ገድለ ቅዱሳን

አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ!


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር
   ኢትዮጵያዊው ሊቅና ጻድቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ከቅዱስ ያሬድ ቀጥሎታላቅ ቦታ የያዘ ኢትዮጵያዊ ሊቅ ነው፡፡  አባ ጊዮርጊስ የተወለደው 1357. በወሎ ክፍለ ሀገር በቦረና ወረዳ ሰግላ በተሰኘች ቦታ ነው፡፡ ወላጆቹ ልጅስለሌላቸው ዘወትር እያዘኑ ወደ እግዚአብሔር ይጸልዩ ነበር፡፡ አባ ጊዮርጊስየተወለደው በቅዱስ ዑራኤል አብሳሪነት መሆኑን ድርሳነ ዑራኤልይተርክልናል፡፡ አባቱ ሕዝበ ጽዮን እናቱ አምኃ ጽዮን ይባላሉ፡፡  አባቱ ጠቢብናየመጻሕፍት ዐዋቂ፤ የእግዚአብሔር ወዳጅና በቤተ መንግሥት በነበረችውድንኳን “ሥዕል ቤት” ከሚያገለግሉ ካህናት ወገን ሲሆን የሰግላ ሀገረ ገዥምነበር፡፡  የአባ ጊዮርጊስን እናት እምነ ጽዮን ከወለቃ /የዛሬው ደቡብ ወሎ፣ ቦረና/ ከሹማምንት ወገን የሆነች ደግ ሰው ነበረች፡፡

 አባ ጊዮርጊስ በመጀመርያ እናቱ ፈሪሐ እግዚአብሔርን እያስተማረች በጥበብና በዕውቀት አሳደገችው፡፡ አባ ጊዮርጊስ የመጀመርያውን የቤተ ክርስቲያንትምህርት የተማረው ከአባቱ ነበር፡፡ ምክንያቱም አባቱ የመጻሕፍት ሊቅ መሆኑንስንመለከትና ገድሉም አባ ጊዮርጊስን በተመለከተ “ወሶበ ልሕቀ ሕቀ ወሰዶ ኀበጳጳስ ወሴሞ ዲያቆን” የሚለውን ስናጤነው አባቱ የመጀመርያውን ደረጃትምህርት ካስተማረው በኋላ በ1341 ዓ.ም ወደ ኢትዮጵያ ከመጡትና እስከ ዐፄ ዳዊት ዘመነ መንግሥት ጳጳስ የነበሩት ከአቡነ ሰላማ መተርጕም ዘንድ ወስዶዲቁና አሹሞታል ማለት ነው፡፡
                                             
  ዲቁና ከተቀበለ በኋላ ለትምህርት ወደ ሐይቅ እስጢፋኖስ ተላከ፡፡ ወደ ሐይቅየገባው በዐፄ ዳዊት ዘመነ መንግሥት መሆኑን ገድሉ ይገልጣል፡፡ ሐይቅእስጢፋኖስ የተለያዩ ሊቃውንት የሚገኙባት፣ በብዙ መጻሕፍት የተሞላችናዙሪያዋን በሐይቅ በመከበቧ የተማሪን ሳብ ለማሰባሰብ አመቺ የሆነች ቦታናት፡፡ አባ ጊዮርጊስ በሐይቅ እስጢፋኖስ ትምህርት አልገባው ብሎ ለሰባትዓመታት ተቀምጦ ነበር፡፡ አብረውት የሚማሩት ተማሪዎች “ይህ ትምህርትየማይገባው ስለ ምንድን ነውበእርሱ ኃጢአት ነው ወይስ በወላጆቹ ?” ይሉትነበር፡፡ በዚያ ጊዜ የሐይቁ መምህር የነበረው ዐቃቤ ሰዓት ሠረቀ ብርሃን ለአባቱልጅህ ትምህርት አይገባውምና የቤተ መንግሥት ነገር አስተምረው” ብሎመለሰው፡፡ አባቱ ሕዝበ ጽዮን ግን “አንድ ጊዜ ለእግዚአብሔር ሰጥቼዋለሁ፤እዚያው ገዳሙን ያገልግል” ብሎ እንደ ገና ላከው፡፡

 አባ ጊየርጊስ በቀለም ትምህርት እንዲሰንፍ ምክንያት የሆነው ከመማር ይልቅ በሥራ እየደከመ የገዳሙን አባቶች መርዳትና ብሕትውናን ይማርከው ስለ ነበር ነው፡፡ በገዳሙ  እህል በመፍጨት ያገለግል ነበር ፡፡ አባ ጊዮርጊስ እህልይፈጭበት የነበረውን የድንጋይ ወፍጮ እስከ አሁን በገዳሙ አለ፡፡

  አባ ጊዮርጊስ ዕውቀት ስለ ተሠወረውና ጓደኞቹ በትምህርት ሲቀድሙት ባየ ጊዜ እጅግ አዘነ፡፡ ስለዚህም 
በጾምና በጸሎት ወደ እግዚአብሔር መጮኽ ጀመረ፡፡ ሁልጊዜም በሥዕለ ማርያምሥር እየተንበረከከ “የአባቶቻችን አምላክ፣ የምህረት ጌታ፣ ሁሉን በቃልህ የፈጠርክ፣ ሰውንም በረቂቅ ጥበብ የፈጠርክ አቤቱ አንተ ከልዑል ጌትነትህ ጥበብን ስጠኝ በእውነትም አትናቀኝ አኔ ባርያህ ነኝና የባርህም ልጅ ነኝና” እያለ በጠለቀ ተመስጦ ልቦና እንባን በማፍሰስ ይጸልይ ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ በነሐሴ 21ኛው ቀን እመቤታችን ተገለጠችለትና «አይዞህ ዕውቀት የተሠወረብህትምህርት ስለማይገባህ ሳይሆን የእግዚአብሔር ድንቅ ሥራ እንዲገለጥ ነውናታገሥ» አለችው፡፡ ጽዋዕ ልቦናም አጠጣችው፡፡

 ከዚህ በኋላ በሐይቅ እስጢፋኖስ የዜማ የቅኔና የመጻሕፍትን ትርጓሜትምህርቱን በሚገባ ተምሮ አጠናቀቀ፡፡ በዕውቀቱም ቀድሞ የሚያውቁት ሁሉይደነቁበት ነበር፡፡ አባ ጊዮርጊስ የያሬድን ዜማ ከአቡነ ሳሙኤል ዘጋርማእንደተማረው ገድሉ ይነግረናል፡፡ በዚያ ዘመን በዐፄ ዳዊት አማካይነት በሰሜንኢትዮጵያ የያሬድ ድጓ ዋና ማዕከል በሆነው በደብረ ነጎድጓድ ተሾሞ ያስተምር ነበር፡፡

  የማስተማር ሥራውን የጀመረው በዚያው በሐይቅ እስጢፋኖስ መሆኑን ገድሉበሚከተለው መልኩ ይገልጠዋል “ወአብርሃ ለቤተ ክርስቲያን እንተ ተሐንጸትበሐይቅ ባሕር፣ ወእም አሜሃ አሐዙ ይስአሉ እም ኀቤሁ ኩሎሙ ሰብአ ሀገርቃለ መጻሕፍት ወትርጓሜሆሙ፣ ወኩሉ ቃለ ማኅሌት፡፡

 ከሐይቅ በኋላ በዚያ ዘመን ሸግላ በመባል ትጠራ ወደ ነበረችው ወደ ትውልድሀገሩ ወደ ጋሥጫ ተጓዘ፡፡

  አባ ጊዮርጊስ ወደ ሸግላ ሲመጣ አባቱ በጣም አርጅቶና መንኩሶ ነበር፡፡ስለዚህም በአባቱ እግር ተተክቶ በቤተ መንግሥቱ ያለችውን ሥዕል ቤትእንዲያገለግል ወደዚያው አስገቡት፡፡ በቤተ መንግሥቱም የንጉሡን ልጆችከማስተማሩም በላይ በቤተ መንግሥቱ ዙርያ ከነበሩት ሊቃውንት መካከል አባጊዮርጊስ አንዱ ነበር፡፡ በአንድ ወቅት ግብፃዊው ጳጳስ አቡነ በርተሎሜዎስሥላሴን አንድ ገጽ” ብለው ያምናሉ ተብለው በተከሰሱ ጊዜ ነገሩን እንዲያጣሩከተመረጡት ከቄስ ሐፄ ተከሥተ ብርሃንና ከሐይቁ መምህር ከዐቃቤ ሰዓት ዮሴፍጋር አብሮ ተልኮ ነበር፡፡ እነዚህ ሦስት አበው ጳጳሱን ካነጋገሩ በኋላ ክሱ ውሸትመሆኑን በማረጋገጥ ስለ ምሥጢረ ሥላሴ የሚገልጠውን የጳጳሱን እምነትበጽሑፍ ይዘው መጡ፡፡

 በቤተ መንግሥቱ በነበረ ጊዜ የንጉሡን ልጆች ይስሐቅን፣ ቴዎድሮስን፣እንድርያስን፣ ሀብተ ኢየሱስን፣ ሕዝቅያስን፣ ኢዮስያስን፣ ዘርዐ ያዕቆብንና ሴትልጁን እሌኒን በምግባርና በሃይማኖት ቀርጿቸዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል ዘርዐያዕቆብ በድርሰቱ ሲመስለው ቴዎድሮስ ደግሞ በሕይወት መስሎታል፡፡ ዐፄዳዊት የአባ ጊዮርጊስን ሊቅነትና መልካም ሥነ ምግባር በሚገባ ስላወቀ በጋብቻሊዛመደው ወዶ ስለነበር ልጁን እንዲያገባ ዘወትር ይጠይቀው ነበር፡፡ አባጊዮርጊስ ግን በድንግልና ጸንቶ ለመኖር እንደሚፈልግ ከመግለጽ አልተቆጠበም፡፡የዐፄ ዳዊት ጥያቄ ስለበዛበት ወደ አቡነ በርተሎሜዎስ ሄዶ ቅስናን ከተቀበለበኋላ ወዲያው መነኮሰ፡፡

   ከመነኮሰ በኋላ ወደ ሸግላ በመምጣት ለነገሥታትና በቤተ መንግሥቱ ለነበሩካህናት እንዲሁም በቤተ መንግሥቱ ለነበሩ ታላላቆች፣ ለንቡራነ እድናለመኳንንት፣ ለመሳፍንትና በቤተ መንግሥቱ ለነበሩ ባለሟሎች ሁሉ መምህርሆነ፡፡

 አባ ጊዮርጊስ በሸግላ በነበረ ጊዜ በወባ በሽታ ታምሞ ሊሞት ደርሶ እንደ ነበርገድሉ ይናገራል፡፡ ታምሞ በነበረ ጊዜ አንድ ሌሊት ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስጳውሎስ ተገልጠውለት “ከእኛ ጋር ትኖር ዘንድ ልንወስድህ” መጣን አሉት፡፡እርሱም “የድርሰት ሥራዬን ሳልሠራና እግዚአብሔርንም አብዝቼ ሳላመሰግነውአሁን አትውሰዱኝ” ሲል ለመነ፡፡ እነርሱም ልመናውን ተቀብለውት ከሕመሙፈውሰውት ሄዱ፡፡ ለዚህም ይመስላል ከበሽታው እንደ ተፈወሰ ወድያውየድርሰት ሥራውን የጀመረው፡፡

