ ግን በቦታው የዶክትሬት ዲግሪውን በመስራት ላይ በሚገኘው እና ያለውን ትርፍ ጊዜ በሙሉ በቤተ ክርስቲያኒቱን በነፃ በቅዳሴ፣በማስተማር እና ምዕመናንን በመምከር የሚያገለግለው ቀሲስ መንግሥቱ በቦታው የዕለቱን ትምህርት ለመስጠት ሲዘጋጅ ከበጋሻው በኩል ትዕቢት በተሞላበት እና የቤተ ክርስቲያንን ስርዓት ፈፅሞ በተፃረረ መልክ ካህኑን እላፊ ንግግሮችን ከመናገሩም በላይ መርሃ ግብሩን የሚመራው እና ቀደም ብሎ በጋሻውን ለማስመጣት ደብዳቤዎችን መላኩ የተነገረለት ዲ/ን ያሬድ የድምፅ መናገርያውን ከካህኑ ነጥቆ ለበጋሻው ሲሰጥ እና ቀሲስ መንግስቱ እና ምዕመናን ቤተ ክርስቲያኑን ጥለው እያለቀሱ ሲወጡ ተስተውሏል።ይህ ጉዳይ የበርካታ ምእመናንን ልብ ያሳዘነ ከመሆኑም በላይ ጉዳዩ በእዚህ ሳይቆም  ለቅዳሜ ሰኔ 6/2007 ዓም አሁንም በድጋሚ ምእመናንን የሚጠራ ፖስተር ተዘጋጅቶ እንዲሰራጭ መደረጉን ለማወቅ ተችሏል።



በሌላ በኩል ከእዚሁ ከሉንድ፣ስዊድን በዲያቆን ያሬድ አቀናባሪነት'' በጋሻው መጥቶ ያስተምራችሁ'' የሚል ይዘት ያለው ደብዳቤ ኖርዌይ እና ስዊድን ለሚገኙ አጥብያዎች የዲያቆን ያሬድ ምክትል መሆኑ በሚነገረው አቶ ሰለሞን በተባለ ግለሰብ የተፈረመ ደብዳቤ የተላከ መሆኑ እና የእዚሁ ደብዳቤ መላክ በስዊድንም ሆነ በኖርዌይ ባሉት አጥብያ አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ ተቀባይነት ካለማግኘቱም በላይ ጉዳዩን የሰሙ ምዕመናን በሁለቱ ሃገራት ለሚገኙ የመንግስት የፀጥታ አካላት ማሳወቅ እና በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ አብያተ ክርስቲያን ምዕመናን ዘንድ ከፍተኛ ሁከትን ለመፍጠር ያለመ እና ከእዚህ በፊት በሀገር ቤት የተፈጠሩትን ችግሮች በቪድዮ አስደግፈን ማቅረብ ይገባናል ሲሉ ተደምጧል።በአውሮፓ ሕግ መሰረት የእዚህ አይነት ሪፖርት የቀረበበት ግለሰብ በመላው አውሮፓ እስከመቸውም ድረስ እንዳይገባ የመታገድ ዕድል ሊገጥመው ከመቻሉም በላይ በሌሎች ሃገራትም ተመሳሳይ ዕጣ ሊደርሰው ይችላል ሲሉ የሕግ ባለሙያዎች ይገልፃሉ።ይህ በእንዲህ እንዳለ በእዚሁ ሉንድ አጥብያ ያሉት በጋሻውን ያስመጡ ግለሰቦች አጥብያውን በሀገር ቤትም ሆነ በውጭ ካሉ አባቶች የመነጠል እና ሌላ ፈቃድ አውጥቶ ምዕመናንን የመክፈል ሥራ ለመስራት ከቀደመ ጀምሮ የያዙት ዕቅድ መሆኑን መረጃዎቹ ያመላክታሉ።


ይህ በእንዲህ እንዳለ በጋሻው በጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ አቡነ ማቴዎስ ሰኔ 6/2006 ዓም የተፈረመ እና በቋሚ ሲኖዶስ የፀደቀ ነው ብሎ እያሳየ ያለው ደብዳቤ ትክከለኛነት መጣራት ያለበት ከመሆኑም በላይ ደብዳቤው ትክክል  ሆኖም ቢሆን ይህ ጉዳይ በሀገር ቤት ባሉ ምእመናን ዘንድ ከፍተኛ ጥያቄ  እንደሚያስነሳ ሳይታለም የተፈታ ነው።

ከእዚህ በተጨማሪ በሉንድ፣ስዊድን የሚገኘው የቴዎሎጂ ትምህርት ዩንቨርሲቲ የበጋሻውን መምጣት እና በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ስር የሚደረገውን ጉባኤ እንደሚያውቅ ተደርጎ በስዊድንኛ የተፃፈው ወደ ስዊድን እንዲገባ ቪዛ የተጠየቀበት ደብዳቤ ላይ የተገለፀ ሲሆን ዩንቨርስቲው ምንም የሚያውቀው ነገር የሌለ መሆኑን እና ምንም አይነት ተሳትፎ እንዳላደረገ ለማወቅ ተችሏል።


ባጠቃላይ በሀገር ቤት በበርካታ ትምህርቶቹ ከፍተኛ ተቃውሞ የተነሳበት እና ከብዙ መድረኮች የሀገረ ስብከት ሊቃነ ጳጳሳት፣የደብር አለቆች፣የሰንበት ትምህርት ቤቶች እና ምዕመናን ዘንድ የተነቀፈው በጋሻው በሉንድ የቤተ ክርስቲያንን ስርዓት ባልጠበቀ እና መናገርያውን በመንጠቅ በተደረገ ሸፍጥ ለማስተማር መድረክ ላይ መውጣቱ አንድ ሊባል የሚገባ እና ሕግ እና ስርዓት ባለበት አውሮፓ ውስጥ ይህ መፈፀሙ እጅግ አሳፋሪ መሆኑን ምዕመናን በቁጭት ይገልፃሉ። 

በመጨረሻም የቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ግራና ቀኝን የመመልከት እና የዛሬ የህዝብ መሰብሰብን ብቻ ሳይሆን የነገ የምዕመናንን መድረሻ የማገናዘብ ፀጋው የተሰጣቸው በሀገር ቤትም ሆነ በውጭ ሲኖዶስ የሚገኙ አባቶችን በበጋሻው ''ሀገር ቤት ጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ አቡነ ማቴዎስ እንዳስተምር ደብዳቤ ሰጥተውኛል'' የሚል መነሻ ብቻ በመያዝ ስለ መምህሩ በቂ መረጃ ሳይዙ ወደ ማናቸውም አይነት ውሳኔ እንዳይሄዱ ምዕመናን ተማፅኖ እያቀረቡ ነው። የእዚህ አይነቱ አወዛጋቢ እና በበርካታ ትምህርቶቹ ከፍተኛ ወቀሳ የደረሰበትን ግለሰብ መድረክ መስጠት  በአንፃራዊ ሰላም የምትገኘውን በአውሮፓ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት እና ምዕመናንን  አንድነት እና ፍቅር እንዳያናጋ ከፍተኛ ጥንቃቄ መውሰድ እንደሚገባቸው ለብፁዓን አባቶች በስልክ እና በአካል  ምዕመናን እየገለፁ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል።

እግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያናችንን ይጠብቅልን።
ምንጭ: ጉዳያችን
የተዋሕዶ ቤተሰቦች በመላው ዓለም

No comments:

Post a Comment