 የመጀመርያ መጽሐፉን ጽፎ እንደ ጨረሰ ጠፍቶበት እንደ ነበር ገድሉይተርካል፡፡ በቤቱ ውስጥ የነበሩትን መጻሕፍት ሁሉ እያገላበጠ ቢፈልገውምሊያገኘው አልቻለም፡፡ አንድ ቀን በቤተ ክርስቲያን ሌሊት በአገልግሎት ላይእያለ እመቤታችን ተገልጣ “ለምን አስቀድመህ ሳትነግረኝ ጻፍክ?” ስትልጠየቀችው፡፡ እርሱም «አንቺን ደስ ያሰኘሁ መሰሎኝ ነውና ይቅር በይኝ» ሲልመለሰላት፡፡ ከዚህ በኋላ የድርሰት ሥራውን ፈቅዳለት ተሠወረችው፡፡ “ወሶቤሃበርሃ ልቡ ከመ ፀሐይ ወሐተወ ውስተ ኅሊናሁ ባሕረየ መለኮት፤ ወነጸረ ኩሎኅቡአት - ከዚህ በኋላ ልቡ በራለት፣ ኅሊናውም ነገረ መለኮትን ዐወቀ፡፡የተሠወረውንም ሁሉ ተመለከተ” ይላል ገደሉ፡፡

  የመጀመርያው ድርሰቱ አርጋኖን  የተሰኘውና በቅኔ ስለ እመቤታችን ቅድስትድንግል ማርያም የሚያመሰግነው መጽሐፉ ነው፡፡ ስለ አርጋኖን ድርሰቱ ገድሉበሚከተለው መንገድ ይገልጠዋል “ወሰመዮ በሠለስቱ አስማት ዘውእቶሙአርጋኖነ ውዳሴ፣ ወመሰንቆ መዝሙር ወእንዚራ ስብሐት - በሦስት ስሞችምሰየማቸው እነርሱም አርጋኖነ ውዳሴ፣ መሰንቆ መዝሙርና እንዚራ ስብሐት ይባላሉ፡፡

  እመቤታችን አርጋኖንን ስለ ወደደችለት ዚማት በሚባለው ሀገር በነበረ ጊዜከድርሰቶችህ ሁሉ እንደ አርጋኖን የምወደው የለም”  ብላዋለች፡፡ ዐፄ ዳዊትምድርሰቱን በጣም ከመውደዱ የተነሣ በወርቅ ቀለም እንዳጻፈው ገድሉይገልጣል፡፡

  ከዚህ በኋላ የደረሰው ደርሰት ውዳሴ መስቀል ይባላል፡፡ ቀጥሎም መጽሐፈስብሐት ዘመዓልት ወዘሌሊት የተባለውን /ወይም እርሱ ራሱ መጽሐፈ ብርሃንብሎ የሰየመውን/መጽሐፍ አዘጋጅቷል፡፡ ይህን መጽሐፍ «መጽሐፈ ብርሃን»ብሎ የሰየመበትን ምክንያት ገድሉ ሲያበራራ “አስመ ውእቱ ያበርህ ወያስተርኢፍናወ ስብሐቲሁ ለእግዚአብሔር ወፍናወ ስብሐቲሆሙ ለትጉኃን ወለኩሎሙማኅበረ ቅዱሳን ልዑላነ ብርሃን ወዓዲ ይነግር እንዘ ያስተሐውዝ ውዳሴሃለድንግል ንጽሕት— የእግዚአብሔርን የምስጋናውን መንገድ ያበራል /አብርቶያመለክታልና፣ ልዑላነ ብርሃን የሆኑትን የማኅበረ ቅዱሳንንና የትጉኃንንየምስጋናቸውን መንገድ ያመለክታልና፣ የእመቤታችንንም የምስጋናዋን ጣዕምይገልጣልናይላል፡፡

  በዚያ ጊዜ በነበረው ልማድ ካህናቱ ቁርባን በሚያቀብሉ ጊዜ ሕዝቡ ወደካህናቱ መጥተው ሲቀበሉ ንግሥቲቱ ግን ካለችበት ካህናቱ ሄደው ነበርየሚያቆርቧት፡፡ አባ ጊዮርጊስ ግን “ይህ ቁርባን ንጉሠ ነገሥት ነውና ንግሥቲቱወደዚህ መጥታ ልትቀበል ይገባታል እንጂ እኛ መሄድ የለብንም” ሲልተቃወመ፡፡ ይህ ነገር ንግሥቲቱንና አባ ጊዮርጊስን ስላጋጫቸው ዐፄ ዳዊትችግሩን ለመፍታት አባ ጊዮርጊስን ወደ ሀገረ ዳሞት ንቡረ እድነት ሾሞ ላከው፡፡

  አባ ጊዮርጊስና አቡነ ሳሙኤል ዘዋልድባ የተገናኙት አባ ጊዮርጊስ ወደ ዳሞትበሚጓዝ ጊዜ ነበር፡፡ አባ ጊዮርጊስ አለባበሱ እንደ ተርታ ሰው በመሆኑ አቡነሳሙኤል በመጀመርያ አላወቁትም ነበር፡፡ በዚህም የተነሣ አባ ጊዮርጊስ ቅርብሎት ወደ ዳሞት ተመለሰ፡፡ እንደ ሥርግው ሐብለ ሥላሴ ግምት ሁለቱንያላግባባው ሥርዓተ ጸሎት ሳይሆን አይቀርም፡፡ በዚያ ጊዜ በዋልድባ ሥርዓተጸሎቱ ሰባት ጊዜ በቀን መጸለይን የሚያዝ ነበር፡፡ አባ ጊዮርጊስ ግን በቀን ሰባትጊዜ ብቻ መጸለዩ ለእግዚአብሔር ያንሰዋል ብሎ ያምን ነበር፡፡ ምናልባትምበዚያን ጊዜ 22 ሰዓት የሚፈጀውን ሰዓታት ሳያዘጋጅ አልቀረም፡፡

  ከዚህ በኋላ የአባ ጊዮርጊስ ዋናው ትኩረቱ በድርሰቱ ላይ ሆነ፡፡ ወደ ጳጳሱ ወደአቡነ በርተሎሜዎስ ዘንድ በመሄድ የቅዳሴ ድርሰት ለመድረስ እንዲፈቀድለትከጠየቀ በኋላ የቅዳሴ ድርሰት ማዘጋጀቱን ገድሉ ይገልጣል፡፡ ይህም የኢትዮጵያቅዳሴያት ደራሲያቸው ማን ነውለሚለው ጥያቄ መልስ ፍንጭ የሚሰጠንይሆናል፡፡ ገድሉ እንደሚተርከው አንዳንድ ካህናት የአባ ጊዮርጊስን ቅዳሴተቃውመው ነበር፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር አርዮስን በቀጣበት መንገድቀጥቷቸዋል፡፡

   አባ ጊዮርጊስ ነገረ ሃይማኖትን ጠንቅቆ የተረዳና የሚያስረዳ ስለነበር በዘመኑየተነሡ የሃይማኖት ክርክሮች ሁሉ እርሱ ከሌለ አይሳኩም ነበር፡፡ በዚያ ጊዜበሸዋ በይፋት ራሳቸውን ቤተ እስራኤል እያሉ የሚጠሩ አይሁድ ነበሩ፡፡ ከአቡነዜና ማርቆስ ጀምሮ ብዙ መምህራን ወደነዚህ ሕዝቦች እየተሠማሩ ወንጌልንአስተምረዋል፡፡ አቡነ ዜና ማርቆስ ወደ ክርስትና ለተመለሱት ቤተእስራኤላውያን በእመቤታችን፣ በቅዱስ ሚካኤል፣ በአባ ኖብና በሰማዕቱ በጊጋርስም አራት አብያተ ክርስቲያናትን አሠርተው ነበር፡፡ ሁለቱ የመጀመሪያዎቹአሁንም አሉ፡፡ ይህ ሁሉ ቢሆንም ቤተ እስራኤላውያኑ ሙሉ በሙሉ ወደክርስትና አልተመለሱም ነበር፡፡

   ከእነዚህ አይሁድ መካከል አንዱ ከክርስቲያኖች ጋር በነገረ ሃይማኖትለመከራከር ጥሪ አቀረበ፡፡ “ክርስቲያኖች ከረቱኝ ወደነርሱ ሃይማኖት እገባለሁእኔ ከረታኋቸውም ወደኔ ሃይማኖት ይገባሉ” ሲል ነገሩን ጥብቅ አደረገው፡፡ ዐፄዳዊት ይህን ጉዳይ ሲሰማ በጣም ስለ ተናደደ ሊቃነ ካህናቱን፣ ንቡራነ እዱንናየመጻሕፍት ዐዋቂዎችን ሁሉ ከየሀገሩ እንዲሰባሰቡ አዘዘ፡፡ አይሁዳዊው በአንድወገን መምህራኑ በአንድ ወገን ሆነው ክርክሩን ጀመሩ፡፡ የመጀ መርያው እድልየተሰጠው ለአይሁዳዊው በመሆኑ ቀጥሎ ያለውን ጥያቄ አቀረበ፡- “እናንተየእግዚአብሔር ልጅ ነው የምትሉት ይሄ ክርስቶስ እውነት የእግዚአብሔር ልጅከሆነ፣ ወደ ቢታንያ በመጣ ጊዜ አልዓዛር የተቀበረበትን ቦታ ሳያውቅ ቀርቶ'አልዓዛርን የት ቀበራችሁት?” ብሎ እንደ ጠየቀ በወንጌላችሁ ተጽፏል፡፡ ለዚህመልስ ስጡኝ፣እኔንም ከመጽሐፈ ኦሪቴ ጠቅሳችሁ ጠይቁኝ?” ሲል የመከራከርያነጥቡን አቀረበ፡፡

 በዚህ ጊዜ አባ ጊዮርጊስ ታሞ አልጋ ላይ ነበር፡፡ ሊቃውንቱም “እንዲህ ያለውነገር ያለ እርሱ አይሆንምና አባ ጊዮርጊስ ይምጣ” ሲሉ ለዐፄ ዳዊት ጥያቄአቀረቡ፡፡ አባ ጊዮርጊስም በአልጋ ላይ እያለ እንዲመጣ ተደረገ፡፡ በአልጋ ላይሆኖም በጉባኤው ላይ ተገኘ፡፡ ጉባኤተኞቹ የቀረበውን ጥያቄ ነገሩት፡፡ አባጊዮርጊስ የሰጠውን መልስ ገድሉ በሚከተለው መንገድ ይገልጥልናል እኔ ግንበወንጌል ሳይሆን በኦሪት እከራከርሃለሁ፡፡ የምኩራብ መጻሕፍት ሁሉ ለቤተክርስቲያን የታወቁ ናቸውና፡፡ ምኩራብ ዘራች ቤተ ክርስቲያንም አጨደችው፤ምኩራብ ፈተለችው ቤተ ክርስቲያን ለበሰችው፤ አዳምን በገነት ሳለ አዳም ሆይወዴት ነህብሎ የጠየቀው ማነውአብርሃምንስ ሚስትህ ሣራ ወዴት ናት?ብሎ የጠየቀው ማነውእስቲ መልስልኝሰይጣንንስ ከወዴት መጣህብሎየጠየቀው ማነውእግዚአብሔር አብ አይደለምን?” በዚህ ጊዜ አይሁዳዊውመልስ አጥቶ ዝም አለ፡፡ ንጉሡ፣ ሊቃውንቱና መኳንንቱም እጅግ ተደሰቱ፡፡

 አባ ጊዮርጊስ ሌላው ያጋጠመው ክርክር ቢቱ ከተባለው ሰው ጋር ያደረገውክርክር ነበር፡፡ ቢቱ “በምጽአት ጊዜ የሚመጣው ወልድ ብቻውን እንጂ አብናመንፈስ ቅዱስ አይመጡም”  የሚል ኑፋቄ ማስተማር ጀምሮ ነበር፡፡ ቢቱ ከዚህኑፋቄው በተጨማሪ የጥንቆላ ሥራም ይሠራ ነበር፡፡ ቢቱ በጥንቆላ ሥራውየተነ በቤተ መንግሥቱ ተቀባይነት የነበረው ሰው እንደ ነበረ ገድሉ ይናገራል፡፡ይህን መሰሉን ተግባር አጥብቆ የተዋጋው ዘርዐ ያዕቆብ እስኪመጣ ድረስነገሥታቱ ምንም ክርስቲያኖች ቢሆኑ በዚህ መሰሉ ስንኩል ሕፀፅ ይዋጡ ነበር፡፡

 ቢቱና አባ ጊዮርጊስ ወደ ንጉሥ ዳዊት ቀርበው በጉዳዩ ላይ መነጋገርእንደሚፈልጉ ገለጡ፡፡ ዐፄ ዳዊትም ጳጳሱና ሊቃውንቱ ባሉበት እንዲነጋገሩ ስለወሰነ ጳጳሱ እንዲመጡ አዘዘ፡፡ በዚህ ጊዜ ተንኮለኛው ቢቱ ከአባ ጊዮርጊስ ጋርከተከራከረ እንደሚረታ ስላወቀ “ንጉሡ የአባቶቻችንን ሃይማኖት ክዷልናአትምጣ” የሚል ደብዳቤ በአባ ጊዮርጊስ ስም ጽፎ ጳጳሱን ሊጠሩ በሄዱትመልእክተኞች እጅ ላከ፡፡ ወድያውም ለዐፄ ዳዊት ይህንን ነገር አሳበቀ፡፡ ዐፄዳዊትም ፈጣን መልእክተኞች ልኮ የፊተኞቹ መልእክተኞች እንዲመለሱ አደረገናደብዳቤው ተነበበ፡፡ የቢቱ ተንኮል ያልገባው ንጉሥ ዳዊት ይህን ደብዳቤሲመለከት አባ ጊዮርጊስን በደም አበላ እስኪነከር ድረስ እንዲደበደብ አድርጎወደ እስር ቤት አስገባው፡፡ ዐፄ ዳዊት እስኪሞትና ልጁ ቴዎድሮስ እስኪነግሥድረስም በዚያ ቆየ፡፡ ቢቱ ግን በመልአክ ተቀስፎ ሞተ፡፡

  አባ ጊዮርጊስ በወኅኒ ቤት እያለ ጴጥሮስና ጳውሎስ እየመጡ ያጽናኑትነበር፡፡ ውዳሴ ሐዋርያት የተሰኘውንና ከሐምሌ 5 ጀምሮ በ12ቱም ወራት የሚመሰገኑበት የሐዋርያትን ምስጋና የያዘውን መጽሐፍ ያዘጋጀው በወኅኒ በነበረጊዜ ነው፡፡

  ዐፄ ቴዎድሮስ አባ ጊዮርጊስን ከወኅኒ ቤት አውጥቶት በጥንቱ ቦታአስቀመጠው፡፡ አባ ጊዮርጊስ ግን የቤተ መንግሥትን ነገር ለመሸሽ ስለ ፈለገበጋሥጫ ከመቀመጥ ይልቅ ርቆ ጥንት ወደ ነበረበት ወደ ዳሞት በመሄድማስተማር ጀመረ፡፡ ወደ ዳሞት ሲሄድ እግረ መንገዱን ወደ ደብረ ሊባኖስ ገብቶየአቡነ ተክለ ሃይማኖትን መቃብር ተሳልሟል፡፡ በዚያ ጊዜ የደብረ ሊባኖሱ አበምኔት እጨጌ ዮሐንስ ከማ /ሰባተኛው የደብረ ሊባኖስ እጨጌእንደ ነበሩ ገድሉይናገራል፡፡

  ነገር ግን በዕውቀቱ የሚቀኑበት፣ በችሎታው የሚመቀኙት ሰዎች ነገር ሠርተውከንጉሥ ቴዎድሮስ ጋር ስላጣሉት እልም ካለ በረሃ እንዲጋዝ ተደረገ፡፡ አባጊዮርጊስ ከግዞት የወጣው ዐፄ ቴዎድሮስ ሲሞት ነበር፡፡

  የአባ ጊዮርጊስ ሌላው ተማሪ የነበረው ዐፄ ይስሐቅ 1399 . መንግሥቱንሲይዝ አባ ጊዮርጊስን ከግዞት አውጥቶ ወደ ጋሥጫ መለሰው፡፡ በዚያ ጊዜ አባጊዮርጊስ እድሜው 42 ዓመት ሲሆን በስደትና በጤንነት መታወክ የተነሣ ከባድጉዳት ደርሶበት ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ብዙውን ጊዜውን በጾም፣ በጸሎትናበድርሰት ያውለው ነበር፡፡

   “አንድ ቀን ቴዎድሮስ የተባለ መስፍን፣ ዳግመኛም የጦሩ አዛዥ የሚሆን፣ አባጊዮርጊስን ስለ ርትዕት ሃይማኖት ጠየቀው፡፡ አባ ጊዮርጊስም ፍካሬ ሃይማኖት የተባለውን መጽሐፍ ደርሶ ሰጠው፡፡ ንጉሡና የምሥጢር ሊቃውንት የሆኑካህናት ይህንን በተመለከቱና ባነበቡ ጊዜ በእውነት ዮሐንስ አፈወርቅና አፈበረከት የሆነው ቄርሎስ በዘመናችን ተነሥተዋል፡፡ ኢትዮጵያም ቁስጥንጥንያንመስላለች፣ ከእስክንድርያም በላይ ከፍ ከፍ ብላለች ብለው አደነቁ” ይላል ገድሉአባ ጊዮርጊስ ፍካሬ ሃይማኖት የተሰኘውንና የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንየምታምነውንና የምታወግዘውን በግልጥና በዝርዝር የጻፈበትን መጽሐፍ እንዴትእንደ ደረሰው ሲገልጥ፡፡ ፍካሬ ሃይማኖት የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን እምነትበግልጥና በዝርዝር በማስቀመጥ ረገድ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክየመጀመርያው ሥራ ይመስላል፡፡ የዘረዘራቸው የመናፍቃን ስሞችን እናክህደታቸውን ስናይ በዘመኑ የነበሩ ሊቃውንት ስለ ዓለም ቤተ ክርስቲያን ታሪክያላቸውን ዕውቀት ያሳየናል፡፡

  አባ ጊዮርጊስ መከራ ያልተለየው አባት ነበር፡፡ ገድሉ እንደሚተርከው በቤተመንግሥቱ የነበሩ ሰዎች የርሱን መከበርና መወደድ አይፈልጉትም ነበር፡፡በተለይም ፍካሬ ሃይማኖት የተሰኘውን መጽሐፍ በመጻፉ የተነሣ መከበሩአልተዋጠላቸውም፡፡ ስለዚህም ነገር ሠርተው ከዐፄ ይስሐቅ ጋር አሁንምአጣሉት፡፡

 ዐፄ ይስሐቅ አባ ጊዮርጊስን አሳስሮ ውኃ ወደማይገኝበት ዐለታማ ቦታ አጋዘው፡፡በዚያም በመከራ ለብዙ ጊዜ ኖረ፡፡ በዚያ እያለ ዘወትር በጸሎት አብዝቶ ይተጋነበር፡፡ እግዚአብሔርም ዐፄ ይስሐቅ ወደ ልቡናው እንዲመለስ አደረገ፡፡ ንጉሡበአባ ጊዮርጊስ ላይ የፈጸመው ነገር ሁሉ ፀፀተው፡፡ አገልጋዮቹንም ጠርቶ አባጊዮርጊስን እንዲያመጡት አዘዘ፡፡ ነገር ግን እነዚያ ተንኮል ሠሪዎች የአባ ጊዮርጊስመምጣት ተንኮላቸውን ስለሚያጋልጠው “አባ ጊዮርጊስ ሞቷል” ብለውአስወሩ፡፡ ይህንን ሲሰማ ዐፄ ይስሐቅ ፈጽሞ አዘነ፡፡

  አባ ጊዮርጊስ ሞቷል እየተባለ መወራቱን ከደቀ መዝሙሩ ስለ ሰማ በሕይወትየመኖሩን ዜና ጽፎ ለዐፄ ይስሐቅ እንዲያደርስለት አውሎ ንፋስን ላከው፡፡ አውሎንፋሱ ደብዳቤውን ተሸክሞ በመሄድ ዐፄ ይስሐቅ በድንኳን ተቀምጦ በነበረ ጊዜጉልበቱ ላይ አስቀመጠው፡፡ ንጉሡ ምትሐት የተሠራበት ስለ መሰለው ደነገጠናመኳንንቱንና ሕዝቡን ሰብስቦ ጉዳዩን ገለጠ፡፡ ወዲያውም እሳት አስነድዶቢጥለው ሊቃጠል አልቻለም፡፡ ወደ ውኃም ቢጨምረው አልጠፋም፡፡ በዚህተደንቆ ወረቀቱን ከፍቶ አነበበው፡፡ ደብዳቤው ከአባ ጊዮርጊስ የተላከ መሆኑንሲያውቅ ዐፄ ይስሐቅ ደነገጠ፡፡ እነዚያን መልእክተኞች ይዞ ወደ ወኅኒጨመራቸው፡፡ አባ ጊዮርጊስንም ከግዞት ያወጡት ዘንድ ላከ፡፡

 አባ ጊዮርጊስ ወደ ቤተ መንግሥቱ ሲመጣ ንጉሡ በደስታ ተቀበለው፡፡ደብዳቤውን በማን እጅ እንደ ላከውም ጠየቀው፡፡ አባ ጊዮርጊስም ደብዳቤውንበሰው ሳይሆን በእግዚአብሔር ፈቃድ በነፋስ እንደ ላከው አስረዳ፡፡

 ከግዞት ከተመለሰ በኋላ እመቤታችን ተገልጣለት መከራው ሁሉ እንደ ሐዋርያትመሆኑን ገለጠችለት፡፡ አእምሮውን ብሩህ፣ ልቡናውን ትጉኅ የሚያደርግ እጅግብዙ ምሥጢር ነገረችው፡፡ ተሰናብታው ከሄደች በኋላ “እጅግ ብዙ መብራትአቅርቡ አምስት ፈጣን ጸሐፊዎችንም አምጡ” ብሎ አዘዘ፡፡ እርሱ እየነገራቸውእነርሱ እየጻፉ እረፍት ሳያደርጉ ሦስት ቀን ሙሉ አስጽፎ መጽሐፈ ምሥጢርየተሰኘውን መጽሐፍ ፈጸመ፡፡ አምስቱ ጸሐፍትም የየድርሻቸውን አጠናቅቀውበአንድ አደረጉት፡፡ አባ ጊዮርጊስም ይህን ተመልክቶ በእጅጉ አደነቀ፡፡ “እኔየዚህን መጽሐፍ ቃል አልተናገርኩም፤ መንፈስ ቅዱስ በእኔ አፍ ተናገረ እንጂሲል በወቅቱ መመስከሩን ገድሉ ይናገራል፡፡ ይህንም መጽሐፍ መጽሐፈምሥጢር ሲል ሰየመው፡፡ የጻፈው 1409 . እድሜው 52 በደረሰ ጊዜሲሆን የዚህ መጽሐፍ ቅጅ በነጋድያን እጅ እስከ ኢየሩሳሌም ድረስ በወቅቱ ሄዶእንደ ነበር ገድሉ ያስረዳል፡፡

  ዐፄ ይስሐቅ ለአባ ጊዮርጊስ ምድረ ሰዎን የተባለውን የጳጳሳት መቀመጫየነበረውን ሀገር በርስትነት ሰጥቶት ነበር፡፡ አባ ጊዮርጊስ በምድረ ሰዎን ንጉሥይስሐቅ ክረምቱን ያሳልፍበት በነበረው ቦታ ላይ ቤተ ክርስቲያን ሠራ፡፡ በዚያምበማስተማርና በጾም በጸሎት ይተጋ ነበር፡፡ በጋሥጫ እያለ ዐፄ ይስሐቅአስጠራው፡፡ በዚያ ጊዜ ንጉሡ የመናገሻ ማርያምን ቤተ ክርስቲያን አሠርቶ ስለነበር እንዲባርክለት ፈልጎ ነበር፡፡ አባ ጊዮርጊስ ምንም እንኳን በዚያ ጊዜ ታምሞየተኛም ቢሆን ወደ ንጉሡ ተጓዘ፡፡ እዚያ ሲደርስ በጣም ተዳክሞ ነበር፡፡ሥርዓቱን ለመፈጸምም ዐቅም አልነበረውም፡፡ ስለዚህም ንጉሥ ይስሐቅ በአልጋተሸክመውት እንዲዞሩና ቤተ ክርስቲያኗን እንዲባርካት አደረገ፡፡

 ቡራኬውን ከፈጸመ በኋላ ደቀ መዝሙሮቹን ሰብስቦ “ከሞትኩ አባቴ በጸሎተሚካኤል መከራ ወደ ተቀበለባትና እኔም ቤተ ክርስቲያን ወዳነፅኩባት ቦታወስዳችሁ ቅበሩኝ” ሲል አዘዛቸው፡፡ ለደቀ መዛሙርቱ የመጨረሻ የስንብትትምህርቱን እያስተማራቸው እነርሱም በአልጋ ተሸክመውት ወደ ጋሥጫእያመሩ ሳለ በመንገድ ላይ ሐምሌ ሰባት ቀን 1417 . 60 ዓመቱ ዐረፈ፡፡

  እስካሁን ድረስ ያሉን ምንጮች የአባ ጊዮርጊስ ድርሰቶች ቁጥራቸው ከዐርባበላይ እንደሆኑ ይገልጣሉ፡፡ በስም የምናውቃቸው ግን የሚከተሉትን ብቻ ነው፡፡ምናልባት ብዙ ጥናት ማድረግ ሳያስፈልገን አይቀርም፡፡

1. ሰዓታት ዘመዓልት ወዘሌሊት

2. ኖኅተ ብርሃን /ከመጽሐፈ አርጋኖን ጋር አብሮ ታትሟል/

3. ውዳሴ መስቀል

4. ቅዳሴ

5. ውዳሴ ሐዋርያት

6. አርጋኖነ ውዳሴ

7. ፍካሬ ሃይማኖት

8. መጽሐፈ ምሥጢር

9. ውዳሴ ስብሐት

10. እንዚራ ስብሐት

11. ሕይወተ ማርያም

12. ተአምኖ ቅዱሳን

13. መጽሐፈ ብርሃን

14. ጸሎት ዘቤት ቤት

 ጸሎቱና በረከቱ ከመላ ሕዝበ ክርስቲያን ከሀገራችንም ከኢትዮጵያ ጋር ይሁን አሜን!!

ምንጭ፡- 1.የቤተ ክርስቲያን መረጃዎች በዲያቆን ዳንኤል ክብረት፣ ገጽ 591-605
       2.መጽሐፈ ምሥጢር ገጽ 5-9

ይህ የቅዱስ ገብርኤል ድንቅ ተዓምር ነው


(አንድ አድርገን ፤ ጥቅምት 28 2004 ዓ.ም):- የመጀመሪያውን ተዓምር ስፅፍ እንደ እግዚአብሔር መልካም ፍቃድ ሁለተኛውን ለመፃፍ ያብቃኝ ብዬ ነበር፡፡ እነሆ ዛሬ የምነግራችሁ ተዓምር እዛው ኮራ ገብርኤል ላይ የተደረገ ነው ፡፡ ይህ ሁለተኛው ተዓምር ሲሆን የመጀመሪያውን እዚህ ቦታ ላይ የተደረገውን የቅዱስ ገብርኤልን ተአምር ካላነበቡ ለሁለተኛው መንደርደሪያ ይሆኖታልና ቢያነቡት መልካም ነው፡፡


የመጀመሪያውን ተአምር ለማንበብ   ይህን ይጫኑ
እነሆ እንደ እርሱ ፍቃድ የኮራውን የመልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ተአምር ለመፃፍ በቅቻለሁ አስተውለው ያንብቡት ፡፡

ከአሰቦት ገዳም ስንመለስ መጀመሪያ እናየዋለን ያልነው ቦታ የኮራ ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስትያንን ነበር፡፡ ቦታውም ከአዲስ አበባ ወደ ሐረር መንገድ ሲሄዱ አሰቦት መገንጠያ ሳይደርስ በስተቀኝ በኩል 7 ኪሎ ሜትር ድረስ ገባ ብሎ ይገኛል፡፡ ቦታው አጽራረ ቤተክርስትያን በጣም የበዙበት ስለሆነ እግዚአብሔር እነሱን የሚያስተምረው በተዓምር ይመስላል፡፡ ክርስትያኖቹ ተቆጥረው 30 አይሞሉም፡፡ ለኮራ ገብርኤል ያላቸውን ልዩ ቦታ ስትመለከቱ መንፈሳዊ ቅናት ውስጣችሁን ያነደዋል:: እኛ በሺዎች የምንቆጠር ምዕመናን አካባቢያችን ያለውን አንድ ደብር ከአፅራረ ቤተክርስትያን መጠበቅ ሲያቅተን እዚያ በረሀ ላይ ያለውን አንድ የቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስትያን ግን 30 የማይሞሉ ክርስትያኖች በ40 እና በ80 ቀን የስላሴን ልጅነት ያገኙባትን፤ የሚያገለግሏትን፤ ሲያርፉ የሚቀበሩባትን ሁሉ ነገራቸው የሆነችውን ቤተክርስትያንን እንዴት እንደሚጠብቁት ሲመለከቱ ይገርሞታል፡፡


በኮራ ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስትያን ሁለተኛው ተዓምር ሲነገረን በመጀመሪያው በተነገረን ተዓምር እየተደመምንና እየተደነቅን ነበር፡፡ ቦታው ላይ 98 በመቶ የሚሆኑት ሙስሊሞች ብቻ ስለሆኑ ቤተክርስትያኗ ላይ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ተፅዕኖ መኖሩ እሙን ነው፡፡ እያንዳንዷን ፈተና ከትላልቅ የሀይማኖት አባቶች ጋር በመነጋገርና በመወያየት ሲፈቱት አንዳንዱን ግን በጉልበትና በቁጣ ስለሚመጡባቸው ለእግዚአብሔርና ለቅዱስ ገብርኤል አሳልፎ ከመስጠት ውጪ ሌላ ምንም መፍትሄ የላቸውም፡፡

በረሀውን እና ቤተክርስትያኗን ብቻ ሲመለከቱ ያሉበትን የቀን እሳት ሲያስተውሉ እንባዎት አይኖትን ሙልት ያደርገዋል፡፡ እኛን ይዞን የሄደው ሹፌር መንገዱ ትንሽ ኮረኮንች መሆኑን ሲያይ እየሰደበን እየተመናጨቀ ነበር ቦታው ያደረሰን፡፡ ቦታው ስንደርስ መጀመሪያ የወረደው እና ቤተክርስትያኑን የሳመው ሹፌሩ ነበር፡፡ አንዴ ቤተክርስትያኑን ዞሮ ከተሳለመ በኋላ ግን ፊቱ ላይ የሚነበበው ነገር ሀዘን እና አይኖቹ እንባ ቋጥረው ልውረድ ልውረድ እያሉት ‹‹ ይቅርታ አድርጉልኝ እንዲህ መሆኑን አላወኩም እኔ ፤ ይቅርታ አድርጉልኝ አጥፍቻለሁ ማመናጨቅ መሳደብ አልነበረብኝም ፤ ማንም ምዕመን መጥቶ ሊያየው የሚገባ ቤተክርስትያን ነው ፤እዚህ በረሀ ላይ ቤተክርስትያን ይኖራል ብይ አስቤ አላውቅም›ብሎ ከኪሱ 100 ብር  አውጥቶ ‹‹ይህው ይህን ለቅዱስ ገብርኤል ሰጥቻለሁ፤ በማንኛውም ጊዜ የፈለጋችሁት ገዳም መሄድ ብትፈልጉ እኔ ከአጠገባችሁ ነኝ ያጠፋሁትን ጥፋት ይቅር በሉኝ›› ብሎ ንስሀውን እዛው አወረደ፡፡ አብረውን የነበሩት አባት ችግር የለም ልጄ ስላላወክ ነው ብለው ይቅርታውን ተቀበሉት፡፡

የደብሩ አስተዳዳሪ ከነገሩን ተአምር ሁለተኛውን እነሆ
ኮራ ቅዱስ ገብርኤል ታቦቱ የሚያርፍበት አንድ ትልቅ ግራር ከቤተክርስትያኑ ብዙም ሳይርቅ ነበር፡፡ አካባቢው ላይ ያለው ሙስሊም ማህበረሰብ ግራር እንጨት ቆርጦ ፤ እንጨቱን አክስሎ(ከሰል አድርጎ) ፤ ገበያ በማውጣት በመሸጥና ገቢውን ለኑሮ ቀዳዳ ማዋል የተለመደ ነው፡፡ ሶስት ወጣቶች አንድ ቀን ይነሱና ፡፡ የቅዱስ ገብርኤል ታቦት ማረፊያን ግራር ካቆረጥን ይላሉ፡፡ አስበውታል..... ለጥምቀት አዲስ አበባ ያሉ ታቦቶችን ለመሸኝት የሚወጣውን ህዝብ ታቦታቱን ማረፊያቸው አድርሰው ወደቤታቸው ይመለሳሉ፡፡ እነዚህ ክርስትያኖች ግን ቢበዛ ቢበዛ 35 ሆነው ነው ታቦቱን ማደሪያው ግራሩ ጋር የሚያደርሱት ፤  4ኪሎ የሚገኝውን የቅዱስ ገብርኤልን ታቦት ወደ ጃል-ሜዳ ሲሸኝ በ10ሺህዎች የሚቆጠሩ ህፃናት፤ ወጣቶች ፤ አባቶች ምዕመን ከፊት በሰንበት ተማሪዎች በዝማሬ፤ ከኋላ በካህናት ታጅቦ ማደሪያው ይደርሳል፡፡ ኮራ ቅዱስ ገብርኤልን ግን 35 የማይበልጡ ምዕመኖች  አጅበውት ነው ማደሪያው ጋር የሚያደርሱት፡፡ አዛው ድንኳን ይጣላል ያድራል በሚቀጥለው ቀን እየዘመሩ ታቦቱን ወደ ማደሪያው ይመልሳሉ፡፡ ይህን ግራር ነው ሶስት ሙስሊሞች  ካልቆረጥን ያሉት፡፡ ክርስትያቹ ‹‹ ይህ የቅዱስ ገብርኤል ማደሪያ ግራር ነው አትቁረጡብን ቦታው የኛ ነው›ሲሏቸው ‹‹እረ እባካችሁ በፈጣሪያችሁ ይህ ግራር ለረዥም ጊዜ የቅዱስ ገብርኤልን ታቦት የምናሳርፍበት ቦታ ነው አትቁረጡብን› ብለው ቢለምኗቸው ፤ ቢያስለምኗቸው ልመናቸውን የሚሰማ ጆሮ አልነበራቸውም፡፡ ‹‹ማነው ይህን ቦታ ለናንተ የሰጣችሁ እኛ ሀገር መጥታችሁ ቤተክርስትያን ሰርታችሁ ፤ እኛው ሀገር እየኖራችሁ ፤ የእኛ ነው ትላላችሁ እንዴ›› በማለት በቁጣ በማስፈራሪያ በዛቻ መለሱላቸው ለያዥ ለገናዥ አስቸገሩ፡፡ ‹‹ለመስማትም እንቢ አሉ፥ ›› መጽሐፈ ነህምያ 9፤7 ፡፡ በሙስሊም አባቶች ተው ቢባሉ እነዚህ ሰዎች ግን ሊሰሞ አልፈለጉም ‹‹አንገታቸውንም አደንደኑ፥›› መጽሐፈ ነህምያ 9፤7 ፡፡ ‹‹በቃ ተዋቸው በግራር እንጨት አማካኝነት ሌላ ነገር ውስጥ ከምንገባ ይቁረጡት›› አሏቸው ፡፡ይህን ሲሏቸው ነገሩን ማጠፊያ ቦታ ጠፍቷቸው ነበር፡፡ ክርስትያኖቹ በጣም እያዘኑ ከእግዚአብሔር በቀር ታዳጊ ጌታ ፤ ከረድኤቱም በቀር ሰግደድ ያለ ቦታ ፤ ከሃይማኖት የበለጠ ጋሻ ፤ ከእርሱም ውጪ የበለጠ አምባ፤ መጠጊያ ፤ እንደሌላቸው አውቀው ‹‹ቅዱስ ገብርኤል ይፋረዳቸው›› ብለው አልቅሰው አይናቸው እያየ ግራሩን በረዥም መጋዝ መቁረጡን ተያያዙት፡፡ እዛው በአካባቢው ያሉት ክርስትያኖች ስለ ነገሩ አለቀሱ ፤ እንደ ራሄል እንባቸውን ወደ ላይ ረጩት፡፡ የደብሩ አስተዳዳሪም ለምዕመናኑ እንዲህ አሏቸው፡፡ ‹‹ጌታ እግዚአብሔርም ከፊት ሁሉ እንባን ያብሳል›› ትንቢተ ኢሳይያስ 25፤8 እግዚአብሔር ይህን እንባችንን የሚያብስበት ጊዜ ሩቅ አይሆንም ብለው አፅናኗቸው ፡፡ ይህን ነግረውን ሳይጨርሱ ሁላችንም ላይ የሀዘን ስሜት ይነበብብን ነበር ፡፡

እነዚህ ወጣቶች ግራሩን ቆርጠው ለከሰል እንዲሆን እንዲሆን አድርገው ካዘጋጁት በኋላ ከወንዝ መውረጃ ማዶ ከሰል ማክሰሉን ተያያዙት ፤ ግራሩ ከሰል ከሆነ በኋላ ከሶስቱ አንዱ በማዳበሪያ አድርጎ ከሰሉን ለማምጣት ወንዙን ተሻገረ፡፡ በረሀ ላይ ያለ ወንዝ ሁሌም ደረቅ ነው፡፡ ነገር ግን መቼ ውሀ እንደሚኖረው ፤ ጎርፍ መቼ ይዞ እንደሚመጣ አይታወቅም ፡፡ በላይኛው አካባቢ ዝናብ ዘንቦ ኖሮ ከሰሉን ትከሻው ላይ ጣል አድርጎ እየተሻገረ ያለውን ወጣት ውሀው ተሸክሞት ነጎደ፤ ‹‹የእግዚአብሔር ቍጣ በላያቸው መጣ›› መዝሙረ ዳዊት 78፤31 ቢጮህ ቢጮህ ማንም ሊደርስ እና ሊያተርፈው አልቻለም ፤ በዳይ እና ተበዳይ አንድ ላይ ስለሁኔታው አዘኑ ፤ ውሀው የወሰደውን ወጣት ለመፈለግ ሰዎች ተሰበሰቡ ፤ ውሀው መጉደል ስላለበት ውሀው እስኪጉድል ድረስ ጠበቁ ፤ ወንዙን ተከትለው ቢፈልጉ ቢፈልጉ ልጁን በህይወት ማግኝት አልተቻለም ፤ ፀሀይ ወደ መግቢያዋ እያጋደለች ስለሄደች የልጁን ሬሳ ፍለጋ በሚቀጥለው ቀን ሙስሊም ክርስትያኑ ለመፈለግ በሁለተኛው ቀን በማለዳ ወጡ ፤ ሬሳውን ግን አሸዋ ደብቆታልና በቀላሉ ማግኝት አልተቻለም ፤ ሬሳው ሲፈለግ ሶስት ቀን አለፈ ፤ ፈላጊዎቹም ተስፋ ቆርጠው መፈለጉን እርግፍ አድርገው ተውት፡ ቤተሰቦቹ በጣም አዘኑ ‹‹ይህ የአላህ ቁጣ ነው›› አሉ፡፡ የዚህን ልጅ ሬሳ ከ5 ቀን በኋላ እንደ እግዚሐብሔር መልካም ፍቃድ አሸዋው ተፍቶት ተገኝ፡፡ ግብአተ መሬትም ተፈፀመለት ፡፡እኛም በጣም አዘንን

ይህ እንዲህ እያለ  የሁለተኛውን ወጣት እጣ ፋንታ የደረሰበትን ነገር እንዲህ ብለው ነገሩን
የዚህ ልጅ ሀዘን ገና ለአካባቢው መፅናናት ሳይደርስ  ‹‹የእግዚአብሔር ቍጣ በዚህች ምድር ነደደ››  ኦሪት ዘዳግም  2927 ሌላ ነገር ደግሞ በሁለተኛው ላይ ተከሰተ ፡፡ ሁለተኛው ልጅ ‹‹ብርሃን የለበሰ  ሰው የሚመስል ፤ በጣም ረዥም ፤ መስቀል በእጁ የያዘ መጥቶ ተቆጥቶት ለምን ማደሪያዬን ቆረጣችሁ›› ብሎ በጥፊ እንደመታው ለቤተሰቦቹ መስክሮ ከጨረሰ በኋላ ሙሉ ሰውነቱን ማዘዝ ተስኖት ፓራላይዝ መሆኑ ሲሰማ ሁሉም ሰው ደነገጠ ፡፡ ‹‹እኔም በተዘረጋች እጅና በብርቱ ክንድ፥ በቍጣና በመዓት በታላቅም መቅሠፍት እወጋችኋለሁ። ትንቢተ ኤርምያስ 21፤5 ልጁ አይሰማም ፤ አይናገርም ፤ ምግብ በአግባቡ መመገብ አይችልም ፤ ሰውነቱን እንደ ከዚያ በፊቱ ማዘዝ ተሳነው :: ሞቷል እንዳይባል እስትንፋስ አለው ፤ ለተመለከተውም ሆነ ለሚሰማው ግራ የሚያጋባ ሁኔታ ነበር ፡፡ ‹‹አሕዛብ ሁሉ። እግዚአብሔር በዚህች ምድር ስለ ምን እንደዚህ አደረገ? ይህስ የቍጣው ታላቅ መቅሠፍት ምንድር ነው? ይላሉ።›› ኦሪት ዘዳግም 2924
እስላም ክርስትያኑም በሆነው ነገር ደንግጠው ነበር፡፡ ከዚያ ቀን በፊት እንዲህ አይነት ነገር በአካባቢያቸው አይተውም ሰምተውም ስለማያውቁ ምን እንደሚያደርጉ ግራ ገባቸው፡፡ ቤተሰቦቹ ልጁን ለማሳከም ብዙ ቦታ ይዘውት ቢሄዱም ካለበት ሁኔታ ግን አንዳች ሊነቃ አልቻለም፡፡ ሙስሊሞቹ ‹‹ዱአ›› የሚሉት ነገር አላቸው፡፡ አንድ ሰው ሲታመም ጫት እየተቃመ ‹ዱአ›› ይደረግለታል ፈጣሪያቸውን ይለማመኑለታል ፡፡ ገጠር ወሰዱት‹ዱአ›› አደረጉለት ፤ አሰበ ተፈሪ ወሰዱት ‹ዱአ›› ተደረገለት ፤ አለ የሚሉት ቦታ ሁሉ ወሰዱት ነገር ግን ምንም አንዳች ለውጥ ሊያመጣ አልቻለም፡፡ መጨረሻም ላይ የክርስትያኖቹ ቄሶች ጋር ይዘውት ይሂዱ ተብለው አባትየው ልጃቸውን ይዘው ወደ ቤታቸው ተመለሱ አሁን ቤት ነው ያለው ብለው ነገሩን …. ወላጆች ‹‹ልጄ ደረሰልኝ ስራ ይዞ ይጦረኛል ብለው ተስፋ በሚያደርጉበት ሰዓት በእንደዚህ አይነት ቁጣ ልጆች ላይ ሲያጋጥም ስሜቱን የሚረዱት ወላጆች ብቻ ናቸው›› ካሉን በኋላ  ‹‹ቆይ ልጆቼ አባትየው እየመጡ ነው እሳቸውው የሆነውንና ልጁ ያለበትን ነገር ይንገሩአችሁ›› አሉን፡፡  ለካ ቤተክርስያን እኛ መምጣታችን ተነግሯቸው ኖሯል እኛል ለማየት አባትየው እየመጡ ነበሩ፡፡

አባትየው እድሜያቸው ከ60 የዘለለ ሲሆን የሙስሊሞቹ ሼካዎች አይነት ዕይታ አላቸው ፡፡ ቤተክርስትን መጥተው ሁላችንንም ሰላምታ ከሰጡን በኋላ እኛን ተቀላቀሉን፡፡ ምን ብለን እሳቸውን ማውራት እንዳለብን እንዴት መጠየቅ እንዳለብን ምንም የምናውቀው ነገር የለም፡፡ አባ ‹‹ልጁ እንዴት ነው›› አሏቸው ‹‹ደህና ነው›› ብለው መለሱ ፡፡ በዚያው አባ የነገሩንን ሁሉ ነገር ከልጁ አባት ደግመን ሰማነው፡፡ እኛም ‹‹ እይዞት አባባ እግዚአብሔር መሐሪ ነው ይምረዋል እያመጡ እዚህ ልጁን ፀበል ያስጠምቁት እግዚአብሔር በፈቀደና በወደደ ቀን ምህረቱን ይልክለታል አይዘኑ›› በማለት ትንሽ ልናፅናናቸው ሞከርን፡፡ እሳቸውም ‹‹እሺ ›› አሉን፡፡ ይህ ልጅ በቅርብ ጊዜ ነበር እግዚአብሔር ምህረቱን ልኮለት ከረዥም ጊዜ በኋላ ሊድንና ወደ መጀመሪያ ጤናማ ሁኔታው ሊመለስ የቻለው፡፡

በጣም ይገርማል. . .በጣም እኔ ከዚህ በፊት እንዲህ አይነት ነገር ሰምቼ ስለማላውቅ በቃ አይኔም ጆሮዬም ልቦናዬም እያንዳንዷን ነገር በማስተዋል ነበር የማየው ፤ የምሰማው ፤ የሰዎችን ስሜት የምመለከተው ፡፡ የቤተክርስትያኑ አስተዳዳሪ ቤተክርስትያኑ ጧፍ ፤እጣን፤ ፤ የቤተክርስትያን መገልገያዎች እንደሚቸገሩና እነሱን እንኳን አሟልተው ማገልገል ከባድና በጣም አስቸጋሪ መሆኑን ነገሩን ፡፡ እኛም መጀመሪያ ከአዲስ አበባ ስንነሳ በረሀ መሆኑን ጧፍ እና እጣን እንደሚቸገሩ ነግረውን ትንሽ ይዘን ነበር፡፡ ከሱ በተጨማሪ ሁላችንም ኪሳችንን ዳበስ ዳበስ አድርገን 700 ብር ያህል አንድ ላይ ከመጣነው ከ30 የማንበልጥ ሰዎች ሰበሰብንና ለቤተክርስትያኗ አስተዳዳሪ አስረከብን፡፡ በጣም ደስ አላቸው አመስግነው ተቀበሉን ፡፡

ከዚያም እንዲህ አሉን
‹ቁልቢ ገብርኤል በዓመት ሁለት ጊዜ ሲከብር በሺህ የሚቆጠር ምዕመንና በሺህ የሚቆጠር መኪና ነው እኛን አልፎ የሚሄደው፡፡ ቢያንስ እንኳን ምንም አያድርጉንል ጧፍም፤ እጣንም ፤ የቤቱ መገልገያም ፤ብርም አይስጡን ፤ ግን ምን አይነት ሁኔታ ላይ እንዳለን እንኳን አይተውን ቢያልፉ ለእኛ እርሱ ነው ትልቁ ስጦታ ፤ አይዟችሁ ቢሉን ፤ እኛም የእናንተ ወገን ነን ቢሉን ፤ ይበቃን ነበር ብለው ፊታቸው ላይ አንዳች ሀዘን ይዟቸው ረዘም ያለ ጊዜ ዝም አሉ፡፡ እንዲህ ሲሉ ለካ ‹‹አይዟችሁ ቢሉን ፤ እኛም የእናንተው ወገን ነን ቢሉን› ያሉት ነገር ውስጤ ቀርቶ ኖሮ እንባዬ እንኳን በአይኔ ላይ ሲፈስ አላውቀውም ነበር፡፡
ስንት ቤተክርስትያኖች በበረሀ ላይ በእንደዚህ አይነት ሁኔታ ላይ እንደሚኖሩ ለአንድ ጊዜ እንኳን አስበን አናውቅም ፡፡ እኛ ከተማ ላይ የምንኖር ምዕመናኖች የገጠሪቱን ቤተክርስትያን ጧፍ እጣን የቤቱ መገልገያዎችን የማሟላት ግዴታው አለብን፡፡ ስንቶቻችን ነን ግሸን ማርያም፤ አክሱም ፅዮን ፤ ቁልቢ ገብርኤል ስንሔድ መንገድ ላይ ያሉትን ቤተክርስትያኖች ጧፍና እጣን የምንሰጠው? ለአንዲት ደቂቃ እንኳን ያሉበትን ሁኔታ የምናስታውሰው?  ችግራቸው ችግራችን መስሎ የሚታየን ? በየገጠሩ ስንሔድ እንደ ኮራ ገብርኤል በረሀ ላይ ያሉ ምዕመኖች የአፅራረ ቤተክርስትያን ተቋቁመው ሲኖሩ ፤ ካህናት ደግሞ ቅዳሴ ለመቀደስ  ጧፍና እጣን በጣም ይቸገራሉ :: እዚህው አካባቢ የሚገኝ የፃድቁ አባታችን የአቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስ ቤ/ን አንዲት ጧፍ በቅዳሴ ሰዓት አጥተው በጋዝ ብርሀን(ኩራዝ) ወንጌል እንደተነበበ ሲነግሩን በጣም ነው ያዘነው፡፡ ምን ያህል ችግር እንዳለባቸው ለመረዳት ብዙ ነጋሪ አያሻም፡፡ ችግራቸው አንዲት ጧፍ እስከማጣት ይደርሳል፡፡ አንዲት ጧፍ 1ብር ናት ይችም ለካ የምትቸግርበት ጊዜ አለ?  የእነዚህን ቤተክርስትያኖች ችግር የእኛ ችግር አድርገን በመውሰድ የአቅማችንን ብንረዳቸው መልሱን ከእግዚአብሔር እናገኝዋለን፡፡

የሶስተኛው ጓደኛቸው እጣፈንታ ደግሞ የቤተክርስትያኑ አስተዳዳሪ እንዲህ ብለው ነገሩን
‹‹በዚህም ሁሉ እንኳ ቍጣው አልተመለሰችም›› ትንቢተ ኢሳይያስ 9፤21 ሶስተኛው የደረሰበት  እንኳን ከቀደሙት ከሁለቱ ብዙም አይለይም እሱም ይህው ጨርቁን ጥሎ ሀገር ጥሎ ከጠፋ ቆየት እንዳለና የት እንደሚገኝ ቤተሰቦቹ እንኳን አያውቁም፡፡ ›› ብለው የሶስተኛውን ወጣት የደረሰበትን ነገር ነገሩን፡፡ ‹‹ተመክሮ ካለመስማት ፤ አይቶ ካለመማር ፤ ሰምቶ ካለማስተዋል ፤ልብን ከማደንደን እግዚአብሔር ይጠብቀን ›› ብለው መከሩን፡፡ምን ይባላል ? እኛ ዝምታን ነበር የመረጥነው፡፡ኦሪት ዘጸአት 32፤9 ላይ ‹‹እኔ ይህን ሕዝብ አየሁት፥ እነሆም አንገተ ደንዳና ሕዝብ ነው።›› ይላል፡፡  ይህ ሁሉ ነገር በቦታው ላይ ሲደረግ፤ ይህን ሁሉ ተዓምር እግዚአብሔር ቢያሳያቸው ፤ ቤተክርስትያኗን እንዳይተናኮሏት ቢያስተምራቸው ልባቸው አንዴ ደንድኗልና እነሱም ከመተናኮል አርፈው የሚያውቁበት ጊዜ የለም፡፡

እኛ ሁሌ እንበድላለን ፤ ሁሌ እሱን እናሳዝናለን ፤ መደረግ የማይገባቸው ነገሮችን እናደርጋለን እንሰራለን ፤ ለምን ‹‹በደልን ይቅር የሚል›› ትንቢተ ሚክያስ 7፤18 አምላክ እግዚአብሔር የቁጣ ሰይፉን እንዳልመዘዘብን አስበነው እናውቃለን?  ለምን እንደ ሎጥ ሚስት(ዘፍ 19፤27)እንደ ኤሳው (ዘፍ 25፤32)፤ እንደ ዳታንና አቤሮን ፤ ቄሬ ነገደ ሌዊ (ዘኁ 16 ፤1-50)፤ የኤሊ ልጆች (1ኛ ሳሙኤል 2፤11-22) ፤ ንጉስ አዝያን (2ኛ ዜና 26፤16-21) ፤ የናቡከደነፆር ልጅ ብልታሶር (ዳን 5፤1-31) ስናጠፋ የቁጣ ሰይፉን አልመዘዘብንም?

ነገ አይደግሙት፤ ለሰሩት በደል ‹‹ንስሐ ቢገቡ ›› መጽሐፈ ዜና መዋዕል ካልዕ 6፤37 በንስሀ ይመለሳሉ ፤ የንስሀ እድሜ ልጨምርላቸው ብሎ እንጂ እንደ እኛ ስራ አይደለም በህይወታችን ላይ ይች ቀን የተጨመረችልን፡፡  ‹‹እግዚአብሔር መሓሪና ይቅር ባይ ነው፥ ከቍጣ የራቀ ምሕረቱም የበዛ። ›› መዝሙረ ዳዊት 103፤3 ስለሆነ ነው፡፡  እግዚአብሔር ለሙሴ ከሰጠው 10ቱ ትዛዛት በቀን ስንቱን ስንት ጊዜ እንተላለፋቸዋለን? ከእኔ በቀር ሌላ አምላክ አታምልክ ይላል፡፡ እኛ ገንዘብ አምላካችን ከሆነ ሰንበትበት ብሏል፡፡ ‹‹ለሁለት ጌቶች መገዛት የሚቻለው ባርያ ማንም የለም፤ ወይም አንዱን ይጠላልና ሁለተኛውንም ይወዳል፥ ወይም ወደ አንዱ ይጠጋል ሁለተኛውንም ይንቃል። ለእግዚአብሔርና ለገንዘብ መገዛት አትችሉም።›› የሉቃስ ወንጌል 16፤13 ስለገንዘብ ብለን የማናደርገው ነገር ምን አለ? ከዚህስ በላይ አምላክ ሊሆን የሚችል ምን አለ? በወንጌል እንደተነገረን አንዱ አምላክ የተባለው ገንዘብ መሆኑን ምን ያህላችን እናውቃለን?


ይህን ሁሉ ካየው ከሰማው በኋላ ለራሴ እንዲህ ስል ጠየኩት
‹‹እግዚአብሔር ለምን ይህ ተአምር ሊያሳየኝም ሆነ ሊያሰማኝ ወደደ? ከዚህ በኋላ ከእኔ ምን ይጠብቃል? ገዳም መመላለሴ ጥቅሙ ምንድነው? አሰቦት ገዳም ፤ ዋልድባ ፤ ደብረሊባኖስ ገዳም እያልኩ መሽከርከር? ወደ ህይወት ቀይረህ ካልተጠቀምክበት ፤ ክርስትና ህይወትህን አንድ ደረጃ ከፍ ካላደረገልህ ፤ የበፊት ክፋትህን ትተህ ለህጉ ካልተገዛህለት ፤በንስሀ ህይወት ካልተመላለስክበት ፤ ስጋውን ለመብላት ደሙን ለመጠጣት ካልበቃህበት ፤ ትህንና ፤ ቅንነትን፤ ርህራሄን ገንዘብ ማድረግ ካልቻልክ ምንድነው ጥቅሙ ?›› ለጊዜው መልስ ያላገኝሁለት ጥያቄ ነበር፡፡

በተነገረን ሁሉ  የእግዚአብሔርን ስራ እየገረመን ፤ እነደ እግዚአብሔር መልካም ፍቃድ ሌላ ጊዜ እንደምንመለስ ቃል ገብተን የቦርደ የአቡነ ገ/መንፈስ ቅዱስን ቤተክርስትያን  ለማየት ተንቀሳቀስን፡፡

ቦርደዴ አቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስ ቤተክርስትያን በ12 እና በ13ተኛው ክፍለ ዘመን በኢቲሳ ተክተኃይማኖት የነበረ ፅላት ሲሆን ሙሉ ታሪኩን እንዴት ወደ ቦርደዴ(አዋሽ አካባቢ) ሊመጣ የቻለበትን ሁኔታ ፤ አመጣጡን ፤ መቼ ቅዳሴ ቤቱ እንደከበረ ፤ ቦታው ላይ ስለተደረጉ ገቢረ ተዓምራት ፤ የክርስትያኖቹን ብዛት ፤ የአፅራረ ቤተከርስትያን እያደረሱ ያለውን ፈተና ከቤተክርስትያኑ አስተዳዳሪ ጠይቄ ያወኩትን ለናንተ በሰፊው ለመፃፍ የእግዚአብሔር መልካም ፍቃዱ ይሁንልኝ፡፡አሜን

መርዳት ለምትፈልጉ ሰዎች

ቦታውን ሄደን ማየት እንፈልጋለን ቤተክርስትያኖቹንም መርዳት እንፈልጋለን  ለምትሉ ሰዎች 0913-833532 (የቦርደዴ አቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስ ቤተክርስትያ አስተዳዳሪ ስልክ ነው )፡፡  ይህን ስልክ በመጠቀም በእሳቸው አማካኝነት በበረሀ አካባቢው የሚገኙትን የኮራ ገብርኤል፤ የሚካኤልን ፤የቦርደዴ የአቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስን የኪዳነ ምህረትን አብያተክርስትያናትን በጧፍ በእጣን በቤተክርስትያ መገልገያዎች መርዳት ይችላሉ ፡፡
በነዚህ ጊዜያት ቤተክርስትያኖቹን ማየት ይችላሉ
  • ጥቅምት 29:-  የአባ ሳሙኤል ዘደብረ ወገግ እረፍታቸው
  • ግንቦት 27:- የአባ ሳሙኤል ዘደብረ ወገግ ፍልሰተ አጽም
  • ሀምሌ 10:- የአባ ሳሙኤል ዘደብረ ወገግ ልደታቸው
  • ጥር 7 እና ሐምሌ 7:-  የአሰቦት ስላሴ አመታዊ ክብረ በአል
  • ጥቅምት 5 :-  የአቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስ አመታዊ በአል
  • ታህሳስ 19 እና ሐምሌ 19 ፡ የቅዱስ ገብርኤል አመታዊ ክብረ በአል 


እንደ እግዚአብሔር መልካም ፍቃድ መፃፍ ጀመርኩ እንጂ አልጨረስኩም በቦርደዴ አቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስ ቤተክርስትያን ታሪክና የተደረጉ ገቢረ ተአምራትን ደግሞ ቀጥዬ ለናንተው ለመፃፍ የእግዚአብሔር መልካም ፍቃድ ይሁንልኝ፡፡

‹‹እግዚአብሔር ቤተክርስትያንን ይጠብቅ››

"ምንጭ: አንድ አድርገን የጡመራ መድረክ"




ቅዳስ ያሬድ




ቅዳስ ያሬድ አባቱ አብድዩ /ይስሐቅ/ እናቱ ክርስቲና /ታውክልያ/ ይባላሉ /በሌላም በኩል አባቱ እንበረም እናቱ ትውልያ ይባላሉ የሚል ታሪክም አለ፡፡/ የትውልድ ሥፍራው አከሱም ነው፡፡ የተወለደው በ505 ዓ.ም/ ሚያዝያ 5 ቀን የሚል አለ/ ሲሆን በተወለደ በ7 ዓመቱ ወላጅ አባቱ ስለሞተ እናቱ የአክሱም ጽዮን መምህር ለነበረው ለአጎቱ ለጌዴዎን እያስተማረ እንዲያሳድገው ሰጠችው፡፡ ከአባ ጌዴዎንም ዘንድ እየተማረ ለ25 ዓመት ተቀመጠ፡፡

ሆኖም ቃለ እግዚአብሔር የመቀበል ችሎታው ደካማ ስለሆነ በጣም ያዝን ነበር፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን ከትምህርት ድክመቱ የተነሣ አጎቱ በጨንገር ቢገርፈው በዚህ ተበሳጭቶ ትምህርቱን ትቶ ሄደ፡፡ በመንገድም ሲጓዝ ውሎ በቀትር ደክሞት ከዛፍ ሥር ዐረፈ፡፡ በዚያ ጊዜ አንድ ትል ከዛፉ ላይ ያለውን ፍሬ ለመብላት ስድስት ጊዜ በመውደቅና በመነሣት ዛፉ ላይ ለመውጣት ሞክሮ በሰባተኛው ሰተት ብሎ ወጥቶ ሲበላ ተመለከተ፡፡ እርሱም በፈጸመው የብስጭት ተግባር በመጸጸት ተመልሶና አጎቱን ይቅርታ ጠይቆ ትምህርቱን ቀጠለ፡፡ አጎቱም ተደስቶ ዓይነ ልቡናውን ያበራለት ዘንድ እያለቀሰ ፈጣሪውን ለመነለት፡፡ እግዚአብሔርም ጸሎቱን ሰምቶ ለቅዱስ ያሬድ ዕውቀትን ገልጾለት መጻሕፍተ ብሉያትንና ሐዲሳትን ዐወቀ፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ይህን በተመለከተ

ሰላም ለያሬድ ስብሐተ መላእክት ለሕዋጼ
እንተ አዕረገ በልቡ ኅሊና መንፈስ ረዋጼ
ለትምህርተ መጽሐፍ ገብአ እምኀበ ኮነ ነፋጼ
በብዙኀ ፃማ ዘአልቦ ሐጻጼ
መልዕልተ ዕፅ /ኮሞ/ ነጸሮ እንዘ የዐርግ ዕጼ

የሚል ዐርኬ ደርሰውለታል፡፡ ይህን አርኬ የድጓ መምህራን ጠዋት ጉባኤ ሲዘረጉ ተማሪዎቻቸውን ያስደርሷቸዋል፡፡

ከዚያም በኋላ ወደ መምህሩ ተመልሶ ትምህርቱን ቀጠለና ቅዱሳት መጻሕፍትን በሚገባ አጠና፡፡ ሢመተ ዲቁናን ቀጥሎም ሢመተ ቅስናን ተቀበለ፡፡ ቅዱስ ያሬድ ግእዝ፣ እዝልና አራራይን ከሦስት ወፎች/መላእክት በወፎች ተመስለው/ መማሩን ሊቃውንት ይገልጣሉ፡፡ እነዚህ በወፍ የተመሰሉ መላእክት እየመሩት ወደ አርአያም አርጎ የ24ቱን ካህናተ ሰማይ ዜማ ከተማረ በኋላ ጠዋት በ3 ሰዓት በአክሱም ቤተ ክርስቲያን «ሃሌ ሉያ ለአብ ሃሌ ሉያ ለወልድ ሃሌ ሉያ ለመንፈስ ቅዱስ ቀዳሚሃ ለጽዮን ሣረረ ወበዳግመ አረአዮ ለሙሴ ዘከመ ይግበር ግብራ ለደብተራ» ብሎ አዜመ፡፡ ይህን ዜማ የደረሰበት ወሩ ታኅሳስ ቀኑም ዕለተ ሰኞ ነው ይባላል፡፡ የቅዱስ ያሬድ የመጀመሪያ ዜማው «አርያም» በመባል ይታወቃል፡፡ ይህም ከመላእክት ወይም ከሰማይ የተገኘ መሆኑን ለማጠየቅ የተሰጠው ስም ነው፡፡

ቅዱስ ያሬድ ይህንን ዜማ በተመስጦ ሲያዜም ንጉሡ፣ንግሥቲቱ፣ ጳጳሱ መኳንንቱና ካህናቱ ወደ አኩስም ቤተ ክርስቲያን ተሰባስበው መጥተው በአድናቆት ያዳምጡት ነበር፡፡ ምክንያቱም ገደለ ቅዱስ ያሬድ እንደሚገልጥልን ከዚያ በፊት በውርድ ንባብ ከሚደረግ ጸሎትና መንፈሳዊ አገልገሎት በቀር ይህን የመሰለ ዜማ አልነበረምና፡፡

የቅዱስ ያሬድ ድርሰት ብሉይን ከሐዲስ ያስማማ፣የሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በሚገባ የያዘ፣ እንዲሁም ለልዑል እግዚአብሔር፣ለእመቤታችን፣ለቅዱሳን መላእክት፣ ለጻድቃንና ለሰማዕታት ተገቢ የሆነውን ምስጋና የያዘ ነው፡፡ ከዚህም በላይ ለአራቱ የዓመቱ ወቅቶች እንዲስማማ አድርጎ ለበጋ፣ ለክረምት፣ ለመጸውና ለጸደይ እንደሚሆን አድርጎ ከፋፍሏቸዋል፡፡ ለየበዓላቱም ተስማሚ ድርሰት መድቦላቸዋል፡፡ ይህንን ድርሰቱን በግእዝ፣ በእዝልና በአራራይ ዜማ ያዘጋጀው ሲሆን ለነዚህም ስምንት የዜማ ምልክቶች ሠርቶላቸዋል፡፡

የቅዱስ ያሬድ ዜማ አንዴት ሁሉንም ይመስጥና ወደ አርያም በመንፈስ ይወስድ እንደ ነበር ለማስረዳት በገድሉም በሌሎችም መጻሕፍት የተመዘገቡ ታሪኮች አሉ፡፡ አንድ ቀን ንጉሥ ገብረ መስቀል፣ንግሥቲቱ፣ ጳጳሱ፣ ካህናቱና ምእመናኑ በተሰባሰቡበት ቅዱስ ያሬድ ዜማውን ሲያዜም ንጉሡ በመመሰጡ የተነሣ በመሰቀል ተሰላጢኑ ጫፍ የቅዱስ ያሬድን እግር ወጋው፡፡ ነገር ግን ማንም አላወቀም ነበር፡፡ ቅዱስ ያሬድ መዝሙሩን ሲፈጽም ንጉሡ መስቀል ተሰላጢኑን ቢያነሳው የቅዱስ ያሬድ ደሙ ፈሰሰ፡፡ ንጉሡ በዚህ ደንግጦ ለዚህ ካሣ ይሆን ዘንድ የፈለግከውን ጠይቀኝ እሰጥሃለሁ ብሎ ቃል ገባለት፡፡ ቅዱስ ያሬድ ግን ከዚህ ዓለም ተለይቶ በምናኔ መኖርና መዝሙሩንም በሚገባ ማዘጋጀት እንደሚፈልግ ገለጠ፡፡ ምንም እንኳን አኩስምን ለቅቆ መውጣቱ ንጉሡን ቅር ቢያሰኘውም ቃሉን አንድ ጊዜ በመስጠቱ ምንም ሊያደርገው አልቻለም፡፡ ቅዱስ ያሬድም ከዚህ በኋላ አኩስምን ለቅቆ ወደ ስሜን ተራራ ጸለምት መጓዙ ይነገራል፡፡

በጐንደር ፎገራ በሚባል ሥፍራ ቅዱስ ያሬድ ጣዕም ያለው ዜማውን ሲዘምር ተጠምደው የሚያርሱ በሬዎች ድምፁን እየሰሙ ገበሬውን ሥራ ስለ አስፈቱት በዚህ ተናዶ ቅዱስ ያሬድን በጅራፍ እንደ ገረፈው ይነገራል፡፡ ቦታውም «ወርቀ ደም´ እየተባለ እስከ ዛሬ ይጠራል፡፡ ወርቃማና ንጹሕ ደሙ የፈሰሰበት ማለት ነው፡፡

ቅዱስ ያሬድ ዜማውን ያዘጋጀበት ዘመን ከ540-560 ዓ.ም. ባለው ጊዜ መሆኑ ይነገራል፡፡ ዜማውን ካዘጋጀ በኋላ 11 ዓመት አስተምሯል፡፡ በእርሱ ዘመን ተሰዓቱ ቅዱሳን በሃይማኖት ችግር ምክንያት ወደ ኢትዮጵያ ተሰደው መጥተው ስለ ነበር ቅዱስ ያሬድ ከአንዱ ከአባ ጰንጠሌዎን የውጭውን ሀገር ቤተ ክርስቲያን ባሕልና ሥርዓት ይጠይቅ ነበር፡፡ በጆሮ የሰማውንም በዓይን ለማየት ሁለት ጊዜ ሮም የተባለችውን የቁስጥንጥንያ ቤተ ክርስቲያን ጐበኘሁ ይላል፡፡ «ወሪድየ ብሔረ ሮሜ ለቤተ ክርስቲያን ርዒክዋ» እንዲል፡፡ የታሪክ ምሁሩ ሥርግው ሀብለ ሥላሴ ለቁስጥንጥንያ ዜማ መነሻው ቅዱስ ያሬድ ነው ይላሉ፡፡ ለዚህም ማስረጃ የሚያደርጉት የቁስጥንጥንያን ዜማ የደረሰው ሊቅ ዜማውን አገኘው የሚባለው የቅድስት ሶፍያን ቤተ ክርስቲያን ሲዞር ከሰማው ዜማ ነው፡፡ ይህ ዘመን ደግሞ ቅዱስ ያሬድ ከተነሣበትና ወደ ሮሜ ሄድኩ ካለበት ዘመን ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ እናም ምናልባት ያ ሰው ዜማውን የሰማው የቅድስት ሶፍያ ቤተ ክርስቲያንን እየዞረ ሲዘምር ከነበረው ከቅዱስ ያሬድ ሳይሆን አይቀርም ይላሉ፡፡ Ancient and medival Ethiopian History/

ቅዱስ ያሬድ ማትያስና ዮሴፍ በተባሉ የአቡነ አረጋዊ ደቀ መዛሙርት መሪነት ወደ ደብረ ዳሞ ተራራ ላይ ወጥቶ ከጻድቁ ጋር በመገናኘትና የቤተ ክርስቲያኑን ሥራ እያደነቀ ዙሪያውን ከዞረ በኋላ «ዖድክዋ ወርኢኩ ሥነ ሕንፃሃ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን» ሲል ዘመረ፡፡ በዚያም ለአንድ ሳምንት ሰንብቶ ሄዷል፡፡

ቅዱስ ያሬደ ከአቡነ አረጋዊ እና ከዐፄ ገብረ መስቀል ጋር በመሆን በወሎ፣ በጎንደር፣ በሸዋ እና እስከ ጋሞጎፋ ብርብር ማርያም ድረስ በመሄድ አስተምሯል፡፡ አንዳንድ መረጃዎች የዐርባ ምንጭን ታሪክ ከቅዱስ ያሬድ፣ ከአቡነ አረጋዊ እና ከዐፄ ገብረ መስቀል ታሪክ ጋር ያያይዙታል፡፡ ሦስቱም ብርብር ማርያምን ለማየት ሄደው በነበረ ጊዜ በዛሬው ዐርባ ምንሥ አካባቢ ሠፍረው ነበር፡፡ በዚያ ቦታ ለወታደሩ የሚበቃ የሚጠጣ ውኃ በመጥፋቱ አቡነ አረጋዊ ጸልየው መሬቱን በመስቀል ቢመቱት ዐርባ ውኃዎች ፈለቁ ይባላል፡፡

ዐፄ ገብረ መስቀል የጣና ቂርቆስን ቤተ ክርስቲያንን በሚያሠራ ጊዜ በዚያ ቦታ ለሁለት ዓመት ተቀምጦ ድጓውን በማስተማሩ ምልክት የሌለው ድጓው እስከ ዛሬ በገዳሙ ይገኛል፡፡ ቀጥሎም የዙር አባን ቤተ ክርስቲያን ለማሠራት ወደ ጋይንት በተጓዙ ጊዜም በዚያ ሁለት ዓመት ዝማሬ መዋሥዕት የተባለ ድርሰቱን አስተምሯል፡፡ ይህ ቦታ እስከ ዛሬ የዚህ ትምህርት ማስመስከሪያ ነው፡፡

ቅዱስ ያሬድ ከዚያ በኋላ ወደ አከሱም ተመልሶ በመደባይ ታብር በተባለ ቦታ ቅዳሴያትን በዜማ አዘጋጅቷል፡፡ ይህ ቦታ ከአከሱም 15 ኪ.ሜትር ርቆ ይገኛል፡፡ ከዚህ በኋላ ለመጨረሻ ጊዜ አኩስምን ተሰናብቶ ለመሄድ ወደ ጽዮን ቤተ ክርስቲያን ገባና «ቅድስት ወብጽዕት ስብሕት ወቡርክት ክብርት ወልዕልት አንቀጸ ብርሃን ማዕርገ ሕይወት» እያለ አንቀጸ ብርሃን የተባለውን ድርሰቱን ሰተት አድርጎ አዘጋጀው፡፡ ይህንን ድርሰት ሲያዜም አንድ ክንድ ያህል ከምድር ከፍ ብሎ ይታይ ነበር ይባላል፡፡

ቅዱስ ያሬድ በሰሜንና ወገራ፣ አገውና በጌምድር እየተዘዋወረ አስተምሮ ከሰሜን ተራራዎች ውስጥ እየጾመና እየ[ለየ በብሕትውና ለብዙ ዘመን ከኖረ በኋላ በሰሜናዊ ምሥራቅ በኩል ባለው በጸለምት ዋሻ ውስጥ በ571 ዓ.ም ግንቦት 11 ቀን ተሠውሯል፡፡ ይህ ቦታ በተለምዶ የሰሜን ተራሮች በሚባለው ወስጥ የሚገኝ ከፍተኛና ብርዳማ ቦታ ነው፡፡

ቅዱስ ያሬድ ለኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሰማያዊ ዜማን ከማበርከቱም ሌላ በትምህርት ሂደትም አስተዋጽዖ አድርጓል፡፡ የድጓን፣ የጾመ ድጓን የዝማሬ መዋሥዕትንና የቅዳሴን ትምህርት ከማስተማሩም በላይ ለቅኔ ትምህርትም መሠረት ጥሏል፡፡




የመላው ዓለም የተዋሕዶ ቤተሰብ

8 comments:

  1. የቅዱስ ገብርኤል ሥራ እጅግ በጣም ነው ያስደነቀኝ

    ReplyDelete
  2. ይህንን እጅግ ኣስተማሪ የሆነ ጽሁፍ ስላቀረብክልን በእውነት እግዚኣብሔር ይባርክህ።

    ReplyDelete
  3. እግዚአብር የተመሰገነ ነው ምህረቱ ለዘላለም ነው

    ReplyDelete
  4. የቅዱስ ገብርኤል ታአምር ድንቅ ነው፡፡

    ReplyDelete
  5. Besimu lamenut gena sint dink sira yadergal. Benitsihina, beyewahinet ena betiru emnet bininor sint teamir baderegin? Egziabher hulachinim keyekenu yeseytan fetena yitebiken!Amen!!!

    ReplyDelete
  6. Besimu lamenut egziabher dink yadergal. Tinish yewahinet, tinish emnet binoren enkuan sint dink neger baderegelin neber. Egziabher hulachininim lekidus sira tesatafi yadirgen!!Amen

    ReplyDelete
  7. YIHIN ASTEMARY YEEGZIABHERN DINK SIRA LEGN SILASTEMARACHIHUN EGGIBHIAR YAKBIRLIN

    ReplyDelete
  8. antewushetam gebreal betfi aymatam !

    ReplyDelete